ስለ ምን ጾምን፥ አንተም አልተመለከትኸንም?ሰውነታችንንስ ስለ ምን አዋረድን፥ አንተም አላወቅህም? ይላሉ። እነሆ፥ በጾማችሁ ቀን ፈቃዳችሁን ታደርጋላችሁ፥ ሠራተኞቻችሁንም ሁሉ ታስጨንቃላችሁ።

እነሆ፥ ለጥልና ለክርክር ትጾማላችሁ በግፍ ጡጫም ትማታላችሁ፤ ድምፃችሁንም ወደ ላይ ታሰሙ ዘንድ ዛሬ እንደምትጾሙት አትጾሙም።

እኔ የመረጥሁት ጾም ይህ ነውን?ሰውስ ነፍሱን የሚያዋርደው እንደዚህ ባለ ቀን ነውን? በውኑ ራሱን እንደ እንግጫ ዝቅ ያደርግ ዘንድ ማቅንና አመድንም በበታቹ ያነጥፍ ዘንድ ነውን? በውኑ ይህን ጾም፥ በእግዚአብሔርም ዘንድ የተወደደ ቀን ትለዋለህን?

እኔስ የመረጥሁት ጾም ይህ አይደለምን? የበደልን እስራት ትፈቱ ዘንድ፥ የቀንበርንስ ጠፍር ትለቅቁ ዘንድ፥ የተገፉትንስ አርነት ትሰድዱ ዘንድ፥ ቀንበሩንስ ሁሉ ትሰብሩ ዘንድ አይደለምን?

እንጀራህንስ ለተራበ ትቈርስ ዘንድ፥ ስደተኞቹን ድሆች ወደ ቤትህ ታገባ ዘንድ፥ የተራቈተውንስ ብታይ ታለብሰው ዘንድ፥ ከሥጋ ዘምድህ እንዳትሸሽግ አይደለምን?

የዚያን ጊዜ ብርሃንህ እንደ ንጋት ይበራል፥ ፈውስህም ፈጥኖ ይበቅላል፥ ጽድቅህም በፊትህ ይሄዳል፥ የእግዚአብሔርም ክብር በኋላህ ሆኖ ይጠብቅሃል።

የዚያን ጊዜ ትጠራለህ እግዚአብሔርም ይሰማሃል፤ ትጮኻለህ እርሱም። እነሆኝ ይላል። ከመካከልህ ቀንበርን ብታርቅ፥ ጣትህንም መጥቀስ ብትተው፥

ባታንጐራጕርም፥ ነፍስህንም ለተራበ ብታፈስስ፥ የተጨነቀውንም ነፍስ ብታጠግብ፥ ብርሃንህ በጨለማ ይወጣል ጨለማህም እንደ ቀትር ይሆናል።

እግዚአብሔርም ሁልጊዜ ይመራሃል፤ ነፍስህንም በመልካም ነገር ያጠግባል አጥንትህንም ያጠናል፤ አንተም እንደሚጠጣ ገነት፥ ውኃውም እንደማያቋርጥ ምንጭ ትሆናለህ።

ከዱሮ ዘመን የፈረሱት ስፍራዎች ይሠራሉ፥ የብዙ ትውልድም መሠረት ይታነጻል፤ አንተም። ሰባራውን ጠጋኝ፥ የመኖሪያ መንገድን አዳሽ ትባላለህ።

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
ትንቢተ ኢሳይያስ
፶፰፥፫-፲፪
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
🔔ያሬድ ክብር አነሰው🔔

ገና ጥንት ያኔ . . . .
ሰውም ሳይሰፍርባት አሜሪካ ታውቃ፣
ገና ጥንት ያኔ . . .
እንዲህ ሳትሠለጥን አውሮፓም ተራቅቃ፣
ገና ጥንት ያኔ . . .  ዓለም፣ ከእንቅልፏ ሳትነቃ፣
እነ ሞዛርት እና እነ ቤት ሆቨን፣ 
የዜማን ምልክት ገና ሳይነግሩን፣
ያሬድ አንተ ነበርክ የዜማን ቅማሬ የሠራህልን፣ . . . .
መንኮራኩር ሠርተው 
ጨረቃ ላይ ወጥተው፣ 
አፈር ስላመጡ ዓለም ተደነቀ፣
ወሬው ተሟሟቀ፣ . . . .
ከምዕራብ ተነሥቶ ከምሥራቅ ዘለቀ፣ . . . .
ከሺ ዓመት በፊት ግን ያሬድ የተባለ አንድሊቅ ነበረ፣ . . . .
ጨረቃንም አልፎ ጠፈር ተሻገረ፣ . . . .
ሐኖስን ሰንጥቆ ሰማያት ውስጥ ገብቶ፣ . . . .
አስደናቂ ዜማ ከመላእክት ሰምቶ፣ . . . .
አክሱም ላይ አዜመው 
ከጽናጽል እና ከመቋሚያ አስማምቶ፣ . . . .
ግና ምን ያደርጋል . . .
ከጨረቃ አፈር የሚበልጥ ነገር፣ . . . .
ጨረቃም ላይ ካለው የሚበልጥ ምሥጢር፣ 
ያሬድ ይዞ መጥቶ፣ . . . .
የሚናገር እና የሚያደንቅ ጠፍቶ፣ . . . .
ዓለም አያውቀውም አልሰማውም ከቶ፣ . . . .
ያሬድ ግን ቅዱስ ነው ያሬድ ምሁር ሊቅ፣ . . . .
ያሬድ መተርጉም ነው ምሥጢር የሚያረቅቅ፣ . . . .
ያሬድ ፈላስፋ ነው ያሬድ ባለ ቅኔ፣ . . . .
ያሬድ ባለ ዜማ የዜማው መጣኔ፣ . . . .
ያሬድ ሐጋጊ ነው ሥርዓት የሠራ፣ . . . .
ያሬድ መምህር ነው ዕውቀትን ያበራ፣ . . . .
ያሬድ ቀማሚ ነው ብሉይ ከሐዲስ፣ . . . .
ያሬድ ሰባኪ ነው ነፍስ የሚመልስ፣ . . . .
ያሬድ አመልካች ነው ኖታን የፈጠረ፣ . . . .
ያሬድ መናኒ ነው በጸሎት የኖረ፣ . . . .
እነ ቸርችል፣ ፑሽኪን እና ካኒንግሃም 
አደባባይ መንገድ ሲሰየምላቸው፣
ያሬድን ስላጡት አዘነ ልባቸው፣ . . . .
ነቢይ በሀገሩ አይከብርም እንዲሉ፣ . . . .
እኒህ ኢትዮጵያውያን እጅግ ይሞኛሉ፣ . . . .
የእጃቸውን ንቀው ሌላ ያከብራሉ፣ . . . .
ብለው አዘኑብን በፈጸምነው ግፍ፣ . . . .
ያሬድን ረስተን ሌላውን ስናቅፍ፣ . . . .
አይበቃም ወይ ታድያ የሞኝነት ኑሮ፣ . . . .
መቅረት አለበት ወይ ታሪኩ ተቀብሮ፣ . . . .
ይተረክ ታሪኩ ይነገር ዝናው፣ . . . .
ይጠና ይመርመር ይታወቅ ሥራው፣ . . . .
መወያያ ይሁን በየሚዲያው፣ . . . .
መማማርያ ይሁን ትውልድ ያድንቀው፣ . . . .
ያለበለዚያ ግን ያለፉትን ንቀን ወደፊት ብንሄድ፣ . . . .
እኛንም የሚንቅ ይመጣል ትውልድ . . . .

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
 ምንጭ :-
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
✞ረጅሙ ተራራ✞
🔸 @Behila_Abew 🔸
#ረጅሙ_ተራራ

#አዘጋጅ
መጋቤ ምስጢር ብሩክ አሳመነ
#ተራኪ
ኢዮብ ዮናስ

🔥 🔥 🔥 🔥 🔥 🔥 🔥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
​​💦የወለተ ሄሮድያዳ መንፈስ አሁንም በመካከላችን አለ፦

የምወዳችሁ ልጆቼ! ለወለተ ሄሮድያዳ እንዲሁም በዚህ ዘመን እርሷን ለሚመስሏት ኹሉ እናልቅስላቸው፡፡

እንዲህ ዓይነቱ ዲያብሎሳዊ ግብር አሁንም በስፋት እየተፈጸመ ይገኛልና ለወለተ ሄሮድያዳና ወለተ ሄሮድያዳውያን እናልቅስላቸው፡፡

ምንም እንኳን በዚህ ዘመን ዮሐንስ አንገቱ ባይሰየፍም፥ ከዚህ በባሰ መልኩ ግን የክርስቶስ ሕዋሳት እየተሰየፉ ነው፡፡

በዘፋኞቹ ያደረው ርኵስ መንፈስ የሚጠይቀው እንደ ወለተ ሄሮድያዳ የሥጋን አንገት አይደለም፤ የነፍስን እንጂ፡፡

ዘፋኞች በቅድሚያ ሰዎች የነርሱ ባርያ (አድናቂ) ያደርጓቸዋል፡፡

በመቀጠልም በዘፈኖቻቸው አማካኝነት እነዚህን ነፍሳት በፍትወት እንዲቃጠሉ ያደርግዋቸዋል፡፡ ዝሙት እንዲሠሩም ያበረታቱዋቸዋል፡፡

ባርያዎቹም (አድናቂዎቹ) በዚህ ግብራቸው የሚጠየቁት የሥጋ አንገታቸውን አይደለም፡፡

ዘማውያን፣ ለነፍሳቸው ግድ የሌላቸው ልል ዘሊል እንዲሁም አመንዝራ እንዲኾኑ በማድረግ የነፍሳቸውን አንገት እንጂ፡፡

ወዳጄ ሆይ! ወይንን በመጠጣት ሰክረህ ሳለ አንዲት ቆንጆ ሴት በፊትህ መጥታ ብትዘፍን፥ እንዲሁም አንተን በሚያማልልና በሚያንቆለጳጵስ ቃላት እያናገረችህ “ምንም ዓይነት ፍትወት አይነሣብኝም፡፡ ከእርሷ ጋር ለመዘሞት አልነሣሣም፡፡ ክብረ ንጽህናዬንም አላጐድፍም” ብለህ በፍጹም ራስህን አታታልል፡፡

ዲያብሎስ በእርሷ አምሳል በፊትህ የቆመው የክርስቶስ ብልት የኾነው ሥጋህን የጋለሞታን ብልት ለማድረግ እንደኾነ ዕወቅ፤ ተረዳም /1ኛ ቆሮ.6፡15/፡፡

ምንም እንኳን ዛሬ ወለተ ሄሮድያዳ በአካለ ሥጋ ባትኖርም፥ እርሷን ያስዘፈናት ዲያብሎስ ግን አለ፡፡

አሁንም ብዙዎችን እንዲዘፍኑና ክሳደ ነፍሳቸውን ለመቅላት የሚቀሰቅሳቸው እርሱ ነውና በፍጹም ራስህን አታታልል፡፡

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
​​💦ምክር ከጠቢቡ ሰለሞን

ልጄ ሆይ፥
💧ሕጌን አትርሳ፥ ልብህም ትእዛዛቴን ይጠብቅ።
ብዙ ዘመናትና ረጅም ዕድሜ ሰላምም ይጨምሩልሃልና።

💧ምሕረትና እውነት ከአንተ አይራቁ፤ በአንገትህ እሰራቸው፤ በልብህ ጽላት ጻፋቸው።
በእግዚአብሔርና በሰው ፊትም ሞገስንና መልካም ዝናን ታገኛለህ።

💧በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታመን፥ በራስህም ማስተዋል አትደገፍ፤
በመንገድህ ሁሉ እርሱን እወቅ፥ እርሱም ጎዳናህን ያቀናልሃል።

💧በራስህ አስተያየት ጠቢብ አትሁን፤ እግዚአብሔርን ፍራ፥ ከክፋትም ራቅ፤
ይህም ለሥጋህ ፈውስ ይሆንልሃል፥ ለአጥንትህም ጠገን።

💧እግዚአብሔርን ከሀብትህ አክብር፥ ከፍሬህም ሁሉ በኵራት፤
ጐተራህም እህልን ይሞላል፥ መጥመቂያህም በወይን ጠጅ ሞልታ ትትረፈረፋለች።

ልጄ ሆይ፥
💧የእግዚአብሔርን ተግሣጽ አትናቅ፥ በገሠጸህም ጊዜ አትመረር።
እግዚአብሔር የወደደውን ይገሥጻልና፥ አባት የሚወድደውን ልጁን እንደሚገሥጽ።

💧ጥበብን የሚያገኝ ሰው ምስጉን ነው፥ ማስተዋልንም ገንዘቡ የሚያደርግ፤
በወርቅና በብር ከመነገድ ይልቅ በእርስዋ መነገድ ይሻላልና።
ከቀይ ዕንቍም ትከብራለች፥ የተከበረም ነገር ሁሉ አይተካከላትም።
በቀኝዋ ረጅም ዘመን ነው፥ በግራዋም ባለጠግነትና ክብር።
መንገድዋ የደስታ መንገድ ነው፥ ጎዳናዋም ሁሉ ሰላም ነው።
እርስዋ ለሚይዙአት የሕይወት ዛፍ ናት፥ የተመረኰዘባትም ሁሉ ምስጉን ነው።

💧እግዚአብሔር በጥበብ ምድርን መሠረተ፥ በማስተዋልም ሰማያትን አጸና።
በእውቀቱ ቀላያት ተቀደዱ፥ ደመናትም ጠልን ያንጠባጥባሉ።

ልጄ ሆይ፥
💧እነዚህ ከዓይኖችህ አይራቁ፤ መልካም ጥበብንና ጥንቃቄን ጠብቅ።
ለነፍስህም ሕይወት ይሆናሉ፥ ለአንገትህም ሞገስ።
የዚያን ጊዜ መንገድህን ተማምነህ ትሄዳለህ፥ እግርህም አይሰነካከልም።
በተኛህ ጊዜ አትፈራም፤ ትተኛለህ፥ እንቅልፍህም የጣፈጠ ይሆንልሃል።
ድንገት ከሚያስፈራ ነገር፥ ከሚመጣውም ከኃጥኣን ጥፋት አትፈራም፤
እግዚአብሔር መታመኛህ ይሆናልና፥ እግርህም እንዳይጠመድ ይጠብቅሃልና።

💧ለተቸገረው ሰው በጎ ነገርን ማድረግ አትከልክል፥ ልታደርግለት የሚቻልህ ሲሆን።
ወዳጅህን። ሂድና ተመለስ፤ ነገ እሰጥሃለሁ አትበለው። በጎ ነገርን ማድረግ ሲቻልህ።

💧በወዳጅህ ላይ ክፉ አትሥራ፥ እርሱ ተማምኖ ከአንተ ጋር ተቀምጦ ሳለ።
ከሰው ጋር በከንቱ አትጣላ፥ እርሱ ክፉ ካልሠራብህ።

💧በግፈኛ ሰው አትቅና፥ መንገዱንም ሁሉ አትምረጥ።

💧ጠማማ ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት ርኩስ ነውና፤ ወዳጅነቱ ግን ከቅኖች ጋር ነው።

💧የእግዚአብሔር መርገም በኃጥእ ቤት ነው፥ የጻድቃን ቤት ግን ይባረካል።

💧በፌዘኞች እርሱ ያፌዛል፥ ለትሑታን ግን ሞገስን ይሰጣል።

💧ጠቢባን ክብርን ይወርሳሉ፤ የሰነፎች ከፍታቸው ግን መዋረድ ነው።

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
መጽሐፈ ምሳሌ
ምዕራፍ ፫፥፩-፴፭
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
"ክፉ ሥራ ካልሠራን በቀር ጠባቂ መልአካችን ከእኛ አይለይም፡፡

ጭስ ንብን ከቀፎው እንዲወጣ እንደሚያደርገው ኹሉ የእኛ ኃጢአትም ጠባቂ መልአካችን ከእኛ እንዲለይ ያደርገዋል" ብሏል፡፡


💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያ
ሰውን ስለሚጠብቁ መላእክት ሲናገር ፦
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
መስቀል ኃይላችን ነው።
ኃይላችን መስቀል ነው።
የሚያጸናን መስቀል ነው።
መስቀል ቤዛችን ነው።
መስቀል የነፍሳች መዳኛ ነው።
አይሁድ ይክዱታል እኛ ግን እናምነዋለን።
ያመነው እኛም በመስቀሉ እንድናለን ድነናልም።

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
የሃይማኖት ጸሎት
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
አዘክሪ ድንግል
@Behila_Abew
የምዕራፈ ጻድቃን አቡነ ገብረመንፈስቅዱስ ካቴድራል

በኆኅተ ጽድቅ ሰ/ት/ቤት ኪነ ጥበብ ክፍል ተዘጋጅቶ የቀረበ

#መነባንብ

#አዘክሪ_ድንግል

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
 አብሬሽ_ልመለስ

በስመአብ ወወልድ ወመንፈስቅዱስ አሐዱ አምላክ
አሜን!!!

ከክብር ማረፊያው ከገሊላው ቤትሽ
ሰማሁ መፍለስሽን ወደ ግብጽ ወደ ኩሽ
ፀሐይ ሲያከትራት ያቺን የበረሃ ዖፍ
ጼዋዌን ስትናፍቅ ላንዲት ቅጽበት ሳታርፍ
ሰማሁኝ ስደቷን መጠጊያ ሳታገኝ በልቤ ላይ ስታልፍ
....ፈላሲተ ቁስቋም ወዴት ነው ሀገርዋ
ኀበ ሖረት ላቲ በብካይ እትልዋ

ናዛዚት እም ኃዘን ሁሉ ያላት ለማኝ
የምድረ በዳ ዖፍ ጎጆዋን እስካገኝ
መኃልየ ብካይ ኃዘንዋ እየሆነኝ
..... እፈልጋታለሁ
እፈልጋታለሁ....እፈልጋታለሁ
እንዲያም ያጣኋት ለት..... ፈልጊኝ እላለሁ
አልያማ
ያለ ምዕራፈ ክብር....ያለ ነፍሴ አስኬማ
ያለ ብሔረ ሰላም ....ያለ ጽድቅ ከተማ
ያለ ጽናት አክሊል ..... ያለ ፍቅር ማማ
ምሕረትን ሲርበኝ ..... ይቅርታን ስጠማ
ከበረሃ እንዳልቀር .... ድምጼ ሳይሰማ
..... እፈልጋታለሁ
እፈልጋታለሁ....እፈልጋታለሁ
እንዲያ ያጣኋት ለት..... ፈልጊኝ እላለሁ
ዋዕየ ፀሐይ ዘመዓልት.... ክምር ኃጢዓቴን ንጄ
የሌሊቱን ቁረ ገዳም ... ፈቃደ ሥጋውን ክጄ
ካንቺው ጋራ ልመለስ ..... ከግብጽ ተሰድጄ

" ውስተ ርስትኪ ሰድኒ... እም ብኄረ ዓለም ባዕድ
በቤተልሔም ቤትኪ …..አልቦ አመጻ ወሃይድ "
አ...ብ...ር...ሬ...ሽ.... አይደለም አብሬሽ ልመለስ
ክብርሽን አክብሬ ውድሽን ሳወድስ
.... እያልኩ ሥሉስ ቅዱስ
ሥጋ ዓለሜን ጥዬ ከነፍስ ሀገር ልድረስ
አ...ብ...ር...ሬ...ሽ.... አይደለም አብሬሽ ልመለስ
የነፍሴ ወደቧ ወደ ልጅሽ ልድረስ
ያለ እርሱ እምነት የለም ያላንቺም ክርስቶስ
አ...ብ...ር...ሬ...ሽ.... አይደለም ካንቺው ጋር ከኋላ
መርተሽ አሳርፊኝ በብሔረ ተድላ
ለፈጣሬ ዓለማት አንቺ ነሽ መጾሩ
ለተስፋ ስዱዳን ህጽንሽ ነው አገሩ
የጢሮስ አምኃ ... ከቤተልሔም ግብጽ 
... ተከትሎሽ ሲፈልስ
ከግብጽ ቤተልሔም .... ካንቺ ጋር ሲመለስ
የልጅሽ ፍጥረቱ እኔም ከዚያ እንዳላንስ
ምን ባልገባ እንኳን ስምሽን ባልቀድስ 
..... ልጅሽን ባላወድስ
ጠልተሽ አትጣይኝ ፍኖትሽን ሳስስ
እነሆ ልጅ ልባል ጎልጎታ ልድረስ
አ...ብ...ር...ሬ...ሽ.... አይደለም አብሬሽ ልመለስ
ትተሺኝ አትውጪ ውስተ ምድረ ነኪር
ስደትን ታውቂያለሽ ተሰድጄ እንዳልቀር
መከራን ታውቂያለሽ ተመክሬ እንድኖር
አብሬሽ ልመለስ ወደ ነፍሴ ደብር
እንዳትረሺኝ ከመንገዱ .... አንቺ ቀሊል ደመና
ጥለሽኝ አትሂጂ ከበረሃው .... አማናዊት የሲና መና
በእቅፍሽ ያለው ህብስተ ሕይወት .... የምሕረት ዝናብ ነውና
ዘመንሽ ነውና ዘመኑ .... መጠንሽም ነውና መጠኑ
ለሥጋ ማረግ መሰላሉ .....ለቃል መውረድም ዙፋኑ
ያላንቺማ "እስከማዕዜኑ..."
እንዲህ እየተከዙ እንድያም እያዘኑ...
ጽድቅን እየገፉ ፍዳ እየመዘኑ
ያላንቺማ "እስከማዕዜኑ..."
በንሰሐ እንባ ኃጢአትን ሳይከድኑ
ከነአንን ናፍቀው ግብጽን ቢኮንኑ
ከስጥመተ-ባህር ከጥፋት ላይድኑ
ከሀገር ተለይተው በስደት ቢጸኑ
ያላንቺማ "እስከማዕዜኑ..."
የበጎቹ መሰማርያ..... እምነ ጽዮን እያሉ
ካንቺ ነውና ሚጠለሉ ..... ከእቅፍሽ ነውና ሚውሉ
መፈውስ ነሽና ለቁስለ ነፍስ .....እባክሽን አዛኝቱ
አስከትለሽው ተመልሽ ልጅችን ጥሪው ለቤቱ
ሊቁ እንደነገረን ....
"ብጹዕ ዘርእየኪ በህልሙ ሌሊተ
አመ ትበርቂ በደብረ ምጥማቅ ሐምሰ ዕለታተ"
እኔም ደሞ ናፍቃለሁ ....አንዲት ነገር ልለምንሽ
በነፍሴ ላይ ስትበርቂ.... ጽልመት ግብሬ ፈርቶ እንዲሸሽ
አንድ ጊዜ ባይነ-ልቤ.... ላንዲት ቅጽበት በህልሜ ልይሽ
.....ልመለስ አብሬሽ!

🔔ምንጭ
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
በዲ/ን ዶ/ር ቴዎድሮስ በለጠ
መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ቅዳሜ ኅዳር 6 ቀን፣ 2007 ዓ.ም
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
የአባቶቻችን አምላክ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን፡፡
እርሱ ምስጉን ነው ለዘላለምም ምስጉን ነው፡፡

የተቀደሰ የጌትነቱም ስም ይክበር ይመስገን፡፡
አርሱ ምስጉን ነው በዓለምም ሁሉ ልዑል ነው፡፡

ቅዱስ በሆነ በጌትነትህ መቅደስ አንተ የተመሰገንህ ነህ፡፡
አንተ ምስጉን ነህ ለዘላለምም የከበርህ ነህ፡፡

በኪሩቤል ላይ ሆነህ ጥልቆችን የምታይ አንተ የተመሰገንህ ነህ፡፡
አንተ ምስጉን ነህ ለዘላለምም ልዑል ነህ፡፡

በጌትነትህ ዙፋን ላይ አንተ የተመሰገንህ ነህ፡፡
አንተ ምስጉን ነህ ለዘላለምም ቡሩክ ነህ፡፡

ከሰማዮች በላይ ባለው አንተ የተመሰገንህ ነህ ።
አንተ ምስጉን ነህ፡፡
ለዘላለምም ክቡር ነህ፡፡

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🤲(የአናንያ የአዛርያ የሚሳኤል ጸሎት)

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
💦የወንጌል ገበሬ💦

እግዚአብሔር...
ሊያድነን ፈልጎ ምሕረትን ሲያበዛ
ምክንያት ሲፈጥርልን ለነፍሳችን ቤዛ
ገና ከማኅጸን ወዶ የመረጠው
ለክብር የታጨ ባርኮ የቀደሰው
አባታችን...
ተክለአብ ተክለወልድ ተክለመንፈስቅዱስ
ኃጢአትን አክስሮ በይቅርታ የሚክስ
ለኛ የተፈጠረ የወንጌል ገበሬ
ተድበስብሶ እንዳይቀር ብስሉ ከጥሬ
በሃይማኖት መንሹ አብጠርጥሮ የለየ
እምነቱ የጸና በተጋድሎ የቆየ
ዛሬም...
ዛሬም ቃልኪዳኑ ተርፎ ዓለምን አጥግቧል
ተክለሃይማኖት ብለን የጎደለው ይሞላል
በጻድቁ አባት ጥላ ሁሉም አልፏል
ቃሉ ለማይሻር አምላክ ምን ይሳናል

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
📚 ስናነብ ካገኘነው፦📚
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
​​💦የተስፋው ቃል💦

በአንዲት ፍሬ ቅጠል ሕይወትን አጥቼ
እርስቴን ተነጠቅኩ የሞት ሞትን ሞቼ
በግዞት ተነዳሁ በድቅድቅ ጨለማ
ወደ ፍዳ መንደር ወደ ሞት ከተማ
የተስፋውን ቃል በልቤ ቋጥሬ
ለዲያብሎስ ግብር ሆንኩት ጋሻ አጃግሬ
የባርነት ቀንበር ፍላፃው በርትቶ
በበርባኖስ መሃል ብርሃኔ ጠፍቶ
የመከራው ዘመን በእኔ ላይ አድርቶ
ዙሪያዬን ተብትቦኝ ሆነብኝ ድሪቶ
እሾህ አሜኬላው ነግሶብኝ ሠልጥኖ
የጽዴቅ ስራዬም የመርገም ጨርቅ ሆኖ
ነፍሴ ብትቃጠል ስጋዬም ቢጠፋኝ ከመሬት ተቀብሮ
5500 ዘመን ድምጼን ከፍ አድርጌ አሰማሁ እሮሮ
ትንቢቱ ተሠብኮ ግዜው ተፈጽሞ
ያ . . . የተስፋው ቃል ነጋሪት ጎስሞ
የምስራች ዜና ድኅነትን አብስሮ
ሕይወትን ለሰጠኝ ሞትን በሞት ሽሮ
በንግል ማህፀን ሥጋን ተዋህዶ
ከሰው ልጆች አንሶ እራሱን አዋርዶ
መንበረ ፀባኦት ማደሪያውን ትቶ
አገኘሁት ዛሬ ከበረት ተኝቶ

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
ከጥበብ ወተውኔት ጥራዝ
ገጽ 71
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
💦 ጾም 💦

"ጾም መድኃኒት ናት፡፡ አወሳሰድዋን በትክክል ላላወቁ ግን ጥቅም የላትም፡፡

ይህችን መድኃኒት የሚወስድ ሰው በየስንት ሰዓቱ እንደምትወሰድ፣ በምን ያህል መጠን (Dosage) እንደምትዋጥ፣ ለምን ዓይነት በሽታ እንደምትጠቅም፣ በየትኛው ወራትና በየትኛው የአየር ሁናቴ እንደምትወሰድ፣ ከእርሷ ጋር የሚሄዱና የማይሄዱ ምግቦችን እንዲሁም ሌሎች ከእርሷ ጋር የማይስማሙ ነገሮችን ለይቶ ማወቅ አለበት፡፡

እነዚህን ግምት ውስጥ አስገብተን የማንወስዳት ከሆነ ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ያመዝናል፡፡

አንድ በሐኪም የታዘዘልንን የደዌ ሥጋ መድኃኒት በትክክል ከወሰድነው ከሕመማችን እንፈወሳለን፤ የነፍሳችንን ደዌ ለመፈወስ ብለን በምንወስደው መድኃኒት ደግሞ ከዚህ የበለጠ መጠንቀቅ አለብን፡፡

ጾም ሁለመናችንን የምንለውጥበት መሣርያ ነው፡፡ምክንያቱም የጾም መሥዋዕት ማለት ከምግብ ብቻ መከልከል ሳይሆን ከኃጢአት ሁሉ መከልከል ነውና፡፡

ስለዚህ እየጾምኩ ነው እያለ ራሱን ከምግብ ብቻ የሚከለክል ሰው ካለ እርሱ ጾምን እያቃለለና እያጥላላ ነው ማለት ነው፡፡ እየጾማችሁ ነው? እንግዲያስ መጾማችሁን በተግባር አሳዩኝ፡፡ “እንዴት አድርገን እናሳይህ?” ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡

እኔም እንዲህ ብዬ እመልስላችኋለሁ፡- ደሀው እርዳታችሁን ፈልጎ እንደሆነ ቸርነትን አድርጉለት፤ የጠላችሁት ሰው ካለ ፈጥናችሁ ታረቁ፤ ባልጀራችሁ ተሳክቶለት ስታዩት በእርሱ ላይ ቅናት አትያዙ፤ ቆነጃጅትን በመንገድ ሲያልፉ ስታዩ በዝሙት ዓይን አትመኙ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያደረጋችሁ በትክክል መጾማችሁን አሳዩኝ፡፡

በሌላ አገላለጽ አፋችሁ ብቻ ሳይሆን ዐይኖቻችሁ፣ እግሮቻችሁ፣ እጆቻችሁና የሰውነታችሁ ሕዋሳቶች በሙሉ መጾም አለባቸው፡፡

እጆቻችሁ ከመስረቅና የእናንተ ያልሆነውን ከመውሰድ ይጹሙ፤ እግሮቻችሁ የኃጢአት ሥራን ለመፈፀም ከመፋጠን ይጹሙ፤ ዐይኖቻችሁ ውጫዊ በሆነ ውበት ምክንያት ከመቅበዝበዝ ይጹሙ፡፡

ጥሉላትን (የፍስክ ምግብ) እየበላችሁ አይደለም አይደል? እንግዲያስ በዐይኖቻችሁም ክፉ ነገርን አትብሉ፡፡ የሚታዩ ነገሮች ለዐይን ምግቦች ናቸውና፡፡ ጀሮዎቻችሁም ይጹሙ፡፡
የጆሮ ጾም ሐሰተኛ ወሬንና ሐሜትን አለመስማት የመሳሰለ ነው፡፡

አንደበታችሁም ከከንቱ ንግግር ይጹም፡፡ ዓሣንና ሌሎች ጥሉላትን ከመብላት ተከልክለን ሳለ ነገር ግን ወንድሞቻችንን በሐሜት የምናኝካቸውና የምንበላቸው ከሆነ ምን ጥቅም አለው? ወንድሙን የሚያማና የሚነቅፍ ሰው እርሱ የወንድሙን አካል ያቆስላል ሥጋውንም ይበላል፡፡

ለዚህም ነው ሐዋርያው ይህን አስመልክቶ  እጅግ የሚያስደነግጥ ንግግርን እንዲህ ሲል የተናገረው፡- "እርስ በእርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በእርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ።"ገላ፭፥፲፭

ስታሙ በጥርሳችሁ የወንድማችሁን ሥጋ አትነክሱም፡፡ በክፉ ንግግራችሁ ግን የወንድማችሁን ነፍስ ትነክሳላችሁ፤ ታቆስሉትማላችሁ፡፡ እንዲህ በማድረጋችሁ ራሳችሁን፣ ወንድማችሁንና ሌሎች ብዙ ሰዎችን ትጎዳላችሁ፡፡

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
💦ትንቢተ ዮናስ💦

በህዝብዋ መካከል ዓመጽ ስለ ፀና
በጣም ተቆጥቼ አዝኛለሁና
ይህን ለነነዌ ንገራት በአዋጅ
አለና ለዮናስ ለአሚታይ ልጅ
እግዚአብሔር አዘዘው እንዲሄድ በቶሎ
ዮናስ እምቢተኛው አሰበ ኮብልሎ
ከአምላክ ተደብቆ አምልጦ ሊጠፋ
ወደ ተርሴ ሊጓዝ ፤ ሄደ ወደ ያፋ
ዋጋ ከፈለና በመርከብ ተሳፍሮ
አያጉረመረመ ባህሩን ተሻግሮ
ዮናስ ተደብቆ ሊሄድ በግስገሳ
ከእግዚአብሄር ተልኮ ማዕበል ተነሳ
ታላቅ ሞገድ ሆኖ ባህሩ ተቆጣ
መርከበኞች ፈሩ ትልቅ ሽብር መጣ
መርከቡ እንዲቀለው እናድርግ እያሉ
አንስተው ብዙ እቃ ወደ መርከብ ጣሉ
ባህሩም ባሰበት በጣም ተናወጠ
መርከከቡ መሰለ የተገለበጠ
ሰው ሁሉ ተነሳ ጸሎት ለማድረስ
ይህ ሁሉ ሲሆን ተኝቷል ዮናስ
ወደ ዮናስ ሄዶ የመርከቡ አለቃ
ቀሰቀሰው እና ከእንቅልፉ ሲነቃ
እግዜር እንዲያድነን ከዚህ ክፉ ጥፋት
ተነስ ፀልይ አለው ይብቃህ ማንቀላፋት
በመርከብ ውስጥ ያሉ ሰዎች ተሰብስበው
ተመካከሩ እና በነገሩ አስበው
አለ ኃጢአት ሰርቶ ከእኛ ጋር የመጣ
ለይተን ለማወቅ እንጣጣል እጣ
አለዚያ አንድንም ስለተባባሉ
ተሰበሰቡ እና እጣ ሲጣጣሉ
እውነትም እንዳሉት አጥፊው ሰው ታወቀ
በእንቢተኛው ነብይ በዮናስ ወደቀ
ዮናስ ተረዳና እጁ እንደተያዘ
ያጠፋውን ጥፋት ገልፆ ተናዘዘ
ምነው ባትመጣ ተጣልተህ ከጌታ
እየው መርከባችን እንደሚንገላታ
ቁጣው እንዲታገስ ለማግኝት ጸጥታ
በል አንተው ፍረደን ምን ይበጃል ቢሉ
ዮናስ መለሰና እዚህ ያለህ ሁሉ
ስለምን ይጠፋል በኔ የተነሳ
ወደ ባህር ጣሉኝ አለብኝ አበሳ
ተመልከቱ እነሆ ስራውን አወቀ
ጥፋቱን ገለጠ ይህው መች ደበቀ
እሱ ከፈረደ መልሶ በራሱ
ምን እናድግ ብለው ሊጥሉት ተነሱ
ከደሙ አንፃን ሲሉ ለእግዜር አመልክተው
ወደ ባህር ጣሉት ዮናስን አንስተው
በዮናስ ላይ ኖሮ የመጣው ይህ መዓት
ባሕሩ ፀጥ አለ ልክ በዚያው ሰዓት

ምዕራፍ 2

ይቀጥላል.....
💥 💥💥ምንጭ፦ ከዶክተር💥💥 💥
ከበደ ሚካኤል (1999 ዓ.ም)
"የዕውቀት ብልጭታ"

ከሚለው መፅሀፍ የተወሰደ
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
💦ትንቢተ ዮናስ 💦

ምዕራፍ 2

ዮናስን እንዲውጥ ሕይወቱን ሳይጎዳ
አንድ ትልቅ አሳ እግዜር አሰናዳ
ዮናስም ተውጦ በእግዚአብሔር ፍቃድ
ሦስት ቀን ሦስት ሌሊት ሲያድር በአሳ ሆድ
ተቀይመህ ኖሮ ከላይ ብተቆጣ
ይህን ያህል መዓት በራሴ ላይ መጣ
የባህሩ ሞገድ እኔን አዋከበኝ
ውሀና ጨለማ ሲኦልም ከበበኝ
አያለ በአሳ ሆድ ዮናስ ሲቀመጥ
አምላኩን ለመነው በመለማመጥ
የታዛዥነትም ጠባይ እያሳየ
አዝኖ ተጸጽቶ ከልቡ ጸለየ
ምን ጊዜመ ቢቆጣ ነው እና መሓሪ
ፊቱን መልሶለት ታረቀው ፈጣሪ
አሳውም ዮናስን ውጦ ሳያስቀረው
ከባህር ተፋና መሬት ወረወረው

ምዕራፍ 3

ይህንን የእኔን ቃል ስማና በቶሎ
ሄደ ለነነዌ እንድትነግራ ብሎ
ደገመና እግዚአብሄር ዮናስን አዘዘ
ነነዌ ሊገባ ዮናስ ተጓዘ
ድምጹን ከፍ አድርጎ ነብዩ ዮናስ
" ከዛሬ ጀምሮ አርባ ቀን ድረስ
ነነዌ ጠፊ ነች ከሥር ተገልብጣ "
አለና ለፈፈ የእግዚአብሔርን ቁጣ
ሳያንገራግሩ ሁሉም ስላመኑ
የነነዌ ሰዎች ተጨነቀው አዘኑ
ከትልቅ ጀምሮ ህጻኑ ድረስ
ሕይወቱ የቆመች በስጋ በነፍስ
ሰውም ሆነ እንስሳ ይቀበል ንስሓ
ፍጡር ሁሉ ይጹም ይለይ ከእህል ውኃ
ሁሉም ከልብ አዝኖ ማቅ እየለበሰ
ከክፉ ወደ ደግ እየተመለሰ
መቼም ወሰን የለው እግዚአብሔር ምሕረቱ
ይጸልይ አለና ይለምን በብርቱ
ንጉሡ አሳወጀ ከነመኳንንቱ
የነነዌ ሰዎች በውነት ከልቦና
መጸጸታቸውን እግዚአብሔር አየና
ፍጡር ቢለምነው እንባ እያፈሰሰ
ምህረቱን አውርዶ መዓቱን መለሰ

ምዕራፍ 4

ይቀጥላል.....
💥💥💥 ምንጭ፦ ከዶክተር💥💥💥
ከበደ ሚካኤል (1999 ዓ.ም)
"የዕውቀት ብልጭታ"

ከሚለው መፅሀፍ የተወሰደ
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
💦ትንቢተ ዮናስ 💦

ምዕራፍ 4

የተናገረው ቃል ስላልተፈጸመ
ዮናስ ተቆጥቶ እያጉረመረመ
እኔን መጀመሪያ ነነዌ ለመላክ
አስበህ ብታዘኝ ይህንኑ ዐውቄ
ወደ ተርሴስ ልሄድ ጠፋሁ ተደብቄ
ምህረትህ የበዛ መሐሪና ታጋሽ
በደል የምትረሳ ከቁጣ ተመላሽ
የቁጣህን ያህል ምሕረትህ የጠና
መሆንህን ጥንቱንም እኔ አውቄአለሁና
እኔን ግን ግደለኝ ልሙት ልቀበር
ሀሰት ተናግሬ የማይሆን ነገር
አልፈልግምና ቆሜ ለመኖር
ከከተማ ወጥቶ በምስራቅ በኩል
ከወደ ዳር ሆኖ ነነዌን ሊያስተውል
ምን እንደሚያገኛት ለማየት ዮናስ
ተሰርቶ ተቀመጠ አንዲት ትንሽ ዳስ
እግዜር በጥበቡ አንድ ቅል አብቅሎ
ቅሉም አደገና ከፍ ከፍ ብሎ
የዮናስ ራሱ እንዲያገኝ ጥላ
ከፀሐዩ ንዳድ ሆለት ከለላ
በዚህ በቅል ነገር ዮናስ ደስ አለው
እንዲህ ቶሎ ደርሶ ስላገለገለው
እግዜር በማግስቱ ጧት በማለዳ
ቅል የሚበላ ትል ፈጠረ አሰናዳ
ትሉ ቅሉን በልቶ በፍጥነት  ደረቀ
ፀሐይ ወጣችና ጊዜው በጣም ሞቀ
እግዜር አዘነና ትኩስ ንፋስ መጣ
የሚከለልበት መጠጊያ ስላጣ
ቅሉ ደረቀና ንዳድ ቢያቃጥለው
ዮናስ ተበሳጭቶ ለአምላክ እንዲህ አለው
እንደዚህ ሆኜ ቆሜ ከመኖር
እባክህ ግደለኝ ልሙት ልቀበር
ደረቀብኝ ብለህ ይህን ቅል በማጣት
እውን ይገባል ሆይ ያንተ እንዲህ መቆጣት?
ብሎ እግዜር ቢጠይቅ መለሰ ዮናስ
በንዴት ብዛት እስክሞት ድረስ
አዎን ይገባኛል መናደድ መጤስ
እግዜርም መለሰ ለምን ጠፋ ስትል
ይህ ያለፋህበት ያልደከምክበት ቅል
አንተ ስትናደድ ፈጥሬያት እኔማ
ሳጠፋት ሳፈርሳት ነነዌን ከተማ
መቶ ሀያ ሺህ ነው የህዝቧ ብዛት
ለምን ትቆጣለህ እኔ ባዝንላት
ብሎ በምሳሌ ሲያስተምር ይቅርታ
ለዮናስ ነገረው የምህረቱ ጌታ
ለእግዚአብሔር ቸርነት ምስጋና ይድረስ
በዚህ ተፈፀመ ትንቢተ ዮናስ

💥💥💥 ምንጭ፦ ከዶክተር💥💥💥
ከበደ ሚካኤል (1999 ዓ.ም)
"የዕውቀት ብልጭታ"
ከሚለው መፅሀፍ የተወሰደ
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
መንፈሳዊ ግጥሞች እና ብሂሎች pinned «በስመአብ ወወልድ ወመንፈስቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። ፭፻፺፫ በስ ፸፯ ከካህናት ወገን ማንም ቢሆን በ፵ ጾም በአርብና በረቡዕም ጾም ወይን መጠጣት አይገባውም፡፡ወደ መዋት (ውሽባ ቤት) አይግባ፡፡ ዐቢይ ጾም ወራት ሰው ሚስቱ ጋር አይተኛ፡፡ . . . ፭፻፺፮ ክብርት በምትሆን በ፵ ጾም በመጀመሪያው ሱባዔ ፀሐይ እስኪገባ ድረስ ይጹሙ:- መጀመሪያው ሱባዔ ካለፈ በኋላም እስከ ፲፩ ሰዓት ድረስ ይጹሙ፡፡…»
✍️ "አሁን እየጾምክ ነው? እስቲ ጾምህን በተግባር አሳየኝ? የቱን ሰራህ? ድሃውን ባየህ ጊዜ ምህረትን አሳየው፤ ጠላትህን ስታየው ታረቀው፤

ስኬታማ የሆነ ወንድምህን ስታየው አትቅናበት በመንገድ የምትሔድ ሴትን ስታይ ዝም በለህ እለፋት፤

በአጠቃላይ አፍህ ብቻ አይጹም ነገር ግን ዓይንህ፣ እግርህ፣ እጅህ ሁሉም አካልህ ይጹም፤ እጅህ ከመስረቅና ከስስት ይጹም፣

እግሮችህ ወደ ኃጢአት ከመጓዝ ይከልከሉ፣ አይኖችህም በሌሎች ሰዎች ውበት ላይ ተተክለው ከመዋል ይጹሙ፤

አሁን ስጋ እየበላህ አይደለም አይደል? በዓይንህም መጥፎ ነገር አትመልከት፤ መስማትንም ጹም፤ የፈውስ ጾም ክፉን አለመስማት የሌሎችንም ስም አለማጥፋት ነው፤

አንደበትም ከክፉና ከአጸያፊ ንግግር ይጹም፤ የዶሮና የአሳ ስጋ ከመብላት እንከለከላለን ነገር ግን የወንድማችንን ስጋ ስናኝክና ስንበላ እንውላለን፤ የወንድሙን ስጋ የሚበላ ደግሞ የተረገመና አሳች ነው፤ ቅዱስ ጳውሎስ "ነገር ግን እርስ በርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ" እንዳለን።
📖ገላ 5፥15

💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥
✍️ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
💥 💥 💥 💥 💥 💥 💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
ይህቺን ዓመት ተወኝ

ከዓመት እስከ ዓመት ፍሬን ሳላፈራ ደረቅ እንደሆንኩኝ

በራድ ወይም ትኩስ ሁለቱንም ሳልሆን እንዲያው ለብ እንዳልኩኝ ፤
አለሁኝ በቤትህ ለሙን መሬትህን እያጎሳቆልኩኝ ፤

አውቃለሁ አምላኬ ፍሬዬን ለመልቀም እንዳመላለስኩህ ፤
ዛሬም ሳላፈራ እሾህን አብቅየ ደርቄ ጠበኩህ ፤

ያልተደረገልኝ ያላፈሰስክብኝ ያልሰጠኸኝ የለም ፤
ነገር ግን ይህ ሁሉ አላርምህ አለኝ አልለየኝም ከዓለም
የማትሰለቸኝ ሆይ ተነስቼ እስክቆም እባክህ ታገሰኝ ፤
የኔን ክፋት ተወው መልአክህን ሰምተህ ይችን ዓመት ተወኝ ።

አውቃለሁ ታውቃለህ ቀጠሮን ሰጥቼ እንደማላከብር፤
ብዙ ግዜ አቅጄ ብዙ ጊዜ ዝቼ በወሬ እንደምቀር ።

ዘንድሮስ እንዳልኩኝ አምና ይኼን ጊዜ ሰምተኸኝ ነበረ፤
ምንም ሳልለወጥ ዘንድሮዬ አልፎ በአዲስ ተቀየረ

ፍሬ የማይወጣኝ እኔን በመኮትኮት እጆችህ ደከሙ ፤
እኔ ግን አለሁኝ ዛሬም አልበቃኝም በኃጢአት መታመሙ ።

የቃልህን ውሃ በድንጋይ ልጅህ ላይ ሳትታክት ስታፈስ ዘመን ተቆጠረ ፤
ወደልቤ ሳይሰርግ ህይወቴን ሳይለውጥ እንዲያው ፈስሶ ቀረ

ቃልህን ጠግቤ እያገሳሁት ነው ሌሎች እስኪሰሙ ፤
በቃልህ መኖር ግን አልያዝህ አለኝ ከበደኝ ቀለሙ ።

ብዙ ጥቅስ አገኝሁ ከቅዱስ መጽሐፍህ ገልጬ አይቼ ፤
ከራሴ ላይ ብቻ አንድ ጥቅስ አጣሁንኝ በበደል ተኝቼ ።
ውጤቴ ደካማ ትምህርት የማይሰርጸኝ ተማሪ ብሆንም ፤
ይችን ዓመት ተወኝ ደግሞ ትንሽ ልማር ታገሰኝ አሁንም ።

እባክህ አልቆረጥ በቅዱስ መሬትህ ልቆይ ፍቀድልኝ ፤
ያፈሩት ቅዱሳን የፍሬያቸው ሽታ መዓዛ እንዲደርሰኝ ።

የተሸከምከኝ ሆይ ዛሬም ተሸከመኝ አትሰልቸኝ አደራ ፤
ማን ይታገሰኛል ጠላት እየሆንኩት እይሰሩ ስሰራ ።

አታውጣኝ ከቤትህ ብዙ ቦታ አልይዝም ፍሬ ስለሌለኝ
ስፍራ የማያሻኝ ቤት የማላጣብብ ፍሬ አልባ በለስ ነኝ ።

ቦታ የሚይዙት ባለምግባሮቹ ቅዱሳንህ ናቸው ፤
ልክ እንደ ዘንባባ የተንዠረገገ ተጋድሎ ጽድቃቸው ።
ከሊባኖስ ዝግባ እጅጉን የበዛ ገድል ትሩፋታቸው ፤

እኔ አይደለሁም ቦታስ የምትይዘው የአንተው እናት ናት ፤
ስሮቿ በምድር ጫፎቿ በሰማይ ሲደርሱ ያየናት ፤
ይህቺን ዓመት ተወኝ ከስሯ እሆናለሁ ባፈራ ምናልባት ፤

ይቺን ዓመት ተወኝ እባክህ አምላኬ አንድ ዓመት ምንህ ናት ፤
ሺህ ዓመት አንድ ቀን አይደለም ወይ ለአንተ ዓመት ኢምንትህ ናት ።

ይኸ ዓመት አልፎ ደግሞ ዓመት ስጠኝ እስከምልህ ድረስ ፤
እባክህ ጌታየ ይችን ዓመት ተወኝ የወጉን እንዳደርስ ።

💥  💥  💥  💥  💥  💥  💥
✍️ ዲያቆን ሔኖክ ኃይሌ
💥  💥  💥  💥  💥  💥  💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
ዕለተ ምጽአት

አቤቱ የሚያረጅ የሚጠፋ ይህ የተስፋ ዓለም ለእኛ ለክርስቲያን ወገኖችህ አይደለም የሚመጣውን ተስፋ እናደርጋለን ድጅም እንጸናለን እንጂ። አንተ ሰማይና ምድር ያልፋል ቃሌ ግን አያልፍም ብለሃልና።

በእለተ ምጽዓት አምላክ ሲመጣ ሦስት ጊዜ ታላቅ የሆነ የመለከት መነፋት ይሆናል። ይህ የመለከት ድምጽም ሙታንን ሁሉ የሚያነቃ ነው።

በመጀመሪያው አዋጅ መለከት ሲነፋ በዓለም ዳርቻ ሁሉ የተበተነ የሥጋ ትቢያ ይሰበሰባል። በላይ ያለውና በታች ያለው በባሕር ያለውና በየብስ ያለው በአራዊትም ሆድ ያለው በልዩ ልዩ ሞት ፈጽሞ ያረጀና የጠፋ በምድር ላይ የወደቀ የሥጋ ቅርፍትም ሁሉ ወደ ቀደመ መገናኛው ይሰበሰባል።

በሁለተኛው አዋጅ መለከት ሲነፋ አጥንቶች ከሥጋና ከደም ጋር ይያያዛሉ ያለመንቀሳቀስ ያለመናወጥም እስከ ጊዜው ድረስ ፍጹም በድን ይሆናል።

በሦስተኛው አዋጅ መለከት ሲነፋ ሙታን እንደ ዓይን ጥቅሻ ፈጥነው ይነሳሉ ጻጽቃንና ኃጥአን ክፉም ቢሆን በጎም በጎም ቢሆን በሕይወታቸው ዘመን ሁሉ የሠሩትን ከምድር የተከተላቸውን ሥራቸውን ተሸክመው ይነሣሉ ጻድቃንን በቀኝ ኃጥአንንም በግራህ ታቆማለህ። ለመረጥካቸውም በምሥጋና ቃል ትናገራቸዋለህ እንዲህ ብለህ፥-

እናንተ የአባቴ ብሩካን ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥተ ሰማያት ትወርሱ ዘንድ ወደ እኔ ኑ ብራብ አብልታችሁኛልና፣ ብጠማ አጠጥታችሁኛልና፣ እንግዳ ብሆን አሳድራችሁኛልና፣ ብታረዝ አልብሳችሁኛልና፣ ብታመም ጎብኝታችሁኛልና፣ ብታሠር መጥታችሁ ጠይቃችሁኛልና በማለት (ማቴ ፳፭፥፴፬-፴፮)

እንደተነገረ ሁሉ ዳግመኛም ወደ ግራው ተመልሰህ በወቀሳ ቃል እንዲህ ትላቸዋለህ ብራብ አላበላችሁኝምና፣ ብጠማ አላጠጣችሁኝምና፣ እንግዳ ብሆን አላሳደራችሁኝምና፣ ብራቆት አላለበሳችሁኝምና፣ ብታመም አልጎበኛችሁኝምና፣ ብታሠር አልጠየቃችሁኝምና በማለት (ማቴ፳፭፥፵፫)

ያን ጊዜ ዓመጽና ሽንገላን ይናገር የነበረ አፍና አንደበት ሁሉ ይሸጋል። ያንጊዜ ኃዘን ይደረጋል፡ የማይጠቅም ኃዘን ነው።  ያንጊዜ ጩኸት ይደረጋል የማይጠቅም ጩኸት ነው። ያንጊዜ ፍጅት ይሆናል የማይጠቅም ፍጅት ነው። ያንጊዜ ለቅሶ ይሆናል የማይጠቅም ለቅሶ ነው።

የሚያስደነግጥ የነጐድጓድ ቃል የሚቆርጥና የሚከፍል የሚለይ ብርቱ ብልጭልጭታም ወደነርሱ ይላካል ይኸውም የኃጥአን ዕድላቸው ነው።

ያን ጊዜም ምድር አደራዋን ትመልሳለች እናትም የሴት ልጅዋን ጩኸት አትሰማም። ያን ጊዜ በሕይወትዋ ዘመን የሰራችው የነፍስ ሥራዋ ይገለጻል።

ልዑል እግዚአብሔር ሆይ ያን ጊዜ ትምረን ዘንድ ይቅርም ትለን ዘንድ በበላነው በቅዱስ ሥጋ በጠጣነው በክቡር ደምክ እንማጸንሃለን። ስለ እናት ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ብለህ ስለ ሁሉ ቅዱሳን መላእክት ጻድቃን ሰማህታት ነብያት ሐዋርያት እንዲሁም ደናግላን መነኮሳት እንማጸንሃለን። አምላክ ሆይ ያን ጊዜ ማረን እራራልንም ይቅርም በለን።
    
አሜን

💥  💥  💥  💥  💥  💥  💥
✍️ ቅዳሴ ያዕቆብ ዘስሩግ
💥  💥  💥  💥  💥  💥  💥

🔸 @Behila_Abew 🔸
🔸 @Behila_Abew 🔸
2024/05/04 11:28:40
Back to Top
HTML Embed Code: