Telegram Web Link
የናዝሬቱ ኢየሱስ

“በአባቱም በሄሮድስ ፈንታ አርኬላዎስ በይሁዳ እንደ ነገሠ በሰማ ጊዜ፥ ወደዚያ መሄድን ፈራ፤ በሕልምም ተረድቶ ወደ ገሊላ አገር ሄደ፤ በነቢያት፡- ናዝራዊ ይባላል የተባለው ይፈጸም ዘንድ፥ ናዝሬት ወደምትባል ከተማ መጥቶ ኖረ።” (ማቴ. 2 ፡ 22-23 ።)

ሄሮድስ የሚለው ስም ኋላ ላይ ስመ መንግሥት ሆኗል ። በአገራችን ዐፄ እንደሚባለው ሄሮድስም ስመ መንግሥት በመሆን አገልግሏል ። ሄሮድስ በሚለው ስም ብዙዎች ተጠርተዋል ። ዋነኛው ግን ታላቁ ሄሮድስ ተብሎ የሚጠራው ከክርስቶስ ልደት በፊት ከ37 ዓመት ጀምሮ እስከ 4 ዓ.ም. ድረስ ሥልጣን ላይ የነበረው ፖለቲከኛ ሰው ነው ። ይህ ሰው ሮማውያን የአባቱን የአንቲጳስን ውለታ አስበው ከፍ ያደረጉት ሲሆን በይሁዳ የነበረውን ሥልጣን በተቃዋሚዎች አጥቶ ወደ ሮም በሄደ ጊዜ ንጉሥ አድርገው ለአጥቢያው ሾሙት ። ሄሮድስም አስመሳይ ነበርና ከሮማ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት እስከ ቤተ ጣዖት ድረስ መሥዋዕትን በመሠዋት ታማኝ መሆኑን ገለጠ ። በሮማውያን ወታደራዊ ኃይል ታግዞ ዳግም የእስራኤልን ምድር ተቆጣጠረ ። ታላቁ ሄሮድስ በዓለም ላይ በተለያዩ ሥራዎቹ ይታወቃል ። ለሮም ንጉሥ መቀመጫነትና ለክብሩ በመሠረታት ቂሣርያ ይታወቃል ። ደግሞም ሁለተኛውን መቅደስ በማደስም የታወቀ ነው ። ይህ የመቅደስ እድሳትና መስፋፋት በ19 ዓመት ቅድመ ልደተ ክርስቶስ የጀመረ ሲሆን የተጠናቀቀው በ64 ዓ.ም ነው ። በሚያሳዝን መልኩ 6 ዓመት አገልግሎት ሰጥቶ በ70 ዓ.ም. በሮማውያን ፈረሰ ። ሄሮድስ ፖለቲከኛ ስለነበር የሥልጣኑ ምንጭና ደጋፊ የነበሩትን ሮማውያንን እንዲሁም የሚገዛቸውን አይሁድን በእኩልነት ደስ ለማሰኘት ይሞክር ነበር ። ለሥልጣኑ በጣም የሚሳሳ በመሆኑ ሚስቱንና ሦስት ወንዶች ልጆቹን ፈጅቷል ።

ሄሮድስ ጌታችንን ለመግደል በመነሣቱ ይታወቃል ። ብዙ የቤተ ልሔም ሕፃናትንም አስጨፍጭፏል ። ጌታ ወደ ግብጽ ከተሰደደ በኋላ ሄሮድስ የቆየው ለ3 ዓመታት ያህል ነው ። ሲሞት መንግሥቱ ለሦስት ልጆቹ ተከፋፈለ ። ይሁዳን ወይም ዋናውን ደቡባዊ ግዛት አርኬላዎስ ሲገዛ ፣ በሰሜን ያሉትን ሁለት ግዛቶች ሄሮድስ ፊልጶስና ሄሮድስ አንቲጳስ ገዝተዋል ። እነዚህ ሦስት የሄሮድስ ልጆች ንግሥናን ፈልገው ወደ ሮም ቢሄዱም አስተዳዳሪነቱ ጸናላቸው እንጂ ንጉሥነቱን አላገኙም ነበር ። የአርኬላዎስ ከኢየሩሳሌም መሄድን ታሳቢ አድርገው አይሁድና ሳምራውያን ወኪል በመላክ አርኬላዎስ እንዲነሣ ጥያቄ አቀረቡ ። በተነሣውም ዓመፅ ለመቀጣጫ እንዲሆን ሁለት ሺህ ሰዎች በስቅላት ተቀጡ ። በአርኬላዎስ ላይ የነበረው ጥላቻ እያየለ መጥቶ ሮማዊ ወኪል በእርሱ ፈንታ ተሾመ ። አርኬላዎስም በ6 ዓ.ም. ሥልጣኑን አጣ ።

ታላቁን ሄሮድስ በመሸሽ ግብጽ የነበሩት ሕፃኑ ኢየሱስ ፣ እናቱ ማርያምና አረጋዊው ዮሴፍ ሞቱ እንደ ተሰማ ተመለሱ ። አባቱን በግብር ይመስል የነበረው የይሁዳው ገዥ አርኬላዎስ ስለነበረ ወደ ናዝሬት መሄድን መረጡ ። ምክንያቱን የአባቱን ሥራ እያስፈጸመ ፣ በሺህ የሚቆጠሩ የይሁዳ ነዋሪዎችን እየገደለ ነበርና ። የጌታን መመለስ ቢሰማ አባቱ ያልቻለውን ነገር ለመፈጸም ይነሣ ነበር ። ስለዚህ አርኬላዎስን ላለማነሣሣት ወደ ናዝሬት ሄዱ ። ቍጠኞችን ማነሣሣት ተጨማሪ እሳት በምድር ላይ መለኮስ ነው ። በዚህም የኃጢአት ብዛት መጨመርና የኃጢአት ሎሌ መሆን ይመጣል ። አርኬላዎስ ጌታን መግደል አይችልም ፣ እርሱን አገኘሁ ብሎ ግን ብዙዎችን ይገድላል ። በዚህም ለብዙዎች ማለቅ ምክንያት ላለመሆን ወደ ናዝሬት ሄዱ ። ጌታን አገኝ ብሎ ታላቁ ሄሮድስ የቤተ ልሔም ሕፃናትን ገደለ ፣ ዛሬም ኢየሱስን የምትጠላ ዓለም እርሱን ያገኘች እየመሰላት ተከታዮቹን ትገድላለች ።

ጌታችን ወደ ናዝሬት መሄዱ ትንቢትን ለመፈጸም ነው ። ትንቢት ከእርሱ የመጣ መገለጥ ሲሆን ፍጻሜና እውነት የሚያገኘው በራሱ በክርስቶስ ነው ። የነቢያት ዓይናቸው ፣ እውነተኛ ለመባልም ማኅተማቸው ምጽአተ ክርስቶስ ነው ። ናዝሬት በሰሜናዊው ገሊላ የምትገኝ በኮረብታ ላይ የተመሠረተች ፣ ታሪክ የሚታይባት ማማ ነበረች ። ጌታችን ለልደቱ ናዝሬትን አልመረጠም ። ያለ አባት በምድር ተወልዷልና የናዝሬት ነዋሪዎች ግራ ስለተጋቡ ከትችታቸው ዘወር ማለት ይገባል ። ጊዜ የማይሽረው ሐሜት የለምና ሰዎች በከንቱ ስማችንን ሲያጠፉ ባለመስማት ዘወር እንበል ። በእውነቱ በጌታ እንደ ታየው ከአምስት ዓመት በኋላ ማንም አያስታውሰንም ። ጉድ አንድ ሰሞን ነው ይባላል ። ጌታችን የናዝሬቱ ኢየሱስ ይባላል ። በብሉይ ኪዳን ራሳቸውን ለእግዚአብሔር የለዩ ናዝራውያን የሚባሉ አሉ ። ጌታችን ግን በናዝሬት በማደጉ ናዝራዊ ተባለ ። ናዝሬትን ለምን መረጠ (

ናዝሬት የንቁዎች ፣ የአትንኩኝ ባይ ኃይለኞች ከተማ ናት ። ሁሉም የዓለም ማኅበረሰብ የሚኖርባት ፣ ለሥልጣኔ ቅርብ የሆነ ሕዝብ ያለባት ከተማ ናት ። ናዝሬት ላይ መቆም ከመላው ዓለም ጋር መገናኘት ነው ። ናዝሬት ወደ ይሁዳ ወይም ወደ ደቡብ የሚወስደው መንገድ አውራ ጎዳናው ተዘርግቶባት ሰሜንና ደቡብ እስራኤልን ታገናኛለች ። ከግብጽ ወደ ደማስቆ የሚያልፉ ቃፊሮች ናዝሬት መሸጋገሪያቸው ነበረች ። ከምዕራብ ወደ ምሥራቅ የሮማ ወታደሮች የሚያልፉት በዚህች ከተማ ነው ። በመገናኛዋ ናዝሬት ሰማይና ምድርን ያስታረቀው ኢየሱስ አደገ ። ሰው ሠራሽ የሆነውን ትብታብ የማይወደው ፣ አስጨንቆ ሳይሆን አስደስቶ የሚገዛው ኢየሱስ ለውጥን በሚወዱ መካከል አደገ ። ዓለምን ያለ መዶሻ ያነጠው የአብ ልጅ የማርያም ልጅ ተብሎ በሥጋ በመጣ ጊዜ በናዝሬት መዶሻ የያዘ አናጢ ሁኖ አገለገለ ። ናዝሬት በአክራሪ አይሁዶች የተናቁ ፣ ደግ አይወጣባቸውም ተብለው ተስፋ የተቆረጠባቸው ሰዎች መኖሪያ ናት ። በናዝሬት የመልካሞች መልካም ኢየሱስ ክርስቶስ አደገ ። የናዝሬቱ ኢየሱስ ሲባል የዓለም ጌታ ነው ፣ የሕዝቦች ቋንቋ ነው ማለት ነው ። በናዝሬት ብዙ ቋንቋ ይነገራልና ። የናዝሬቱ ኢየሱስ ሲባል የኃጢአተኞች ወዳጅ ማለት ነው ። ሰዎች ለንቀት የሰየሙትን ስያሜ እርሱ የእውነት አደረገው ። ስድብን ወስደነው ስንጠቀምበት ተሳዳቢው መሣሪያዬ አልሠራም ብሎ ይተወዋል ።

ናዝሬት ዓለምን የምታገናኝ አውራ ጎዳና ናት ፣ ወደ አባቱ ለመድረስ ጎዳና ፣ ወደ ወለደው ለመግባት በሩ የሆነው ኢየሱስ በናዝሬት አደገ ። ልበ ሰፊው በልበ ሰፊዎች ከተማ አደገ ። ተቆርቋሪው አትንኩኝ በሚሉ ፣ ሊቀርቧቸው በማያስቸግሩ ቀናዎች መካከል አደገ ። ናዝሬት በሰዎች የተጠላች በጌታ የተወደደች ናት ፣ ኢየሱስም አናጢዎች የናቁት አባቱ የወደደው የማዕዘን ራስ ደንጊያ ነው ።

ክብር ምስጋና ለናዝሬቱ ኢየሱስ ይሁን ! አሜን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 13 ቀን 2018 ዓ.ም.
41🥰3
ሰባቱ የፈሪሳውያን ዓይነቶች

ፈሪሳውያን የስማቸው ትርጉም እንደሚያስረዳን ለእግዚአብሔር የተለዩ ማለት ነው ። ፓራሽ ከሚለው የዕብራይስጥ ቃል የተገኘ ይመስላል ። ትርጉሙ መራቅ መለየት ሲሆን ፈሪሳዊ ማለትም የተለዩ ማለት ነው ። ራሳቸውን ከመላው ዓለም ብቻ ሳይሆን ከአይሁዳውያንና ከተራው ሕዝብ የተለዩ እንደሆኑ ይቆጥሩ ነበር ። እነዚህ ፈሪሳውያን በቃል ኪዳን ወደዚህ ሕይወት ይገባሉ ። ቃል ኪዳናቸውም ሕጉንና ትርጓሜውን በዘመናቸው ሁሉ ለማጥናትና ለመጠበቅ ሲሆን እርስ በርሳቸውም እንደ ወንድማማች ለመተያየት በሦስት ሰው ፊት ቃል በመግባት ይጀምሩ ነበር ። ፈሪሳውያን አነሣሣቸው ከክርስቶስ ልደት 200 ዓመት ቀደም ብሎ ነው ። ግሪካዊው የመንግሥት ሥልጣን ቦታውን በለቀቀ ጊዜ የግሪክ ቋንቋና ሔለናዊ የተሰኘው የዘመናዊነት ባሕል መላውን ዓለም መግዛት ቀጥሎ ነበር ። አጭር የነበረው የታላቁ እስክንድር ዓለምን የመግዛት ራእይ የቀጠለው በግሪክ ቋንቋና ፍልስፍና ነው ። ፈሪሳውያን አዲሱ ትውልድ በባዕድ ጠባይ እንዳይወረር ማንነታቸው እንዳይጠፋ በጣም ይጨነቁ የነበሩ ስብስቦች አገርን ለመታደግ የጀመሩት እንቅስቃሴ ነው ። እነዚህ ፈሪሳውያን ከሥልጣን የራቁ ሲሆኑ ቤተ መቅደሱ አካባቢ ላሉት ካህናት ጥሩ አመለካከት የላቸውም ። እኛ እናጠብቃለን ብለው ስለሚያስቡ ሌላውን ሁሉ እንደ ሕግ አፍራሽና ግዴለሽ ያዩት ነበር ። ፈሪሳውያን አገራዊ ስሜት ከእኛ ውጭ ለሐሳር ብለው የሚያስቡ ፣ ከእኛ በላይ ፉጨት አፍ ማሞጥሞጥ የሚሉ ነበሩ ። ጌታችን በምድር ላይ በነበረ ጊዜ ቍጥራቸው ከስድስት ሺህ የማይበልጥ ቢሆንም በጣም ተጽእኖ ፈጣሪዎች ነበሩ ። የጌታችንን ስብከት በማወክ ፣ በመጨረሻ ለሞት አሳልፎ በመስጠት እጃቸው ረጅም ነበር ።

እነዚህ ፈሪሳውያን ሰባት ቡድኖች ወይም ዓይነት ነበራቸው ። ፈሪሳዊነት ጠባይ በመሆኑ በሁሉም ዘመን ያለ ነው ። በአዲስ ኪዳን ከዘጠና ስምንት ጊዜ በላይ በግልና በቡድን የተጠቀሱ ናቸውና ለእኛ ትምህርት ባይሆኑ ይህን ያህል ሽፋን አያገኙም ነበር ። ሰባቱ የፈሪሳውያን ዓይነቶች፡-

1- የታይታ ፈሪሳውያን

እነዚህ “የትከሻ ፈሪሳውያን” በመባልም ይታወቃሉ ፣ ሕጉ የተጻፈባቸውን ጥቅልሎች በእጃቸውና በግንባራቸው ላይ በማሰር ይታወቃሉ ። ሕጉ የተሰጠበት ዓላማ እንደ ጌጥ እንዲንጠለጠል ሳይሆን ለሕይወት ለውጥ ነው ። ፈሪሳውያን ግን ሕጉ ከልባችንና ከቤታችን ተርፎ በልብሳችን ላይ ተጽፏል የሚል መልእክት ለማስተላለፍ ይጥሩ ነበር ። እነዚህ ፈሪሳውያን ረጃጅም ቀሚሶችን በመልበስ ፣ ዘርፋቸውን በማስረዘም መንደር ለመንደር የሚዞሩ ፣ የምስኪኖችን መቀነት የሚያስፈቱ ነበሩ ። ጻድቅነታቸውን ሁሉ ሰው እንዲያውቅላቸው ይፈልጋሉ ። እዩልኝ ስሙልኝ ይላሉ ። በጎ ተግባርን የሚያደርጉት ለሰው እንጂ የተፈጠሩበት ዓላማ መሆኑን ተገንዝበው አይደለም ። ዛሬም በጥቅስ ቤታችንና መኪናችን ተንቆጥቁጧል ። አማኝ መሆናችንን ለማሳየት የመሐላ ብዛት እንደረድራለን ። አንዱ በኢየሱስ ስም ፣ በጌታ ይላል ፣ ሌላው መድዬን እመቤቴን ይላል ። የሰቀልነው ጥቅስ ግን በዕለታዊ ኑሮአችን ላይ ተጽእኖ አያሳድርም ። የኢየሩሳሌም ፣ የግሪክ እያልን እናጌጣለን ፣ በኃጢአት ግን ወይበናል ። “ጠጉራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል” እንዲሉ ከእኛ ይልቅ ልብሱ አማኝ ነው ። ጭንቀታችን ጌጠኛ መስቀል ወይም አይከን በሺህ ዶላር ለማንጠልጠል እንጂ የሕዝብን ስቃይ ለመካፈል ፣ የክርስቶስ የሕማሙ ወዳጅ ለመሆን አይደለም ። የምናገለግለው ሕዝብ በችግር ሰክሮ የምንሰብከውን እንኳ መስማት አልቻለም ። እኛ ግን በዘመናት ሁሉ እንደ ታየው ከሟች ጋር ሳይሆን ከገዳይ ጋር የምንሰለፍ ሆነናል ። የቀረው ልብሳችን እንጂ ጨካኝነት ሙሉ በሙሉ ወርሶናል ። ሕገ ፍቅር ሳይሆን ሕገ አራዊት ሰልጥኖብናል ። ያሸነፈ ብቻ የሚኖርበት ዓለም መሥርተናል ። ግፈኛን ተው ለማለት ግፍን ስላልተውን አፍ እያለን ዱዳዎች ሆነናል ። በዋና ከተማ ላይ እንተራመሳለን ፣ የተወለድንበት መንደር በሁከት ሲናወጥ የመጸለይና ተዉ የማለት የሞራል ልዕልና እንኳ አጥተናል ። “እውነት መናገር ካልቻልህ ዝም በል” ይባላል ። እኛ ግን በቍስል ላይ ጥዝጣዜ ለመሆን ከንቱ ንግግር መናገርን አላቆምንም ። “በየቀኑ በግ የሚያስበላ እረኛ ከተሸለመ ፣ ሸላሚው ቀበሮ ነው” ይባላል ። ይህ ሁሉ ሸብ ረብ ፣ ይህ ሁሉ ውድድር በግ የሚያስበሉትን ከፍ ለማድረግ ነው ።

ወጣቱ ከቀይ ሽብር አንሥቶ ሜዳ ላይ ሲወድቅ እንደሌለ ሁነን አልፈናል ። በየዘመናቱ የፈሰሰው የልጆቻችን ደም ዛሬ የሚበላ ምግብ ተገኝቶ አላስበላ ብሎናል ። በየጎጆው በረሀብ የሚሞቱት ሊቃውንት ረሀባቸው እየተፋረደን በሰላም ቤት ውስጥ ሰላም አጥተናል ። ዝናብ የሌላቸው ደመናዎች ሁነን መጡ መጡ ከመባል ውጭ ምንም ትርጉም የማንሰጥ መሆናችን ያሳዝናል ። ቤተ ክርስቲያን የነፍስ ደጃፍ መሆንዋን ባንገነዘብ እንኳ የእንጀራዬ ገበታ ነች ብለን ብናከብራት መልካም ነበር ። አንድ ወጣት ለዚህ ቁመና እስኪበቃ የሚከፈለው ዋጋ ቀላል አይደለም ። ከፅንስ ጀምሮ ፣ በምጥ እስከ መወለድ ፣ በጣር እስከ ማደግ ድረስ ዋጋ የተከፈለበት ወጣት ሲሞት እንዴት በክርስቶስ ፍቅር ያለን ሰዎች ያስችለናል ( ወጣቱ ለማየት ሲያሳሳ ጦርነት ይቆርጠዋል ። ወላድም ቀኑ ጨልሞበት እንዳዘነ ያልፋል ። የዚህ ሁሉ ችግራችን ለባለጠግነት እንጂ ለወንጌል አለመሮጣችን ነው ። ለታይታው ፣ ለእዩኝ ስሙልኝ እንጂ ለእውነት አለመኖራችን ነው ። በዚህ ዘመን ቁመናውን የሚሸጥ አገልጋይ እያመረትን ፣ እየቀደሰ ፎቶ አንሺ የሚቀጥር ቀዳሽ እያበዛን ነው ። ጸሎቱ ባያርግ የሚደንቅ አይደለም ። የተሻለ ካገኘ ለመሄድ በጨረታው የማይገደድ አገልጋይ ሰብስበናል ። የመከረንን ስም ሰጥተን ፣ አላዋቂውን አነሣሥተንበት እናጠፋዋለን ። ግን ወደ ሥራችን ፍጻሜ እየተጓዝን መሆኑን እንዘነጋለን ። ነብር እንኳ ሲሞት ቆዳውን ትቶ ይሞታል ፣ እኛ ለትውልድ ምን ትተን እንሄድ ይሆን ?

አቤቱ በቤትህ ውስጥ የጠፋነውን አግኘን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 14 ቀን 2018 ዓ.ም .
40😢4🥰1
ዛሬ ዓርብ ጥቅምት 14 ቀን 2018 ዓ.ም. ከምሽቱ 2:00 ሰዓት  ላይ ትምህርታችን ይጀምራል ::

የትምህርታችን ርእስ " ብሉይ ኪዳን"

ክፍል 4

የሚል ነው

ማስታወሻ ብትይዙ ይመከራል።

ሌሎች ወገኖቻችንንም ጋብዙ

https://www.tg-me.com/Nolawii
16
Live stream started
Live stream finished (1 hour)
Audio
ብሉይ ኪዳን 4

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
17👏1
ሰባቱ የፈሪሳውያን ዓይነቶች /2
አልምጥ ፈሪሳውያን

በሁለተኛ ምድብ የሚገኙት ፈሪሳውያን ከበጎ ነገር የዘገዩ ፣ ዳተኛ ምድብ ናቸው ። ለሌሎች መልካም ሥሩ ብለው ያስተምራሉ ፣ እነርሱ ግን አያደርጉትም ። በጎ ለማድረግ ያስባሉ ነገር ግን ዛሬ አይደለም ይላሉ ። አንድ በጎ ነገር በማድረግ ለነገ የሚቆይ ነገር ለመሥራት ምክንያት ይፈጥራሉ ። እነዚህ ፈሪውያን አድርጉ የማለት እምቅ ትምህርት አላቸው ፣ ትእዛዙ ግን እነርሱን የሚመለከታቸው አይደሉም ። ሐኪሙ ይህን አታድርጉ ብሎ ራሱ ግን ያደርገዋል ። እነዚህም ለሌሎች ጤና ቀና ምክር ይሰጣሉ ፣ ለራሳቸው በሽታ ግን መድኃኒት አይወስዱም ። ሰዎች ታማሚ እንደሆኑ ፈውስም እንደሚያስፈልጋቸው እርግጠኛ ናቸው ፣ የራሳቸውን በሽታ ስላላመኑ መድኃኒቱን አይፈልጉትም ። እነዚህ ፈሪሳውያን ጊዜው አሁን ነው የሚለውን የእግዚአብሔር መንግሥት መመሪያ አይከተሉም ፣ ነገ ይሆናል ብለው ይወረውሩታል ። ክፉ ከሚያደርጉት በላይ በጎ ባለማድረጋቸው እግዚአብሔርን ያሳዝናሉ ።

አይሁዳውያን እግዚአብሔር ሁለት ሚዛን እንዳለው ያስቡ ነበር ። የአይሁድ ጥፋትና የአሕዛብ ጥፋት አንድ ዓይነት ቢሆንም እግዚአብሔር እኩል አይቀጣንም ብለው ያስቡ ነበር ። ስህተታቸውን ቀላል ለማድረግ የሄዱበት ርቀት እግዚአብሔርን አባይ ሚዛን ያለው አስመስለው ሳሉት ። አይሁዳዊ መሆን በጎ ለማድረግ መመረጥ ነው የሚለውን አይሁዳዊ መሆን ክፉ ለማድረግ ፈቃድ ማግኘት ነው ብለው ተረጎሙት ። ነቢዩ ሳሙኤል፡- “ባሪያህ ይሰማልና ተናገር” አለ ። በዚህ ዘመን ያለን አማንያን “ባሪያህ ይናገራልና እግዚአብሔር ሆይ ስማ” የምንል ይመስላል ። አይሁዳውያን በስህተታቸው እንደሚቀጡ ብዙ ማሳያዎች አሉ ። ወንድማቸውን ዮሴፍን በመሸጣቸው ምክንያት በግብጽ ምድር ባሪያ ሆኑ ፣ የሐሰት ነቢያትን በመከተላቸው በባቢሎን ተጋዙ ። መሢሑን በመስቀላቸው በሮማውያን ተደመሰሱ ። እስካለፉት ሰባ ዓመታት ድረስ አገር አልባ ሆነው ለ1900 ዓመታት በዓለም ላይ ተበተኑ ። የፈለግነውን እየሠራን እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ጥሎ አይጥልም ማለት ግብዝነት እንጂ እምነት አይደለም ። በጎ እየሠራን ያንን ብንናገር ወይም ክፉ ነገር ሳይመጣብን ብንፎክር ያምር ነበር ። በዓለም የሌለ መከራና ጉድ ተሸክመን ከዚህ በላይ መጣልና መውደቅ አለ ወይ( በሚሊየን የሚቆጠር ወገን በጦርነት ሲያልቅ እነዚያ ኢትዮጵያውያን አይደሉም ወይ ( አጉል መመጻደቅ ንስሐ እንዳንገባና ለተጎዱት እንዳናዝን አድርጎናል ። ትንቢት የተነገረለትን ፣ ሱባዔ የተቆጠረለትን ፣ አንተ አትሠራውም ልጅህ ሰሎሞን ይሠራዋል የተባለውን መቅደስ ያፈረሰው ኃጢአት ነው ። እግዚአብሔር በዓላማው ጨካኝ ነው ፣ በፍርዱም አድልኦ የለውም ።

አንዳንድ ሰዎች የብሉይ ኪዳኑ እግዚአብሔርና የአዲስ ኪዳኑ እግዚአብሔር ልዩ እንደሆነ ያስተምራሉ ። የብሉይ ኪዳኑ ጨካኝ ፣ የአዲስ ኪዳኑ ሩኅሩኅ እንደሆነ ይገምታሉ ። እግዚአብሔር ግን ፍርዱ ምሕረቱን ሳያስቀርበት ፣ ምሕረቱም ፍትሑን ሳያጓድልበት ለዘላለም ይኖራል ። እግዚአብሔር በአንድ ጊዜ ፈራጅም መሐሪም ነው ። እናት ለልጅዋ መሐሪ ብትሆን ፍትሕን ረግጣ ነው ፣ መንግሥት ፍትሐዊ ቢሆን ፍቅር የሚባልን ነገር ላለማወቅ ወስኖ ነው ። እግዚአብሔር ግን የፍቅርም የፍትሕም አምላክ ነው ። ሁላችንም ብንሆን ደግ ሲጠቃ ክፉ ሲያጠቃ ማየት አንችልም ። ይህ ማለት እግዚአብሔር እንዲፈርድ እንከጅላለን ማለት ነው ። በሌሎች ስህተት ላይ የሚፈርደው በእኛም ስህተት ላይ እንዲፈርድ መፍቀድ አለብን ። የተቀበልሁት የሚገባኝን ነው ማለት ታላቅ ብፅዕና ነው ። በአዲስ ኪዳን የተገኘው ነጻነት እንደ ፈለግን የመኖር ሳይሆን እንደ ተፈቀደልን የመገኘት ነው ። ነጻነት ከባርነት በላይ ኃላፊነትን የሚጠይቅ ነው ። ነጻነትን ማስተዳደር አለመቻል ከባድ ነገር ነው ።
በዚህ ዘመን ያለን ሰባክያን ምናልባት አልምጥ ክርስቲያን ሆነን ይሆናል ። ቤተ ክርስቲያንን እነ እገሌ ጎዷት ብለን እንቆረቆራለን ፣ እኛ ስንጎዳት ግን አይሰማንም ። የአንዳንዶችን ነቁጥ ስህተት እናጎላለን ፣ የሌሎችን ተራራ የሚያህል ስህተት ደግሞ በአገር ልጅ ስሜት እናልፈዋለን ። እገሌ የተናገረውን ስህተት ስህተት ስንለው ፣ ወዳጅ ከሆነ ደግሞ የአንደበት ማዳለጥ ፣ ከፍቅር የተነሣ የተነገረ ነው ብለን እናልፈዋለን ። ቤተ ክርስቲያንን ዘረኝነት የሚወዘውዛትን ያህል ቤተ መንግሥትን አይወዘውዘውም ። የፖለቲከኞች ዘረኝነት ጠቅለል አድርጎ አራት ክፍለ አገርን ላንዱ ፣ አምስት ክፍለ አገርን ለሌላው ሰጥቶ ነው ። በእኛ ያለው እስከ ቤት ቍጥር ወርዶ እስከ ጎጥ ዘቅጦ ይታያል ። ፈሪሳዊነት አስመሳይነት ነው ።

ጌታችን ወደ ዓለም የላከው ሕይወታችን እንዲመሰክር እንጂ ቃላችን ብቻ እንዲመሰክር አይደለም ። አንድ ሰው፡- “የምትናገረውን የምትኖረው እያፈረሰብኝ ነውና ልሰማህ አልቻልኩም” እንዳለው እኛም ሆነናል ። በጎ ሥራ ምግባርን ሙሉ ያደርገዋል ። ባለ መስረቅ ብቻ ምግባር ሙሉ አይሆንም ፣ መስጠትም ያስፈልጋል ። ምግባር ሁለት እጆች አሉት፤ ክፉን ማቆምና በጎ መጀመር ናቸው ። የኃጢአት በጀታችን ለጽድቅ ካልዋለ ገና አላመንም ማለት ነው ። አለማመንዘር ብቻውን ብቂ አይደለም ፣ ለትዳር አጋር አሳቢ መሆንም ያስፈልጋል ። በጎ ሥራ ትላንት የሠራነውን ክፉ ነገር መካሻ ማጠቢያ ነው ። የበደሉትን መካስ ፣ የቀሙትን መመለስ እርሱ ንስሐ ይባላል ። በጎ ሥራ ዛሬን ኖርኩ የሚያሰኘን ነው ። ለነገው ትውልድ ቀሪ ሀብት ነው ። “የቄስ ልጅ እግዚአብሔር አጎቱ ይመስለዋል” እንዲሉ እኔን ምንም አይለኝም ብሎ ያውም በቤቱ በበደል መጽናት ተገቢ አይደለም ። ምክንያት አያድንም ። ወገን እያለቀ ምክንያት የሚደረድር ሹም ካለ ተባባሪ ነው ። ይህን ካላቆምሁ የእኔ መኖር ምን ጥቅም አለው ( የሚል ወኔያም ያስፈልጋል ። ዛሬ ማድረግ የሚገባንን ነገ ብናደርገው ከክፉ ሊቆጠር ይችላል ። ታሞ ያልረዳነውን የመቃብሩን ሐውልት ብንሠራለት ጥቅም የለውም ። ብዙዎች ስሞት አትቅበሩኝ ፣ ዛሬ አዳምጡኝ እያሉን ነው ። ፈሪሳዊነታችን ግን አልሰማቸውም ።

አንድ የበላይ ሰው አውቃለሁ ። ራበኝ የሚል ማመልከቻ ሲመጣላቸው በእሳቱ “ሰ” ሊጻፍ የሚገባውን በንጉሡ “ሠ” ጽፈሃልና አስተካክለህ አምጣ ይሉ ነበር ። ያ ረሀብ ዘመኑን እንዳያሳጥርበት የሚጨነቅ አገልጋይ “መቼ(” ሲል “ከዐሥር ቀን በኋላ ና” ይባላል ። ምክንያቱም ነገ የቦርድ ስብሰባ ፣ ተነገወዲያ የውጭ እንግዶች … እየተባለ ምክንያት ይሰጠዋል ። ረሀብተኛን ነገ ና ማለት አይቻልም ፣ ያለው ቀን ዛሬ ነውና ። ለፊደሉ ስንጨነቅ ለራበው ሰው ግን አንጨነቅም ። ጭካኔም ልክ አለው ።

አቤቱ ምን እየሆንን ነው ፣ እባክህ መልሰን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 15 ቀን 2018 ዓ.ም.
26🥰2
እግዚአብሔር ቢፈቅድ ብንኖር ነገ

እሑድ ጥቅምት 15 ቀን 2018 ዓ.ም. ከ ጠዋቱ 4፡00 ሰዓት  ላይ ትምህርታችን ይጀምራል ::

የትምህርታችን ርእስ " የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስደት

ክፍል 3


ልደቱና ስደቱ ይተነተናል

ማስታወሻ ብትይዙ ይመከራል።

ሌሎች ወገኖቻችንንም ጋብዙ

https://www.tg-me.com/Nolawii
20👍2
Live stream started
Live stream finished (1 hour)
Audio
የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስደት 3
የመጨረሻው ክፍል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
15
ሰባቱ የፈሪሳውያን ዓይነቶች /3

የማያዩ ፈሪሳውያን

እነዚህ የፈሪሳውያን ወገኖች ሴቶችን ላለማየት ፊታቸውን አዙረው ፣ አቀርቅረው ፣ ዓይናቸውን ጨፍነው ይሄዱ ነበር ። በመንገድ ላይ እኅታቸውንና እናታቸውን ቢያገኙ እንኳ ሰላምታ አይሰጡም ነበር ። ሴቶችን ላለማየት በሚያደርጉት ጥረት ከግንብ ጋር ይጋጫሉ ፣ ወደ ገደል ይገባሉ ። በዚህ ምክንያት የሚደርስባቸውን ጉዳትና ቍስል ለሃይማኖት እንደ ተከፈለ ዋጋ ይቆጥሩታል ፣ የቅድስናም አካል እንደ ሆነ ያስባሉ ። ራሳቸውንም እንደ ሰማዕት ይቆጥራሉ ። ሃይማኖት ሰምቶ ማመዛዘን እንጂ ከንቶውም አልሰማም የሚል አይደለም ። ሐዋርያው፡- “ሁሉን ፈትኑ መልካሙንም ያዙ ፤” የሚለው ምክሩ ዝነኛ ነው ። (1ተሰሎ. 5 ፡ 21) በተለያዩ ዩንቨርስቲዎች ላይ ይህ ጥቅስ መሪ ቃል ሆኖ ተለጥፏል ። ሁሉን መፈተን መልካሙን መያዝ ፣ ልበ ሰፊ መሆን የሚያዋጣውን ግን መለየት ይገባል ። ጌታችን ክፉ ከሚባሉት ሳይቀር መማር እንደምንችል ሲገልጥ “እንደ እባብ ብልህ ሁኑ” አለ ። እባብ እንደ ጠላት የሚታይ ነው ። ከጠላትም ትምህርት መውሰድ ይገባል ። ጠላቶቻችን ራሳቸውን የሚጠብቁ ፣ ጠንቃቃ የሆኑ ፣ ብዙ ለመኖር የሚያቅዱ ፣ ወጥመድ ውስጥ ልገባ እችላለሁ ብለው ከዝሙትና ከመጠጥ የሚርቁ ሊሆኑ ይችላሉ ። ይህንን ከእነርሱ መማር ብልህነት ነው ። ሃይማኖተኛነት ምንም ነገር አላይም ማለት አይደለም ፣ የማየውን ሁሉ ግን አልከተልም የሚል መርህ ያለው ነው ።

ዝሙት ያለው ከዓይናችን ይልቅ በልባችን ውስጥ ነው ። በርግጥ ዓይንና ጆሮ የልብ መስኮት ናቸውና መጠበቅ ይገባናል ። መስኮት መክፈቻ ብቻ ሳይሆን መዝጊያም አለው ። የመስኮት ዓላማ ደጁን ለመመልከት ፣ ብርሃንና ነፋስ ለማግኘት ፣ ከቤት የማይገባውን ሰው በሩቅ ለመሸኘት ፣ ሒሳብ ለመቀበል የሚያገለግል ነው ። መስኮት ግን ካልተዘጋ ለሌባ በሩ ነው ። ሌባ ስልጠናው በበር ከመግባት በመስኮት መግባት ነውና ። ለምናየው ለምንሰማው ጠንቃቃ መሆን ይገባናል ፣ ጨርሶ አላይም አልሰማም ማለት ግን አንችልም ። ጨርሶ ሴት ባለማየት ከዝሙት ለመራቅ የሚፈልጉ ሰዎች ይኖራሉ ። ሴቶች ግን እኅቶችም ፣ እናቶችም ከሁሉ በላይ የተፈጥሮ እኩዮቻችን ናቸው ። ከሴቶች ጋር አንድ አማኝም አገልጋይም ያላቸው ግንኙነት ሥርዓት ያለው ሊሆን ይገባዋል ። ሴቶችም ከወንዶች ጋር ያላቸው ግንኙነት ለውድቀት የማያደርስ መሆን አለበት ። አስቀድመው ካላጠሩት ድንበሩ ላይ ከደረሰ በኋላ መመለስ ይከብዳል ። አገልጋዮች ሁለት ሁነው አንዲት ሴትን ቢያገለግሉ መልካም ነው ፣ አሊያ ሁለት ሴቶችን አንድ አገልጋይ ማገልገል አለበት ፣ ስፍራውም ግልጥ መሆን ይገባዋል ። ይህ ሁሉ ዝሙት እስከ ዕድሜ ልክ ድረስ የሚጓዝ ቀውስን ሊያመጣ ስለሚችል ፣ ከሁሉ በላይ የአገልግሎት ጉዞን ስለሚያሰናክል ነው ። በወጣትነት የተዘራው በሽምግልና ይታጨዳልና ጠንቃቃ መሆን ይገባል ።

ጥንቃቄአችን ጥላቻን እንዳይፈጥር መጠንቀቅ ይገባል ። እጅግ ጥንቃቄ ከስህተት ይዳርጋል ። ቅድስና በእኛ ፈቃደኝነት መንፈስ ቅዱስ በውስጣችን የሚሠራው የለውጥ ሂደት ነው ። ቅድስና በጉልበት አይደለም ፣ በስጦታው መንገድም መጓዝ ያስፈልጋል ። መሳሳቦችን ማርገብ ይገባናል ። አንድ ወንድ ወንጀል ፈጸመ ማለት መላው ወንድ ክፉ ነው ማለት ላይሆን ይችላል ። የወንዶች ማኅበር ፣ የሴቶች ጽንፍ አስፈላጊ አይደለም ። ይህን ዓለም ቀና ለማድረግ የሁለቱም አስተዋጽኦ ያስፈልጋል ። ጥንቃቄአችን ጥላቻ እንዳይሆን አሁንም ደግመን ማሰብ ይገባናል ። ፈሪሳውያን እንዲህ ሰንጥረው የሚያዩ ፣ በአጉሊ መነጽር እያዩ ለመታዘዝ የሚፈልጉ ናቸው ። ውስጣቸው ግን ቅሚያና ግድያ ሞልቶበታል ።

በዚህ ዘመንም አሸንክታብ ባይኖረንም ፣ የፈሪሳውያንን ቀሚስ ባንለብስም ዘመናዊ ፈሪሳዊ ልንሆን እንችላለን ። ፈሪሳውያን እስራኤልን ይወዳሉ ፣ እስራኤላውያንን ግን ይንቃሉ ። ፈሪሳዊነት ዕውር ስለሚያደርግ ኢትዮጵያን እወዳለሁ እያሰኘ ኢትዮጵያውያንን ግን ሊያስጠላና ሊያስንቅ ይችላል ። ስለ ቅድስና ሲያወሩ ነቁጥ ስህተት የሌለባቸው የሚመስሉ ፣ በቅድስና ችግር እገሌን ገፋሁ ፣ አወገዝሁ የሚሉ ራሳቸው እጅግ የረከሱ ናቸው ። መግለጥና ማጋለጥን ለይተው የማያውቁ ፣ ለቅድስና በመቆርቆር ስሜት በሐሜት ሰውን ሲበክሉ የሚውሉ አያሌ ፈሪሳውያን አሉ ። አንዱ ቅድስና አትፍረድ የሚለው ትእዛዝ ነው ። እገሌ ደከመ ሲባል እኔም የማውቀው አለ ብለው ቶሎ ብለው አደባባዩን የሚይዙ ሰዎች በብዙ ጭቃ ውስጥ እንደ ቦኩ ሕሊናቸው ያውቀዋል ። በሰው ስህተት የራስን ቅድስና መሥራት አይቻልም ። ምሕረት የለሾች ስለ ኢየሱስ ተቆርቋሪ ነን ብለው ሲናገሩ እንሰማለን ። ወንጌል ያለወጣቸው ጨካኞች ለወንጌል ተገፋሁ ብለው ሲያነቡ ፣ ተውኔት ሲሠሩ እንመለከታለን ። መቼም ባለጌና ጨዋ ቢጣላ የሚያሸንፈው ባለጌ ነው ይባላል ። ምክንያቱም ባለጌ የሚገድበው ምንም የሞራል አጥር የለምና እንደ ፈለገው ያወራል ፣ ጨዋው ግን ለራሱ ክብር ስላለው ዝም ይላል ። በዚህ የተነሣ ጨዋውን ሁሉም ይኰንነዋል ።

ፈሪሳዊነት አቀርቃሪነት ነው ። አንገት ደፊ አገር አጥፊ እንደሚባለው እጅግ ዘማዊ የሆኑ ሰዎች ከቀልቃሎች ይልቅ ስልክልኮቹ ናቸው ። በአደባባይ ሴት ሰላም ማለት የሚሰቀቁ ፣ የብዙዎችን ዕድል የሰበሩ ፈሪሳውያን ዛሬም አሉ ። ስለ ፍቅር የሚያስተምሩ ፣ በመንገዴ ቆሟል የሚሉትን ሰው ግን የሚያስወግሩ እየበዙ ነው ። ከዚያን ጊዜው ይልቅ ቤቱ የወንበዴዎች ዋሻ የሆነው አሁን ነው ። ወንበዴ ሌባ ብቻ አይደለም ፣ ገዳይም ነው ። ነፍስን ሰርቆ ኪስን የሚፈትሽ ነው ። ዛሬም ቀማኛነትና ገዳይነት እያበዛን ነው ። አንድ ጊዜ መግደል ሞኝነት ነው ብለን መጀመሪያ በሥነ ልቡና ፣ ቀጥሎ በመንፈሱ እንዲሞት እንታገላለን ። እኛው ገድለን ጥሩ የቀብር ሥነ ሥርዓትን እናዘጋጃለን ። ለሰው የተሰወረው ሳይገልጥ ለሚያየው ጌታ የተብራራ ነው ። ፍርድም በደጅ ነው ።

ጌታ ሆይ ከውጫዊ ይልቅ ውስጣዊ ጭምትነትን አድለን !

ዲያቆን አሸናፊ መኮንን
ጥቅምት 17 ቀን 2018 ዓ.ም.
19
2025/10/28 02:28:22
Back to Top
HTML Embed Code: