Telegram Web Link
ከመዋል የሚቀር አይኖርምና ንጉሣችንና አባታችን ቅዱስ ይምርሐነ #ክርስቶስም የእረፍት ዘመኑ ሲደርስ #እግዚአብሔር_አምላክ ቃል ኪዳኑን ለዘላለም እንደሚያፀናለት ነግሮት በዚህች በተባረከች #በጥቅምት_19 ቀን በክብር አሳረፈው።

መቃብሩንም አስቀድሞ እነደነገረው በዛው በተቀደሰ ዋሻ ውስጥ አደረገለት። እናም ዛሬ ድረስ ቦታው በክብር ተጠብቆ ይኖራል። ምእመናንም ቃል ኪዳኑን በማሰብ "ማረኝ ይምርሐ" እያሉ መቃብሩን ይዞራሉ። ያንን ከሰማይ የወረደለትን #መስቀልም በቤተመቅደሱ የሚያገለግሉት ካህናት አባቶች ቦታውን ለመሳለም የሚመጣውን ሕዝበ ክርስቲያን በበዓል ቀን ይባርኩበታል፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አባት ይምርሐነ #ክርስቶስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_በርቶሎሜዎስና_ሚስቱ

ዳግመኛም በዚህች ቀን በከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን ቅዱስ በርቶሎሜዎስና ሚስቱ በሰማዕትነት አረፉ።

እሊህ ቅዱሳንም የግብጽ ምዕራብ ከሆነ ፍዩም ከሚባል አገር ናቸው ክርስቲያኖችም እንደሆኑ በመኰንኑ ዘንድ ወነጀሏቸው መኰንኑም ልኮ አስቀረባቸውና ስለ ሃይማኖት ጠየቃቸው እነርሱም ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በፊቱ ታመኑ።

መኰንኑም ጥልቅ ጒድጓድ እንዲቆፍሩላቸው በዚያም እንዲጨምሩአቸውና በሕይወታቸው እንዲደፍኑባቸው አዘዘ። መኰንኑም እንዳዘዘ አደረጉባቸው በዚህም ምስክርነታቸውን ፈጽመው የሰማዕትነት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#የጳውሎስ_ሳምሳጢን_ውግዘት

በዚችም ቀን ስለ ጳውሎስ ሳምሳጢ በአንጾኪያ አገር የቤተ ክርስቲያን የአንድነት ስብሰባ ተደረገ። ይህ ጳውሎስም ከአንጾኪያ አገሮች በአንዲቱ አገር ኤጲስቆጶስነት በተሾመ ጊዜ ክፉ ዘርን ሰይጣን በልቡ ውስጥ ዘራበት #ሎቱ_ስብሐት አካላዊ ቃልን አካል እንደሌለ የ #ክርስቶስም ጥንት መገኛው #ሎቱ_ስብሐት#ማርያም እንደሆነ እርሱም አለምን ያድንበት ዘንድ #ሎቱ_ስብሐት #እግዚአብሔር የፈጠረው እንደሆነ #ሎቱ_ስብሐት ከመለኮትም ጋር ያልተዋሐደ በላዩ ወርዶ በ #እግዚአብሔር ፈቃድ አደረበት እንጂ ብሎ የሚያምን ሆነ በ #ወልድም ቢሆን በ #መንፈስ_ቅዱስም ቢሆን የሚያምን አልሆነም።

ስለዚህም ኤጲስቆጶሳት በአንድነት ተሰበሰቡ የእስክንድርያው አባ ዲዮናስ የሮሜ አባ ዲዮናስዮስ እሊህ ሊቃነ ጳጳሳት ስለ እርጅናቸው ከዚያ ደርሰው ከእርሳቸው ጋር ሊሰበሰቡ አልቻሉም ነገር ግን መልእክትን ጻፉ።

የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዲዮናስም እንዲህ የሚል መልእክትን ጻፈ። የ #እግዚአብሔር ልጁም ቃሉም የሆነ #ክርስቶስ#መለኮቱም ከእርሱ ጋር ትክክል የሆነ እርሱም ከሦስቱ አካላት አንዱ #ወልድ ስለእኛ ከ #እመቤታችን ከቅድስት ድንግል #ማርያም ያለ ዘር ስጋንና ነፍስን ነሥቶ ፍጹም ሰው የሆነ በመለኮቱ ከ #አብ#መንፈስ_ቅዱስ ጋር ትክክል ሲሆን እንደእኛ ፊጹም ሰው ሁኗል ከተዋሕዶውም በኋላ ያለ መለያየትና ያለ መቀላቀል ሁለቱ ባሕርያት አንድ ሁነዋል ከብሉይና ከሐዲስ መጻሕፍት ምስክሮችን ጠቅሶ እያስረዳ ጽፎ ይቺንም መልእክት ከሁለት ምሁራን ቀሳውስት ጋር ላካት።

በዚያንም ጊዜ አሥራ ሦስቱ ኤጲስቆጶሳትና እሊህ ሁለቱ ቀሳውስት ጉባኤ አድርገው ይህን ጳውሊ ሳምሳጢን አቅርበው የአባ ዲዮናስን መልእክት በፊቱ አነበቡ። ዳግመኛም #ክርስቶስ#እግዚአብሔር ልጁም ቃሉም የሆነ የጌትነቱ ነጸብራቅ ነው የሚለውን የሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስን ቃል በመጥቀስ እርሱ ከ #አብ#መንፈስ_ቅዱስ ጋር በትክክልነት እንደሚኖር አስረዱት እርሱ ግን ቃላቸውን አልተቀበለም።

ከዚህም በኋላ በእርሱ ትምህርት የሚያምኑትን ሁሉ አው*ግዘው ከምእመናን ለይተው አሳደዱት። ለምእመናንም ሥርዓትን ሠሩ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን አበው በጸሎታቸው ከስሕተት ይጠብቀን በረከታቸውም ትድረሰን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ዘጸይለም

በዚችም ቀን የጸይለም አገር የከበረ አባት ዮሐንስ አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ከሀገሩ ታላላቆች ወገን ናቸው የአባቱም ስም አብርሃም የእናቱም ስም ሣራ ነው እነርሱም ልጆች ስለ ሌሏቸው ብዙ ዘመን ወደ #እግዚአብሔር እየለመኑ ኖሩ።

በአንዲትም ዕለት ሁለት መነኰሳት ወደ እነርሱ እንግድነት መጡ እነርሱም በክብር ተቀብለው አሳደሩአቸው። እሊህ መነኰሳትም አብርሃምን ልጅ የለህምን አሉት እርሱም እንባውን እየአፈሰሰ አባቶቼ ልጅ የለኝም አሁንማ እኔ አረጀሁ የሚስቴም የልጅነቷ ወራት አለፈ ብሎ መለሰላቸው። እሊህ መነኰሳትም ስለ እርሳቸው ጸለዩላቸው ባርከዋቸውም ጎዳናቸውን ተጓዙ።

ከጥቂትም ቀን በኋላ ቅድስትሳራ ፀነሰች ደስ የሚያሰኝም ልጅን ወለደች ስሙንም ዮሐንስ ብለው ሰየሙት በእርሱም ደስ አላቸው የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት እየአስተማሩ አሳደጉት።

ዐሥራ ሰባት ዓመትም በሆነው ጊዜ ወደ መምህሩ ቤት መነኰሳት መጡ ዮሐንስም ከእርሳቸው ጋር እንዲወስዱት ለመናቸው እነርሱም አባትህን እንፈራለንና እኛ አንወስድህም አሉት። መነኰሳቱም ወደቦታቸው እየሔዱ ሳሉ ወደ መረጠው ጎዳና ይመራው ዘንድ ዮሐንስ ተነሥቶ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ ከመምህሩም ቤት ወጥቶ ሊደርስባቸው ወዶ መነኰሳቱን በኋላቸው ተከተላቸው ወደ ታላቅ ወንዝም ደረሰ ብቻውንም መሻገር ፈርቶ ቆመ ከዚያም ሳለ ዓረቦች ከግመሎቻቸው ጋር መጡ ያሻገሩትም ዘንድ ለመናቸው እነርሱም ከእርሳቸው ጋር አሻገሩት አንወስድህም ወደአሉት መነኰሳት ወደ ገዳማቸው በ #እግዚአብሔር ፈቃድ ደረሰ።

ከእርሳቸውም አንዱ አባ ስምዖን የሚባለው ዮሐንስን ወስዶ ደቀ መዝሙሩ አድርጎ ከሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ጋር አኖረው።

አባ ስምዖን የሚሞትበት ጊዜ እንደቀረበ በአወቀ ጊዜ ልጆቹን ጠርቶ ከሞትኩ በኋላ በእናንተ ላይ የሚሆነውን #እግዚአብሔር ያሳየኝን እነግራችሁ ዘንድ ልጆቼ ኑ አላቸውና ከእናንተ አንዱን ጅብ ነጥቆ ይወስደዋል። ሁለተኛው ወደ ዓለም ተመልሶ ይባክናል። የሦስተኛው ግን ዜናው በዓለሙ ሁሉ ይሰማል አላቸው።

ከዚህም በኋላ አረጋዊው ስምዖን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ተመልክቶ ልጄ ሆይ በ #ክርስቶስ ፍቅር ጽና ለብዙዎች አባት ልትሆን እርሱ መርጦሃልና አለው። አባ ስምዖንም ከአረፈ በኋላ በሦስተኛው ቀን አንዱ ረድዕ ወደ ዓለም ተመልሶ ሚስት አገባ ሁለተኛው ወዴት እንደ ደረሰ አልታወቀም። አባ ዮሐንስም ብቻውን ቀረ ፈጽሞ አዘነ በልቡ እንዲህ አለ የጓደኞቼን ወሬ እጠይቅ ዘንድ ከገዳም ወጥቼ ልውረድ ይህንንም ብሎ ከገዳሙ ወጥቶ ሲወርድ የጸይለም ጦረኞች ተቀበሉት ደም ግባታቸው ከሚአምር ከሁለት ሴቶች ጋር አሥረው ወሰዱት በጒዞም ላይ እያሉ ለእንስሶቻቸውና ለራሳቸው የሚጠጡት ውኃ አጡ። አባ ዮሐንስም ከዚህ በረሀ ውስጥ ፈጣሪዬ ውኃን ቢአወጣላችሁ ትለቁኛላችሁን አላቸው አዎን አሉት። በዚያንም ጊዜ አባ ዮሐንስ በስመ #አብ #ወወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ብሎ በምድር ላይ አማተበ ውኃም ፈልቆላቸው ጠጥተው ረኩ።
የከበረ ዮሐንስም ቃል ኪዳን እንደ ገባችሁልኝ አሰናብቱኝ አላቸው እነርሱም እንዳንተ ያለ አናገኝምና ከቶ አንለቅህም አሉት። ይህንንም ብለው ወደ አገራቸው ወደ ጸይለም አደረሱት።

በዚያንም ወራት በጸይለም አገር ታላቅ መቅሠፍት ወረደ የአበ ዮሐንስም ጌታው ከቤተሰቦቹ ሁሉና ከልጆቹ ጋር ሞተ ሚስቱም ከአንዲት ልጅዋ ጋር ብቻዋን ቀረች። የጌታውም ሚስት ቅዱስ ዮሐንስን መሠርይ እንደ ሆነ አሰበች በማደሪያውም ውስጥ እያለ ሊአቃጥሉት እሳት ለቀቁበት #እግዚአብሔርም ከእሳት ውስጥ በደኅና አወጣው የጸይለም ሰዎችም ይህን ድንቅ ተአምር አይተው ሴቶችም ወንዶችም በ #ጌታችን አምነው በእጆቹ ተጠመቁ።

ከዚያም ተነሥቶ ወደ ሌላ አገር ሔደ። የአገር ሰዎችም ዛፎችን ሲያመልኩ አግኝቷቸው እርሱም ከክህደታቸው እንዲመለሱ አስተማራቸው ባልሰሙትም ጊዜ ምሳር ይዞ በሌሊት ወደ ዛፎቹ መካከል ገብቶ ክብር ይግባውና ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ ምሳሩንም አንሥቶ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም እቆርጣችኋለሁ አለ። ወዲያውኑ በአንዲት ምት ዐሥር ሽህ ዛፎች ወደቁ የሀገር ሰዎችም ይህን ድንቅ ተአምር አይተው ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ አመኑ ሁሉም ከሴቶችና ከልጆች ጋር ተጠመቁ።

ከዚያም ዳግመኛ ወደ ሌላ አገር ሔደ ሰዎችንም እሳትን ሲያመልኩ አገኛቸው እርሱም ይህን ደንቊርናቸውን ይተዉ ዘንድ አስተማራቸው ገሠጻቸውም እነርሱም በእርሱ ላይ ተቆጥተው ከእሳት ጨመሩት። እርሱም በደኅና ወጣ ሦስት ጊዜም ጨምረውት በደኅና ወጣ ውኃቸውንም ደም አደረገባቸው የሚጠጡትም አጥተው በተጨነቁ ጊዜ ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_ኢየሱስ ሁሉም አመኑ። አራት መቶ ሽህ ሰዎችም በእጁ ተጠመቁ ቤተክርስቲያንም ሠራላቸው አስተምሮም በቀናች ሃይማኖት አጸናቸው ቁጥር የሌላቸው ድንቆች ተአምራትንም አደረገ #እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም በፍቅር አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት_19)
#ጥቅምት_፲፱ (19) እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ_ኤርትራ_አገር የሚገኘውን በተፈጥሮአዊ አቀማመጡ እጅግ አስደናቂውን #ፃዕዳ_ዓምባ_ቅድስት_ሥላሴ_ገዳምን ለመሠረቱት ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ሰይፈ_ሚካኤል ለዕረፍታቸው ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል #እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።

#አቡነ_ሠይፈ_ሚካኤል ከአባታቸው ከዓምደ ሚካኤልና ከእናታቸው ከኅሪተ ማርያም ተወለዱ፡፡ ወላጆቻቸው #እግዚአብሔርን የሚፈሩና በጾም ጸሎት የተወሰኑ የዋኆች ስለነበሩ በሃይማኖትና በምግባር ኮትኩተው አሳድገዋቸዋል፡፡ አባታቸው ቃለ #እግዚአብሔር እንዲማሩላቸው ልጃቸውን ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ወስደው ለመምህር ሰጧዋቸው፡፡ መምህሩም በደስታ ተቀብለው ቅዱሳት መጻሕፍትንና ያሬዳዊ ዜማን አስተማሯቸው፡፡

ከዚህም በኋላ አቡነ ሠይፈ ሚካኤል "እኔን ሊከተለኝ የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ #መስቀሉን ተሸክሞ ይከተለኝ" የሚለውን #ጌታችንን ቃል ለመፈጸም ዓለምን ከነምኞቷ ንቀው ትተው #መስቀሉን ተሸክመው #ጌታችን ተከተሉት፡፡ ከዚህም በኋላ አባታችን ወደ ዋሻዎችና ገዳማት እየሄዱ በአድያቦ ቤተ ቂርቆስ የሚባል ገዳም ደርሰው ከአቡነ ኖላዊነኄር ግብረ ምንኵስና እየተማሩ በገዳሙ ውስጥ የነበሩ መነኰሳት እስከሚደነቁ ድረስ በጽኑ ትጋትና በብዙ ትሩፋት በተጋድሎ አገልግሎታቸውን ይፈጽሙ ነበር፡፡ ከጽኑ ተጋድሏቸው የተነሣ ሰውነታቸው እንደ በረዶ ነጭ ሆነ፡፡ በዚህም ምክንያት አቡነ ዕንቆ ብርሃን ልብሰ ምንኵስናና አስኬማ መላእክት አለበሷቸው፡፡ እንዲህ ባለ ጽኑ ገድል በኣድያቦ ከመንፈስ አባታቸው ከአባ ዕንቆ ብርሃን ብዙ ዓመታትን ቆይተው በኋላ ወደ ዋልድባ ሄዱ፡፡ ዋልድባ ከገቡም በኋላ እዛ ከነበሩ ቅዱሳን ተባርከው ጽኑ ተጋድሏቸውን ቀጠሉ፡፡

ከዚያም በዋልድባ ቅዱሳን ፈቃድ ወደ ወገሪቆ አቡነ ተክለሃይማኖት ገዳም ሄደው አበምኔትና መምህር ሆነው አገለገሉ፡፡ አቡነ ሰይፈ ሚካኤል በተሰጣቸው ጸጋ ወንጌልን እያስተማሩና ሕሙማን እየፈወሱ እስከ ጋሽ ባርካ ደብረ ሳላ የሚባል ቦታ ዞሩ፡፡ ይሄን አገልግሎታቸው ከፈጸሙ በኋላ የ #እግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል እየመራ ማረፍያ ቤታቸው ወደሆነችው ፃዕዳ እምባ #ሥላሴ ገዳም በደብረ ከባቦ አደረሳቸው፡፡ በዚያም በጾምና በጸሎት ተጠምደው #እግዚአብሔርን አገለገሉ፡፡ሲጸልዩም እስከ ሰማይ ድረስ ዓምደ ብርሃን ተተክሎ ይታያቸው ነበር፡፡

አባታችን በጸሎት ላይ ሳሉ አጋንንት በእባብና በንብ እየተመሰሉ ይፈታተኗቸው ነበር ነገር ግን አባታችን በጾምና በጸሎት ድል ይነሷቸው ነበር፡፡ በደብረ ከባቦ ቤተ ክርስትያን አንጸው ማኅበር አቋቁመው ለ9 ዓመት ከ6 ወር አገልግሎታቸውን እየፈጸሙና መከራ እየተቀበሉ ከቆዩ በኋላ አንድ ቀን በሰርክ ጸሎት እየጸለዩ ሳለ መልአክ መጥቶ "…ወደ ገዳሙ አስገባሃለሁና ተከተለኝ" አላቸው፡፡ እሳቸውም ከኋላው እየተከተሉ መልአኩ ወደ ዛሬይቱ ወንዶች ብቻ ወደሚገቡባት ገዳም አስገባቸው፡፡ ያቺን ለማየትም ጭምር የምታስፈራዋን መንገድ አባታችን "ጸናፌ ፅልመት"ብለው ሰየሟት፡፡ ከገቡም በኋላ በገዳሙ ውስጥ ቤተ ክርቲያን አንጸው ቤተ ማኅበር አቋቋሙ።

አቡነ ሰይፈ ሚካኤል በተሰጣቸው ጸጋ ርኲሳን መናፍስትን ከሕሙማን ያወጡ ስለነበር እነዚያ አጋንንትም "እዚህ እንድትኖር አንፈቅድልህም" እያሉ በገሃድ ለሞት እስከሚደርሱ ድረስ ዐይናቸውን አፈሰሱባቸው ሆኖም ግን መልአከ #እግዚአብሔር ዳስሶ ዐይናቸውን መልሶ አበራላቸው፡፡ እንዲሁም አጋንንቶቹ በማደርያ ቤታቸው እሳት እያቀጣጠሉ በላያቸውም ትላልቅ ድንጋዮችን እየወረወሩ ከበፊቱ በእጅጉ ይፈታተኗቸው ነበር፡፡ እነዚያ የተወረወሩባቸው ድንጋዮች ግን አቡነ ሰይፈ ሚካኤል ይጸሉዩበት በነበረ ቦታ በደቡብ አቅጣጫ ተተክለው ቀርተዋል፡፡ ድንጋዮቹ እስከ አሁን ድረስ አሉ፡፡

አቡነ ሰይፈ ሚካኤል በአገልግሎታቸው ለሚያምኑ እያጽናኑና እያበረቱ፣ ለማያምኑ ደግሞ አሳምነው እያጠመቁ እስከ ማዕርገ ክህነት አድርሰው ቤተ ክርስትያን ይሠሩላቸው ነበር፡፡ በስተመጨረሻ ቅዱስ አባታችን በብዙ ተጋድሎ ሐዋርያዊ ተልዕኮአቸውንና አገልግሎታቸውን ከፈጸሙ በኋላ ከ #እግዚአብሔር የምሕረት ቃልኪዳን ተቀብለው ጥቅምት 19 ቀን 1722 ዓ.ም በ96 ዓመታቸው ራሳቸው በመሠረቱም በገዳም ፃዕዳ ዓምባ ቅድስ ሥላሴ ዐርፈዋል፡፡

የአባታችን የአቡነ ሰይፈ ሚካኤልን መንገድ የተከተሉ የዚህ ገዳም መነኰሳትም በጾምና በጸሎት ተወስነው #ጌታችን_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ "ሑሩ ወመሐሩ" (ማቴ 28፡19) ባለው አምላካዊ ቃል መሠረት ሐዋርያዊ ተልኮአቸውን እየፈጸሙ ብዙ አብያተ ክርስቲያናን ከከረን እስከ ኦምሓጃር ከዛ አልፎም እስከ ከሰላ ሱዳን አንጸዋል፡፡ በፃዕዳ እምባ ሥላሴ ገዳም ሐምሌ 7 ቀን የ #ሥሉስ ቅዱስ ዓመታዊ ክብረ በዓል እና የአቡነ ሰይፈ ሚካኤል በዓለ ዕረፍታቸው ጥቅምት 19 ቀን በደማቅ ሁኔታ ይከበራል፡፡ በእነዚህ ክብረ በዓላት ላይ በርካታ ምእመናን ከተለያዩ ቦታዎች በመምጣት ከበረከቱ ይሳተፋሉ፡፡ ከአባታችን የአቡነ ሰይፈ ሚካኤል እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸውም ይማረን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ ከገድላት አንደበት።

#ጻድቁ_አቡነ_ሠይፈ_ሚካኤል_ስለመሠረቱት_ፃዕዳ_ዓምባ_ቅድስት_ሥላሴ_ገዳም

#አቡነ_ሰይፈ_ሚካኤል፦ እኚህ ጻድቅ በ1669 ዓ.ም የገደሙት ይህ እጅግ ድንቅ የሆነ ገዳም ፃዕዳ ዓምባ #ቅድስት_ሥላሴ ከኤርትራ በዓንሰባ ዞን ከከረን 25 ኪ.ሜ እርቆ በደቡባዊ ምዕራብ ከባሕር ጠለል በላይ 2500 ሜትር ከፍታ ላይ ይገኛል፡፡ ወደዚህ ድንቅ ገዳም የሚያደርሰው መንገድ ዳገትና ቁልቁለት የበዛበት አስቸጋሪ ከመሆኑ የተነሣ ብርቱ ትዕግሥትና መንፈሳዊ ጽናት ይጠይቃል፡፡ ገዳሙ ለመድረስ ከከረን ከተማ በደቡባዊ ምዕራብ በኩል ወንዞችንና ጋራ ሸንተረሮችን ማቋረጥ ግድ ነው፡፡ ከዚያም "ድንጃ ወርቅ" በተባለ ከገዳሙ እግር ሥር በሚገኘው ረጅሞ ተራራ ከተደረሰ በኋላ ከድንጃ ወርቅ የአንድ ሰዓት ተኩል ዝግዛግ የእግር ጉዞ ያስኬዳል፡፡ ከዚያም "ማዕዶዋይ" ከተተባለው ቦታ ይደረሳል፡፡ ትርጓሜውም በርቀት የሚታይ ማለት ነው፡፡ ከማዕዶዋይ ወደ ገዳሙ ውስጥ ለመግባት ከእግር መረገጫ የማያልፍ ስፋት የሌላት በቀኝና በግራ የምታስፈራ በጭንቅ የሚሻገርዋት "ጸናፌ ጽልመት" ተብላ የምትጠራዋን አስጨናቂ ገደል ማለፍ ግድ ይላል፡፡ ይህቺን ለመሻገርም ሆነ ለማለፍ አስቸጋሪ የሆነችን መንገድ ለብዙ ጊዜ የተመላለሱባት ምእመናን ግን ከባድ እቃ በሸክም ይዘውም ቢሆን ያለ ምንም ፍርሃት ይሻገሩባታል፡፡ በጭንቅ የሚሻገርዋትን ይህችን አስጨናቂ ገደል ከታለፈ በኋላ ቀጥሎ "ደገ ሰላም" ና "መንገደ ሰማይ" የሚባል ወደ ገዳሙ የሚያስገባ ዝግዛግ መንገድ አለ፡፡

አባታችንን ወደዚህ ድንቅ ገዳም እየመራ ይዞአቸው የገባው የታዘዘ መልአክ ነው፡፡ ወደ ገዳሙ ቅጥር ውስጥ ከተገባ በኋላ ዕፁብ ድንቅ የሆኑ ልዩና መንፈሳዊ ሐሴትን የሚሞሉ በርካታ ተአምራት የተፈጸመባቸውን ነገሮችን መመልከት ይቻላል፡፡ተአምራቶቹም "ድሮ እንዲህ ነበር፣ እንደዛ ተደረገ…" ተብሎ በአፈ ታሪክ ብቻ የሚወራ ሳይሆን አሁንም ድረስ በዐይን የሚታዩ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ገዳሙ አጠገብ የሚገኙት ዛፎች ብዙ ዕድሜ ከማስቆጠራቸው የተነሣ በንፋስ ኃይል ሲወድቁ ወደ ታች መውደቅ ሲገባቸው በተቃራኒው ግን ዛፎቹ የሚወድቁት ወደ ላይ ነው፡፡ በተጨማሪም ገዳሙ ውስጥ በላዔ ሥጋ ሥጋን የሚበላ ንስር ሳይቀር እንኳን የሞተ እንስሳም ቢያገኝ ሥጋ የሚባል ነገር አለመብላቱ አሁንም ድረስ በዐይን የሚታይ
እውነታ ነው፡፡

እንዲሁም እዚህ ድንቅ ገዳም ውስጥ መርዛማ እባብም ነድፎ ሰው ሊገድል አይችልም፡፡ በእባቡ የተነደፈ ሰው እንኳን ቢኖር በጉንዳን የተነከሰ ያህል ይሰማዋል እንጂ ፈጽሞ አይሞትም፡፡ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ ላይ "ለሚያምኑ እነዚህ ምልክቶች ይከተሉዋቸዋል፡- በስሜ አጋንንትን ያወጣሉ፣ እባቡን ይይዛሉ፣ የሚገድል መርዝ ቢጠጡ እንኳን ከቶ አይጎዳቸውም" ያለው አምላካዊ ቃል እዚህ ገዳም ውስጥ ባለንበት ዘመን በግልጽ በተግባር ይታያል፡፡ ማር 16፡16-18፣ ሐዋ 28፡3-6፡፡ እንዲሁም በዚህ ገዳም ውስጥ ከነበሩ ዛፎች ውስጥ አንዱ ዳዕሮ የተባለ ትልቅ ዛፍ አለ፡፡ ከዚህ ልዩ ዛፍ ተጠምቆ የሚዘጋጀው መጠጥ ከወይን የሚጥም ኅሊናን የሚመስጥና ሕመምን የሚፈውስ ነበር፡፡ ሌላው በገዳሙ ውስጥ በዐይን ከሚታዩትና ከሚያስደንቁት ተአምራቶች ውስጥ አንዱ በክረምት ወቅት ኃይለኛ ዝናብ ሲጥል በወረደ መብረቅ ምክንያት ገዳሙ ውስጥ የሚገኘው ዐለት ተሰንጥቆ የሀገሪቱ ምስል ተስሎበት ተገኝቷል፡፡ እነዚህና ሌሎችም በርካታ ተአምራት እስከ አሁን ድረስ ጸንተው የሚገኙት የዚህ የፃዕዳ ዓምባ #ቅድስት_ሥላሴ ገዳም መሥራች በሆኑ በአቡነ ሠይፈ ሚካኤል የምሕረት ቃልኪዳን ነው፡፡
#ዳግመኛም በዚህች ዕለት ታላቁ አባት "አቡነ ሐራ ድንግል" ልደታቸው ነው፡፡
አቡነ ሐራ ድንግል፡- ጻድቁ ከአባታቸው ከሬማው ካህን ከቅዱስ ዮሐንስ ከእናታቸው ብፅዕት ወለተ ጊዮርጊስ የተወለዱት ጥቅምት 19 ቀን 1534 ዓ.ም ነው፡፡ የትውልድ ሀገራቸው ጥንት በጌምድር ደብረ ታቦር አውራጃ ደራ ወረዳ ይባል በነበረው አሁን በምዕራብ ጎጃም ዞን ባሕር ዳር ዙሪያ ወረዳ ላጉና ቀበሌ ነው፡፡ ቅዱሳን የሆኑ ወላጆቻቸውም አባታችንን ከልጅነታቸው ጀምሮ በሃይማኖት በምግባር ኮትኩተው አሳደጓቸው፡፡ አባታችንም የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት በሙሉ ተምረው በታላቅ መንፈሳዊ ተጋድሎና አገልግሎት ከኖሩ በኋላ ዓለምን ፍጹም ንቀው መንነው ወደ ሸዋ ተጉዘው ግራርያ ከሚባል አገር ደረሱ፡፡ በዚያም ዘመዶቻቸው ፈልገው ስላገኙዋቸውና ወደ ሀገራቸው ስለመለሷቸው በሌላ ጊዜ ጥቅጥቅ ያለውን ጫካ አቋርጠው አሁን ገዳማቸው ካለበት ጫካ ውስጥ ገቡና ገዳመ ወንያትን መሠረቱ፡፡ በዚያም ፈተናውን ሁሉ ድምጸ አራዊቱን፣ ግርማ ሌሊቱን፣ ብርዱን፣ ሐሩሩን፣ ረሃብ፣ ጥማቱን ታግሰው በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ፡፡ ሰይጣንም በፈተና ሊጥላቸው አንድ ጊዜ በተዋበች ቆንጆ ሴት እየተመሰለ አንድ ጊዜ ደግሞ በሞተ ሰው እየተመሰለ እስከ ሰባት ተከታታይ ቀናት ድረስ ቢፈትናቸውም ድል አድርገውታል፡፡
አባታችን ቀን ላይ ጸሎት እያደረጉ እያለ ነብር የሚያባርራት አንዲት ሚዳቋ መጥታ ከቤት ገብታ ከአቡነ ሐራ ድንግል እግር ስር አረፈች፡፡ ነብሩም ደርሶ ከደጅ እየተቆጣ ቆመ፡፡ ይህን ጊዜ አባታችን ‹‹እርሷን ገድለህ ትበላ ዘንድ #እግዚአብሔር አልሰጠህምና ሂድ›› ባሉት ጊዜ ቃላቸውን ሰምቶ ሄደ፡፡ ሚዳቆዋም እዛው አድራ ሲነጋ በሰላም አሰናብተዋታል፡፡
አባታችን መንኩሰው በገዳማቸው ከገቡበት ፈጽመው ሳይወጡ ለ14 ዓመት በተአቅቦ ተቀምጠዋል፡፡ በአንድ ወቅት ጠላት ተነስቶ አካባቢውን በሙሉ በመውረር ሁሉን ሲማርኩ ገዳሟን አይተው ወደ እርሷም ሊገቡ ሲሉ በተአምራት ባሉበት ተይዘው ቆመው በመቅረታቸው ጉዳት ሳያደርሱባት ተመልሰዋል፡፡ ሱስንዮስ ‹‹ሁለት ባሕርይ ሁለት አካል›› የሚለውን የሮማን የረከሰ ሃይማኖት በሀገራችን ላይ እውጆ ብዙዎች ሰማዕትንትን ሲቀበሉ አቡነ ሐራ ድንግል በገዳማቸው ለብዙዎች መጠጊያ ሆነው ሃይማኖታቸውን ሲያስተምሯቸውና ሲያፀኗቸው ነበር፡፡ በንጉሡም ፊት ቀርበው በድፍረት ‹‹አንድ አካልና አንድ ባሕርይ የሆነውን መለኮትና ትስብእትን ለምን ከሁለት ወገን ትከፍለዋለህ?›› ብለው ሲገስፁት ፈርቶ አሽከሮቹን ‹‹ይህን መነኩሴ ከቤቴ አውጥታችሁ በፍጥነት ወደ ገዳሙ አድርሱልኝ›› ብሏቸዋል፡፡ እመቤታችንን ድንግል #ማርያምን እጅግ አድርገው ይወዷት ነበርና ምስጋናዋን ሲያደርሱ ሦስት ክንድ ከምድር ከፍ ይሉ ነበር፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም የሁልጊዜ ጠባቂያቸው ነበር፡፡ በ1574 ዓ.ም አሁን በስማቸው ወደሚጠራው ገዳመ ወንያት መንነው ገቡ፡፡ በዚያም ወንጌልን እያስተማሩ፣ እጅግ ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን እያደረጉ፣ ሙት እያስነሱ፣ ድውያንን እየፈወሱ #እግዚአብሔርን ሲያገለገሉ ኖረዋል፡፡
አባታችን ሐራ ድንግል ‹‹የማነ ብርሃን›› የሚባል ታማኝ አገልጋይ አህያ ነበራቸው፡፡ አህያውም ጸሎታቸው ይጠብቀው ነበር እንጂ እረኛ አልነበረውም፡፡ አንገቱ ላይ ቃጭል አስረው ወደ ገበሬው አውድማ ይልኩትና አህያውም ቃጭሉን እያጮኸ ወደ አውድማው ሁሉ ሄዶ እየዞረ ‹‹ #ማርያም ባርኪ›› በረከት ሰፍረው ይጭኑታል፡፡ አህያውም ከገበሬው ሁሉ የሰበሰበውን እህል ይዞ ወደ አቡነ ሐራ ድንግል ይገባል፡፡ በፈለጉትም ሰዓት ራሱ አውቆ ይመጣላቸው ነበር፡፡ አህያውም አርጅቶ ሲሞት እንደ ሰው አልቅሰውና በአዲስ ጨርቅ ጠቅልለው ቀብረውታል፡፡ አህያቸው የማነ ብርሃን ከተቀበረበት ቦታ ላይ ጸበል ፈልቆ አስደናቂ ተአምራትን አድርጓል፡፡ የቅዱሳኑ በረከታቸው እስከምን ድረስ እንደሆነ ልብ ይሏል፡፡
ታላላቆቹ ቅዱሳን እንደነ በትረ ማርያም፣ አባ ጽጌ ድንግል፣ ቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ያሉ ሌሎችም በርካታ ደጋግ ቅዱሳን ዝናቸውን እየሰሙ ከያሉበት እየሄዱ ይጎበኙዋቸውና በረከታቸውን ይቀበሉ ነበር፡፡ አባታችን አቡነ ሐራ ድንግልም በክብር ካረፉ በኋላ በመካነ መቃብራቸው ላይ ለ40 ቀን ብርሃን ሲወርድ በገሃድ ታይቷል፡፡ አፅማቸውም ከዚያው ከገዳማቸው በክብር አርፎ ይገኛል፡፡ በጸሎታቸው ያፈለቁት ጸበልና የመቃብራቸው አፈር ሕመምተኞችን ከተለያዩ ደውያት ሰውንም እንስሳትንም እየፈወሰ ይገኛል፡፡ አፈራቸውና ጸበላቸው ለሥጋ ደዌ፣ ለእብጠት፣ ለቁስል፣ ለለምፅና ለመሳሰሉት ፍቱን መድኃኒት ነው፡፡ በዓለ ዕረፍታቸው ጥር 11 ቀን 1624 ዓ.ም ነው፡፡

የአቡነ ሐራ ድንግል ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!!
🌹የጥቅምት_19_ግጻዌ

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጥቅምት_19_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ቲቶ 3
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁸ ቃሉ የታመነ ነው። እግዚአብሔርንም የሚያምኑት በመልካም ሥራ በጥንቃቄ እንዲጸኑ፥ እነዚህን አስረግጠህ እንድትናገር እፈቅዳለሁ። ይህ መልካምና ለሰዎች የሚጠቅም ነው፤
⁹ ነገር ግን ሞኝነት ካለው ምርመራና ከትውልዶች ታሪክ ከክርክርም ስለ ሕግም ከሚሆን ጠብ ራቅ፤ የማይጠቅሙና ከንቱዎች ናቸውና፤
¹⁰-¹¹ መለያየትን የሚያነሣ ሰው ጠማማ እንዲሆን በራሱም ላይ ፈርዶ ኃጢአትን እንዲያደርግ አውቀህ፥ አንድ ጊዜ ሁለት ጊዜም ከገሠጽኸው በኋላ እንዲህ ከሚመስል ሰው ራቅ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ዮሐንስ 2
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²² ክርስቶስ አይደለም ብሎ ኢየሱስን ከሚክድ በቀር ውሸተኛው ማን ነው? አብንና ወልድን የሚክድ ይህ የክርስቶስ ተቃዋሚ ነው።
²³ ወልድን የሚክድ ሁሉ አብ እንኳ የለውም፤ በወልድ የሚታመን አብ ደግሞ አለው።
²⁴ እናንተስ ከመጀመሪያ የሰማችሁት በእናንተ ጸንቶ ይኑር። ከመጀመሪያ የሰማችሁት በእናንተ ቢኖር፥ እናንተ ደግሞ በወልድና በአብ ትኖራላችሁ።
²⁵ እርሱም የሰጠን ተስፋ ይህ የዘላለም ሕይወት ነው።
²⁶ ስለሚያስቱአችሁ ሰዎች ይህን ጽፌላችኋለሁ።
²⁷ እናንተስ ከእርሱ የተቀበላችሁት ቅባት በእናንተ ይኖራል፥ ማንም ሊያስተምራችሁ አያስፈልጋችሁም፤ ነገር ግን የእርሱ ቅባት ስለ ሁሉ እንደሚያስተምራችሁ፥ እውነተኛም እንደ ሆነ ውሸትም እንዳልሆነ፥ እናንተንም እንዳስተማራችሁ፥ በእርሱ ኑሩ።
²⁸ አሁንም፥ ልጆች ሆይ፥ በሚገለጥበት ጊዜ እምነት እንዲሆንልን በመምጣቱም በእርሱ ፊት እንዳናፍር በእርሱ ኑሩ።
²⁹ ጻድቅ እንደ ሆነ ካወቃችሁ ጽድቅን የሚያደርግ ሁሉ ከእርሱ እንደ ተወለደ እወቁ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 20
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁸ በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።
²⁹-³⁰ ከሄድሁ በኋላ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ተኩላዎች እንዲገቡባችሁ፥ ደቀ መዛሙርትንም ወደ ኋላቸው ይስቡ ዘንድ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ ሰዎች በመካከላችሁ እንዲነሡ እኔ አውቃለሁ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_19_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇🌹

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወሶበሂ ይትዋቀስ ይፃእ ተመዊዖ። ወጸሎቱሂ ትኩኖ ጌጋየ። መይኩና መዋዕሊሁ ኅዳጠ"። መዝ 108፥7-8።

#ትርጉም፦ "በተምዋገተም ጊዜ ተረትቶ ይውጣ፤ ጸሎቱም ኃጢአት ትሁንበት። ዘመኖቹም ጥቂት ይሁኑ፤ ሹመቱንም ሌላ ይውሰድ"። መዝ 108፥7-8።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_19_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማቴዎስ 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁵ እውነት እላችኋለሁ፥ በፍርድ ቀን ከዚያች ከተማ ይልቅ ለሰዶምና ለገሞራ አገር ይቀልላቸዋል።
¹⁶ እነሆ፥ እኔ እንደ በጎች በተኵላዎች መካከል እልካችኋለሁ፤ ስለዚህ እንደ እባብ ልባሞች እንደ ርግብም የዋሆች ሁኑ።
¹⁷ ነገር ግን ወደ ሸንጎ አሳልፈው ይሰጡአችኋል፥ በምኩራቦቻቸውም ይገርፉአችኋልና ከሰዎች ተጠበቁ፤
¹⁸ ለእነርሱና ለአሕዛብም ምስክር እንዲሆን፥ ስለ እኔ ወደ ገዥዎች ወደ ነገሥታትም ትወሰዳላችሁ።
¹⁹ አሳልፈውም ሲሰጡአችሁ፥ የምትናገሩት በዚያች ሰዓት ይሰጣችኋልና እንዴት ወይስ ምን እንድትናገሩ አትጨነቁ፤
²⁰ በእናንተ የሚናገር የአባታችሁ መንፈስ ነው እንጂ፥ የምትናገሩ እናንተ አይደላችሁምና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️ 🌹
#ሚቀደሰው_ቅዳሴ_የእመቤታችን_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የአበው ኢጲስ ቆጶሳት፣ የቅዱስ በርተለሜዎስና ሚስቱ፣ የቅዱስ ዮሐንስ ዘለምጽ፣ የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ፣ የአቡነ የሰይፈ ሚካኤል የዕረፍት በዓል፣ የአቡነ ሐራ ድንግል የልደት በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
" #ይምርሐነ_ፍታኝ! "

በባሕር ላይ የታነጸው ቤተመቅደስ እና የቅዱስ ይምርሐነ #ክርስቶስ መካነ መቃብር!

#ጌታችን "ሥጋዬን እየፈተትህ ለሕዝቦቼ ትነግሥላቸው ዘንድ መንግሥትን ለአንተ ሰጠሁህ" ብሎ በተቀደሱ እጆቹ የንግሥና ቅባትን ቀባው፡፡ በዚህም ጊዜ ይምርሐነ #ክርስቶስ "...አምላኬ ሆይ እኔ ከሁሉ ይልቅ ታናሽ ነኝና እባክህ ታነግሥ ዘንድ ሌላ ሰው ምረጥ" ብሎ ከ #ጌታችን ጋር በትሕትና ተከራከረ፡፡ #ጌታችን በቅዱስ ቃሉ "ክህነትህ ምድራዊ አይደለም፣ ሰማያዊ ነው እንጂ" ብሎታል፡፡

ቅዱስ ይምርሐነ #ክርስቶስ ገና ሲወለድ አንደበቱን ፈቶ #እግዚአብሔርን በአንድነቱ በሦስትነቱ ያመሰገነ ታላቅ ጻድቅ ሲሆን 40 ዓመት ሙሉ ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ ከሰማይ እየደወረደለት ቀድሷል፡፡

#እግዚአብሔርን ጌትነትና የይምርሃነ #ክርስቶስ የቅድስና ሕይወት በዓለም ሁሉ መሰማት እንደጀመረ የሮም ሰዎችም ወደ እርሱ መጥተው 55 ውድ መስቀሎችን በስጦታ ገበሩለት፡፡ #እግዚአብሔር በእርሱ ላይ የሚያደርገውን ተአምርና ቅድስናውን የሰሙ ቁጥራቸው 5740 የሆኑ የግብፅና የሮም ጳጳሳትና ኤጲስቆጶሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት እንዲሁ መነኮሳት ቅዱስ ይምርሃነ #ክርስቶስ የሚወርድለትን ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ በእጁ ለመቀበልና በመስቀሉ ለመባረክ መጡ፡፡ የግብፁ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ አትናቴዎስም ‹‹ከዚህ ቅዱስ የ #እግዚአብሔር አገልጋይ እጅ በረከትን መቀበል እሻለሁ›› ብሎ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ከቅዱስ ይምርሃነ #ክርስቶስ ጋር ተገናኝቶ ሁለቱም በረከትን አንዳቸው ከአንዳቸው ተቀብለዋል፡፡ ቅዱስ ይምርሃነ #ክርስቶስም ወደ እርሱ ለመጡት 5740 ደጋግ ጳጳሳትና ኤጲስቆጶሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት እንዲሁ መነኮሳት ሁሉ ቀድሶ ሰማያዊውን ሥጋ ወደሙን አቀብሏቸዋል፡፡ እነርሱም ሰማያዊውን ሥጋና ሰማያዊውን ደሙን ከተቀበሉ በኋላ "ይህን ባየንበትና በቀመስንበት ሌላ አናይም አንቀምስም" ብለው የተወሰኑት ወደሌሎች የአገራችን ገዳማት የሔዱ ሲሆን ብዙዎቹ ደግሞ ከእርሱው ጋር አብረው በዚያው ዐርፈው ተቀብረዋል፡፡ ዛሬም ድረስ የእነዚህ ቅዱሳን ዐፅም ቤተ መቅደሱ ካለበት ጀርባ በኩል በሚገኘው ትልቅ ዋሻ ውስጥ በክብር ተቀምጦ ይገኛል፡፡

በመጀመሪያ ቅዱስ ይምርሐነ #ክርስቶስ በድንኳን ውስጥ ህብስቱና ወይኑ ከሰማይ እየወረደለት ሕዝቡን ያቆርብ ነበር፡፡ #ጌታችንም ተገልጾለት "እስከ ዕለት ምጽአት ድረስ ፈጽሞ የማትፈርስ ቤተ መቅደስ ትሠራለህና ተነሥተህ ሂድ ቦታውን ቅዱሳን ገብርኤልና ሩፋኤል ይመሩሃል" አለው፡፡ በመንገዱም ዕውራንን እያበራና ተአምራትን እያደረገ ተጓዘ፡፡ ቦታው ላይ ሲደርስም #ጌታ አሁንም ተገልጾ ስለ ቤተ መቅደሱ አሠራር ነገረው፡፡ ቤተ መቅደሱንም እንዲሠራ ያዘዘው ከባሕር ላይ ነው፡፡ "በዚህ ባሕር ላይ እንዴት አድርጌ እሠራለሁ?" ብሎ #ጌታችንን ቢጠይቀው እንጨት፣ ድንጋይና ጭቃ እየረበረበ እንዲሠራ ነገረው፡፡ ዕቃዎቹንም ከኢየሩሳሌም በደመና ሠረገላ እየተመላለሰ አምጥቶ እንደታዘዘው አድርጎ አንጾታል፡፡ የቤተ መቅደሱ ልዩ የሆነ የአሠራር ዘዴ ባሕሩን ከታች እንዲሰወር ቢያደርገውም በባሕር ላይ ለመሠራቱ ዛሬም ድረስ ምልክቱ በግልጽ ይታያል፡፡ ቤተ መቅደሱን በሰባቱ ሰማያት መስሎና ከፍሎ ያስጌጠበት ጥበብ ዛሬ በዓለም ላይ የትኛውም አርክቴክት ፈጽሞ ሊሠራው አይችልም፡፡

ጥቅምት 19-ንግሥናን ከክህነት ጋር አስተባብሮ በመያዝ 40 ዓመት ሙሉ ሰማያዊ ኅብስትና ጽዋ ከሰማይ እየደወረደለት የቀደሰው ጻድቁ ንጉሥ ቅዱስ ይምርሐነ #ክርስቶስ ዕረፍቱ ነው፡፡ ሕዝቡንም የሚባርክበት #መስቀል ከሰማይ የወረደለት ሲሆን ቤተ መቅደሱን በባሕር ላይ እንዲሠራ ራሱ #ጌታችን በቃሉ ከነአሠራሩ ጭምር ያስረዳው ነው፡፡

#ጌታችንም በድጋሚ ከመላእክቶቸቱ ጋር ተገልጾ ቃልኪዳን ሰጠው፡፡ “ለኃጢአተኞች መዳን ምክንያት ሆነህ ታድናቸው ዘንድ እኔ ወደቦታህ እመልስሃለሁ፤ እኔና የባሕርይ አባቴ #አብ የባሕርይ ሕይወቴ #መንፈስ_ቅዱስ ካልፈቀድንለት በቀር ቦታህን ማንም አይረግጥብህም፤ በቦታህም መጥቶ መካነ መቃብርህን እየዞረ አቡነ ዘበሰማያት እያለ አምላከ ይምርሃነ #ክርስቶስ ማረኝ ያለውን ሰው ዕለቱን እንደተጠመቀ ከእናቱም ማኅፀን እንደተወለደ ሕፃን ልጅ አደርገዋለሁ፡፡ ቦታዋም ዳግማዊ ኢየሩሳሌም ትሁንልህ…” የሚል ድንቅ ቃልኪዳን ገብቶለታል፡፡ በዚህ ቃልኪዳን መሠረት ቅዱስ መካነ መቃብሩ እየተዞረና አቡነ ዘበሰማያት ከተባለ በኃላ ሦስት ጊዜ "ይምርሐነ ፍታኝ! " ይባላል፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜም ድረስ ከቅዱስ መካነ መቃብሩ " #እግዚአብሔር ይፍታህ" የሚል ጽምፅ ይሰማ ነበር፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን አባቶቻችን በሱባኤ ጠይቀው ድምፁ እንዲጠፋ አድርገውታል፡፡

የቅዱስ ይምርሃነ #ክርስቶስ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን!

"ይምርሐነ ፍታኝ! "
2025/10/31 09:51:02
Back to Top
HTML Embed Code: