Telegram Web Link
+ አባቶቻችን እንዲህ አሉ +

"በኃጢአት በወደቅህ ጊዜ ተስፋ ቆርጠህ ጸሎትህን እንዳታቆም። ንስሓ እስከምገባ ድረስ ብለህ ጸሎት ካቆምክ መቼም ንስሓ አትገባም። ምክንያቱም ጸሎት ራሱ የእውነተኛ ንስሓ መግቢያ በር ነው" ቅዱስ ቄርሎስ ሳድሳዊ

"ሰዎች አንድ ሰው ተነሥቶ ሌላውን ሲገድል ወንጀለኛ ነህ ይሉታል። አንድ ላይ ተሰባስበው ብዙ ሰዎችን ሲገድሉ ግን ውጊያ ይሉትና መግደላቸውን ጀግንነት ይሉታል" ቅዱስ ቆጵሮሳዊ

"ሰዎች የሚያብዱበትና እንደነሱ ያላበደ ሰው ሲያዩ "እንደኛ ስላልሆንክ አብደሃል" የሚሉበት ዘመን ይመጣል"
ቅዱስ እንጦንዮስ

"መካሪ አያስፈልገኝም የማለትን ያህል ታላቅ ትዕቢት የለም"
ቅዱስ ባስልዮስ

"ይህንን ካስታወስክ በሰው መፍረድ ታቆማለህ:: ይሁዳ ሐዋርያ ነበር:: ከጌታ ቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ ነፍሰ ገዳይ ነበር" ቅዱስ ዮሐንስ ዘሰዋስው

"የክርስቲያኖች መሣሪያ በእጃቸው ሰይፍን መታጠቅ ሳይሆን እጃቸውን ወደላይ ለጸሎት መዘርጋት ነው"
ቅዱስ አትናቴዎስ ዘእስክንድርያ

"እግዚአብሔር ለአብርሃም "ከሀገርህ ውጣ ከወገኖችህ"ተለይ ብሎት ነበር። በዚህ ጥሪ እግዚአብሔር ሁላችንንም የተወለድንበት ዘር እንድንተው ይጠራናል። ሰማዕቱ ዮስጦስ (100 AD-165 AD)

"ክርስቶስ ጴጥሮስን "ሰይፍህን ወደ ሰገባው አስገባ" ሲለው ትጥቅ ያስፈታው ጴጥሮስን ብቻ ሳይሆን እንደ ጴጥሮስ በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ ነበር" ሊቁ ጠርጡለስ

‹‹ይጸልያል ነገር ግን የሌሎችን ጸሎትም ይሰማል፡፡ ያለቅሳል የሌሎችን ዕንባ ግን ያብሳል፡፡ ሰው ነውና አልዓዛር ወዴት እንደተቀበረ ጠየቀ፡፡ አምላክ ነውና አልዓዛርን ከሞት አስነሣ፡፡ እርሱ በርካሽ ዋጋ ያውም በሠላሳ ብር ብቻ ተሸጠ፡፡ ነገር ግን ዓለምን በውድ ዋጋ በከበረ ደሙ ገዛ፡፡ እንደ በግ ለመታረድ ተነዳ እርሱ ግን የእስራኤል እረኛ የዓለምም ሁሉ ጠባቂ ነበረ፡፡ እንደ በግ ዝም አለ ነገር ግን እርሱ በምድረ በዳ በሚጮኽ ሰው ድምፅ የተሰበከ ቃል ነበር፡፡ እርሱ የተሰቃየና የቆሰለ ነበር ፤ ሁሉንም በሽታና ቁስል ግን ይፈውስ ነበር›› ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ

"ለቤተ መቅደስህ ተክል ያደረግኸኝ፡፡ አቤቱ ሆይ የውጭ ተክል አታድርገኝ፡፡ የጽድቅ ተክል አድርገኝ፡፡ የኃጢአት አይደለም፡፡ የዕውነት ተክል አድርገኝ የሐሰት አይደለም የፍቅር ተክል አድርገኝ የጽል አይደለም፡፡

የመጻሕፍት መጀመሪያ የምትሆን ኦሪት ደመና የምትጋርደኝ፡፡ ከቅዱስ ወንጌል ፈሳሽ የምጠጣ ከጎንህ ከፈሰሰው ደም የምረካ ልሁን፡፡ በናትህ በድንግል ጸሎት የሃይማኖት አበባ ላብብ፡፡ የጽድቅ ፍሬን ላፍራ ከቅዱሳንህ ሐዋርያትም ከቃላቸው ፍሬ የተነሣ እስከ ዘለዓለሙ ድረስ የተባረከ የወይን ቦታ ልባል የጽድቅን ፍሬ የሚያስቀረውንም የኃጢአት እሾህ ጠምዝዘው ከደጁም አሜከላውን አረሙንም ሙጃውንም ንቀለው፡፡ አቤቱ ከኔም አርቀው ሥርዓትህን የሚሠሩትን ያበባቸውን ፍጻሜ እንዳፈራ አድርገኝ" ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ግንቦት 26 2011
ጅማ ፣ ኢትዮጵያ

https://www.tg-me.com/deaconhenokhaile
"ዘበኀበ: አብ ወልድ ፤ ወበመንፈስ ቃል ፤ ወእምድንግል ሕፃን ፤ ዘበነቢያት ነቢይ ፤ ዘበሐዋርያት ሐዋርያ፤ ዘበሰማዕታት አክሊል ፤ መምህር ፤ ሊቀ ማኅበር ውእቱ ኢየሱስ ክርስቶስ"

ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
+++ ሦስቱ ዛፎች +++

በአንድ ኮረብታ ጫፍ ላይ የተተከሉ ሦስት ዛፎች ነበሩ፡፡ እነዚህ ዛፎች የወደፊት ተስፋቸውና ሕልማቸው ምን እንደሆነና ምን መሆን እንደሚፈልጉ መወያየት ጀመሩ፡፡

የመጀመሪያው ዛፍ ‹‹ታላቅ ንጉሥ የሚተኛበት አልጋ ለመሆን እመኛለሁ፡፡ ዙሪያዬን በልዩ ቅርጽ ተሠርቼ ሰው ሁሉ እንዲያከብረኝ ዝናዬ እንዲነገር እፈልጋለሁ›› አለ፡፡

ሁለተኛው ዛፍ ይኼን ሲሰማ የራሱን የተለየ ምኞት ተናገረ፡፡ ‹‹እኔ ደግሞ የምጓጓው ታላቅ መርከብ ሆኜ ለመሠራት ነው! በዓለም ላይ እጅግ ዝነኛ የሆኑ ነገሥታት በእኔ ላይ ተሣፍረው እንዲሔዱና ከጥንካሬዬ የተነሣ ሰዎች እኔ ላይ በመሳፈራቸው ያለ ሥጋት እንዲጓዙ ነው የምፈልገው!›› አለ - መርከብ ሆኖ በባሕር ላይ ሲንሳፈፍ በዓይነ ሕሊናው እየታየው፡፡

ሦስተኛው ዛፍ ግን ‹‹ዛፍነቴን ብተው ያንዘፍዝፈኝ›› አለ፡፡ ‹‹እኔ የምፈልገው ከዚሁ ሳልነቃነቅ ረዥም ዛፍ ሆኜ ወደ ላይ ማደግ ነው፡፡ እጅግ ከፍ ብዬ አድጌ የዛፎች ሁሉ ንጉሥ ሆኜ ፣ ለሰማይ እጅግ ቅርብ ሆኜ ሰዎች በእኔ መሰላልነት ወደ ገነት እንዲገቡና እኔን ባዩ ቁጥር ፈጣሪያቸውን እንዲያስታውሱ እፈልጋለሁ›› አለና ምኞቱን ተናገረ፡፡

ይህን ተነጋግረው እንደጨረሱ አናጢዎች ወደ እነዚህ ዛፎች መጡ

አንደኛው አናጢ የንጉሥ አልጋ ለመሆን የሚመኘውን ዛፍ ቀረብ አለና ካየው በኋላ ‹‹ይኼ ዛፍ ጠንካራ ይመስላል ፤ ወስጄ ለቤት ዕቃ ሠሪዎች እሸጠዋለሁ›› አለ፡፡ ይህን የሰማው ዛፍ ‹የንጉሥ አልጋ› ሆኖ የመሠራት ሕልሙ ዕውን እንደሚሆን በመተማመን ፈነደቀ፡፡ አናጢው ወስዶ የሸጠላቸው እንጨት ሠሪዎች ግን የዛፉን ሕልም ሳይረዱ የንጉሥ አልጋ አድርገው በመሥራት ፈንታ የከብቶች የሣር ድርቆሽ ማስቀመጫ ሣጥን አድርገው ሠሩትና በአንድ በረት ውስጥ ተጣለ፡፡

ሁለተኛው አናጢ የንጉሥ መርከብ እሆናለሁ ብሎ የሚመኘውን ዛፍ ቀረብ ብሎ አየውና ‹‹ይኼ ዛፍ ጠንካራ ይመስላል ፤ መርከብ ወደሚሠሩ ሰዎች ወስጄ ባሳየው ጥሩ ዋጋ ያወጣልኛል›› አለ፡፡ ዛፉ ‹ስዕለቴ ሠመረ› ብሎ ተደሰተ፡፡ ሆኖም መርከብ ሠሪዎቹ ምኞቱን ሳያውቁ ቆራርጠው ቆራርጠው በርከት ያሉ የዓሣ ማጥመጃ ጀልባዎችን ሠሩበት፡፡ መርከብ እሆናለሁ ብሎ የተመኘው ይህ ዛፍ ዓሣ አጥማጆችን ጭኖ እየተንሳፈፈ የንጉሥ መርከብ ሲያልፍ ተመልካች ሆነ፡፡

ሦስተኛውን ዛፍም በመጥረቢያ ሲቆርጡት የዛፎች ንጉሥ ሆኖ ከፍ ብሎ የማደግ ሕልሙን አብረው ቆረጡት፡፡

ከብዙ ዓመታት በኋላ አንዲት የጸነሰች ብላቴና ከአንድ አረጋዊ ጋር ቤተልሔም በሚባል የይሁዳ ከተማ መጣች፡፡ በወቅቱ የማደሪያ ሥፍራ ስላልነበር በከብቶች በረት ውስጥ ለማደር ገቡ ፤ ጸንሳ የነበረችውንም ልጇን በበረት ውስጥ ወለደችው፡፡ የመኝታ ሥፍራ ስላልነበር ሕጻኑን የከብቶቹ የሣር ድርቆሽ በሚቀመጥበት ሳጥን ውስጥ አስተኛችው፡፡ የዚያን ቀን ለተወለደው ሕጻን ከሩቅ የመጡ ነገሥታት ሳይቀር ሥጦታን አመጡለት፡፡ የንጉሥ አልጋ መሆን ይመኝ በነበረው ያ ዛፍ ሳጥን ሆኖ ቢሠራም የነገሥታት ንጉሥ መኝታ ሆነ፡፡

ይህ ከሆነ ከሠላሳ ዓመታት በኋላ የዓሣ ማጥመጃ ሆኖ በተሠራው ጀልባ ላይ ከወትሮው በተለየ ሁኔታ ዓሥራ ሦስት ሰዎች ተሳፈሩበት፡፡ የንጉሥ መርከብ ለመሆን የተመኘው ይህ ጀልባ በጀልባነቱ ዓሥራ ሦስት ተሳፋሪዎችን ተሸክሞ ሲማረር በጉዞ መካከል ድንገት ትልቅ ማዕበል ተነሥቶ መርከቧን ያናውጻት ጀመረ፡፡ ተሳፋሪዎቹ ጀልባዋን ለመቆጣጠር ታገሉ፡፡

ከመካከላቸው ግን አንዱ ተሳፋሪ ተኝቶ ነበር፡፡ ሞገዱ እየባሰ ሲመጣ የተኛውን ተሣፋሪ ‹‹ስንጠፋ አይገድህምን?›› ብለው ቀሰቀሱት፡፡ እሱም ተነሥቶ ማዕበሉን ገሠጸው፡፡ ጀልባው ድሮ እንደተመኘው የጫነው የነገሥታትን ንጉሥ እንደሆነ ተረዳ፡፡

ይህ ከሆነ ከሁለት ዓመታት በኋላ ደግሞ የዛፎች ንጉሥ ለመሆንና ወደ ሰማይ መውጫ መሰላል ለመሆን የተመኘውን ዛፍ አምጥተው ለአንድ ወንጀል ለሌለበት ንጹሕ አሸከሙት ፣ ከተራራ ጫፍ ሲደርሱም ባሸከሙት እንጨት ሰቀሉት፡፡ እንደተሰቀለ ምድር ለሦስት ሰዓታት ጨለመች ... ብዙ ተአምራት ተፈጸሙ፡፡ ይህ ዛፍ እንደተመኘው የዕጽዋት ሁሉ ንጉሥ ሆነ ፤ ሰዎች በእሱ መሰላልነት ወደ ገነት ገቡ ፤ እሱን ያዩ ሁሉ ፈጣሪያቸውን ያስታውሳሉ፡፡

በሁላችንም ሕሊና ውስጥ የእነዚህ ዛፎች ሕልም የተበላሸው ገና ያን ጊዜ ወዳላሰቡት ሥፍራ ሲጣሉ ነበር፡፡ ነገሩ አበቃ ብለን ስናስብ ግን የሦስቱም ምኞት ተሳካ፡፡ ይህ ጥንታዊ ታሪክ ምሳሌ እንጂ እውነተኛ ታሪክ እንዳልሆነ ግልጽ ነው፡፡ በዚህ ታሪክ ውስጥ ግን አንድ እውነታ አለ፡፡ በሕይወታችን ውስጥ እኛ አበቃልን ስንል እግዚአብሔር ሥራውን ይጀምራል፡፡

‹‹የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔርም ያለቀ የተቈረጠ ነገርን በምድር ሁሉ መካከል ይፈጽማል።›› ኢሳ. 10፡23

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ግንቦት 2007 ዓ ም
ኩዌት የተጻፈ [ከሞት ባሻገር በተሰኘው መጽሐፍ የታተመ]

(ይህን በሥነ ጽሑፍ ዓለም የታወቀ ጥንታዊ ትረካ ያገኘሁት Archangel Michael Coptic Orthodox Church News letter (St. Mary Coptic Orthodox Church, East Brunswick, N.J./ volume 3 Feb. 2002) ዕትም ላይ ሲሆን ሃሳቡን ብቻ በመውሰድና አንዳንድ ለውጦች በማድረግ በዚህ መልኩ አስቀምጬዋለሁ፡፡ ይህ ታሪክ ምክር አዘል ምሳሌ ብቻ እንጂ ለተባሉት ዕቃዎችም ሆነ ለመስቀል ታሪካዊ አመጣጥ የሚጠቀስ ተአማኒ ታሪክ እንዳልሆነ አስታውሳለሁ፡፡)
+ ዘኬዎስ አጭር ባይሆን +

ዘኬዎስ በማጠሩ ምክንያት በኢያሪኮ እያለፈ ያለውን ክርስቶስን ለማየት ተቸገረ:: ሕዝቡ ብዙ ነውና የቆሙት ሁሉ ጌታን ከማየት ከለሉት:: የሾላ ዛፍ ላይ ወጥቶ ጌታን ለማየት ሲሞክር ጌታ አሻቅቦ አየው::

እሱ ዛፍ ላይ ጌታን ሊያይ እንጂ ሊታይ አልወጣም:: ጌታ ሊታዩ ከሚሞክሩ ይልቅ ሊያዩት የሚሹትን ይወዳልና ዘኬዎስን ጠራው::

ከምድር ቆመን ዓይናችንን አንጋጥጠን ማረን የምንለው ጌታ ዘኬዎስን ከምድር ሆኖ ወደ ላይ እያየ ና ልማርህ አለው:: "ዛሬ በቤትህ እውል ዘንድ ይገባኛል" አለው:: ጌታ ወደ ቤቱ ገባ:: ለዘኬዎስ ቤት መዳን ሆነለት::

ዘኬዎስ አጭር ባይሆን ኖሮ ከሰዎች ጋር እየተጋፋ ጌታን ያይ ይሆናል እንጂ በጌታው ዓይን ለመታየት የሚያበቃ ትጋት አያሳይም ነበር:: ምናልባትም ሰዎችን ገለል በሉ እያለ በኩራት ሲጋፋ ከአንዱ ጋር ሲጣላ ሊቆይ ይችል ነበር::

ዘኬዎስ አጭር ባይሆን ከዛፍ ላይ አይወጣም ነበር::
ዘኬዎስ አጭር ባይሆን የሠራዊት አምላክ ወደ ቤቱ አይገባም ነበር:: በኪሩቤል ላይ የሚቀመጠው ንጉሥ በቤቱ ወንበሮች ላይ የተቀመጠው ዘኬዎስ በማጠሩ ምክንያት ነው:: የዘኬዎስ ነፍስ የዳነው በቁመቱ ማጠር ነበር:: እግዚአብሔር የመዳኑን ቀን የቆረጠለት ቁመቱን ሲያሳንሰው ነበር:: በምድር በመጽሐፍ ቅዱስ በሰማይ በሕይወት መዝገብ ስሙ የተጻፈው ዘኬዎስ አጭር በመሆኑ ነው::

ስለ ቁመት የማወራ እንዳይመስልህ:: እግዚአብሔር ለነፍሳችን መዳን የሚያሳጥርብን ብዙ ነገር አለ::
እንደ ዘኬዎስ ቁመትህ አጭር ባይሆን የሚያጥርህ ነገር ግን አይጠፋም::

ይሄ ጎደለኝ የምትለው ከሰዎች አነስኩበት የምትለው ነገር አንዳች ነገር የለም? እሱን ማለቴ ነው::
ይሄ ይጎድለኛል ከሰው አንሳለሁ እያልክ አትማረር::
እጥረትህ መክበሪያህ ነው:: ጉድለትህም መዳኛህ ነው::

እግዚአብሔር ያጎደለብህ የመሰለህ ነገር ወደ ዛፍ እንድትወጣ ምክንያትህ ይሁን:: በጉድለትህ እንደ ዘኬዎስ ከፍ በልበት:: ያኔ ሰዎች አንተን አንጋጠው ከማየት ውጪ አማራጭ አይኖራቸውም::
ፈጣሪ በፍቅሩ ይይህ እንጂ ሰዎች ወዳንተ ያዘነብላሉ:: በቤትህ መዳን ይሆንልሃል:: ከዚያም ስላጠረህ ስለጎደለህ ነገር ፈጣሪህን ስታመሰግነው ትኖራለህ::

እመነኝ አንዳንድ ጉድለቶች እድሎች ናቸው::
ዘኬዎስ አጭር ባይሆን ይሄኔ በሾላው ዛፍ ጥርሱን እየፋቀ ይቀር ነበር::

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ግንቦት 23 2014 ዓ.ም.
አዲስ አበባ
ሰይጣን የኢዮብን ሀብት ሲያወድምበት ፣ ዐሥር ልጆቹን ሲገድልበት ፣ ጤናውን ሲወስድበት አንድ ነገር ግን አልነካበትም::

ሚስቱን::

ለምን?

ሚስቱን ያልነካው ምናልባት ነገረኛ ቢጤ ስለሆነች ከኢዮብ መከራ ውስጥ ተቆጥራ ይሆን? ሰይጣን ሚስቱን ያልነጠቀው " ታንገብግበው" ብሎ ይሆን?

ጠቢቡ "በዝናብ ቀን የሚያንጠባጥብ ቤትና ጠበኛ ሴት አንድ ናቸው" ይላል:: ምሳ.27:15 ምናልባት በሰይጣን እይታ ኢዮብን ለማማረር ሚስቱ መቆየት ነበረባት ይሆን?

በእርግጥ የኢዮብ ሚስት "ፈጣሪን ሰድበህ ሙት" የምትል መሆንዋን ስናይ ለኢዮብ ፈተና እንድትሆን ይሆናል ሳንል አንቀርም:: ሰይጣንም እንዲህ ብናስብ አይጠላም::

ነገሩ ግን ወዲህ ነው:: ሰይጣን የኢዮብን ሚስት እንዳይነካት ያደረገው የራሱ የእግዚአብሔር ትእዛዝ ነበር::

"ሕይወቱን ተወው እንጂ እነሆ እርሱ በእጅህ ነው" ብሎ እግዚአብሔር ለሰይጣን አስጠንቅቆት ነበር:: ሕይወቱን አትንካ የተባለው ሰይጣን ሌላውን ሁሉ ሲያጠፋ ሚስቱን ግን ያልነካው ሚስት ሕይወት ስለሆነች ነው:: ሚስቱን መንካትም ራሱን ኢዮብን መንካት ነበር:: አዎ ሚስት ሕይወት ናት:: እንደ ኢዮብ ሚስት ብትከፋም እንደ ምሳ. 31ዋ ሚስት መልካም ብትሆንም ሕይወት ናት:: ሕይወት ደስታም ኀዘንም አለበት:: "ሕይወት እንዲህ ናት" c'est la vie እንዲል ፈረንሳይ:: ራሱ ኢዮብም "በምድር ላይ የሰው ሕይወት ብርቱ ሰልፍ አይደለምን?" ብሎአል:: ኢዮ. 7:1

አዳምም አለ :-

"ይህች አጥንት ከአጥንቴ ይህች ሥጋ ከሥጋዬ ናት"

"አዳምም ሔዋንን ሕይወቴ ነሽ ይላት ነበር"

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 2016 ዓ.ም.
ሕንድ ውቅያኖስ
++ በሰንበት መፍረስ ++

የኢያሪኮ ሰዎች የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔርን ኃይል በመናቃቸው ምንኛ ተጎዱ?! እርሱ ዓለምን የፈጠረ መሆኑን ስላላመኑ እንዳልተፈጠሩ የሆኑት የኢያሪኮ ሰዎች መጨረሻ እጅግ አሳዛኝ ነበር፡፡

ቅጥራቸው ከመፍረሱ በፊት እስራኤል የእግዚአብሔርን ታቦት ይዘው ለስድስት ቀናት ያህል በዝምታ ኢያሪኮን ዞሯት፡፡ ዓለምን በስድስት ቀናት የፈጠረውን ጌታ እንዲያስተውሉ ስድስት የዝምታ ቀናት ተሠጧቸው፡፡ በሰባተኛው ቀን ግን ጮኹ የኢያሪኮም ቅጥር ፈረሰ፡፡

ሰባተኛ ቀን የዕረፍት ቀን ነው፡፡ ለኢያሪኮ ግን የመፍረስ ቀን ሆነባት፡፡ ሰባተኛ ቀን ፈጣሪን ለሚያምኑ የተቀደሰ ቀን ነበር ፤ ለኢያሪኮ ግን የመረገም ቀን ሆነባት፡፡
እግዚአብሔር የፈጠረው ሁሉ መልካም እንደሆነ ባየበት ሰባተኛ ቀን ኢያሪኮ ግን ከፉ እንደሆነች ታየባት፡፡

እግዚአብሔር የሌለበት ሕይወት እንዲህ ነው፡፡ ወዳጄ እግዚአብሔር በሕይወትህ ውስጥ ከሌለ የሰንበት ቀን የነፍስህ ዕረፍት ቀን መሆኑ ይቀርና እንደ ኢያሪኮ የመፍረስ ቀን ይሆናል፡፡ በዚያ ቅዱስ ቀን ቅጥርህን በመጠጥ ፣ በስካር በዝሙት ስታፈርስ ትውልና ታድራለህ፡፡ ራስህን አንድደህ ትሞቃለህ ፤ እያራገብህ ትቃጠላለህ፡፡ ታቦት ይዘው ቢዞሩህም የኃጢአት ግንብን አጥረሃልና አትሰማም፡፡ በላይህ ላይ ቢቀደስብህም እንደ ኢያሪኮ ሰዎች ካህናቱን እያየህ ‘ዝም ብሎ መዞር ምንድር ነው?’ እያልክ ትስቃለህ፡፡ የካህናቱ የቅዳሴ ዜማ ለአንተ የሚያፈርስ ጩኸት ይሆንብሃል፡፡ የኢያሪኮ ሰው ከመሆን ፣ በሰንበት ፈራሽ ከመሆን ያድንህ!

ቅዳሴያችን መካከል ካህኑ ዕጣን እያጠኑ ዞረው ሲመለሱ የዚህች አጭር ጽሑፍ መነሻ ሃሳብ የሆነውን ይህንን ጸሎት ይጸልያሉ፦ አምላካችን እግዚአብሔር ሆይ አስቀድመህ በባሪያህ በነዌ ልጅ በኢያሱ እጅ የኢያሪኮን ግንብ እንዳፈረስከው የእኔንና የሕዝብህን የኃጢአታችንን ግንብ አፍርሰው፡፡

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ጥቅምት 9 /2012 ዓ.ም.
ቪክቶሪያ አውስትራሊያ

ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን አጥብቃችሁ ስለ እኔ ጸልዩልኝ!
በኮሜንት መስጫው ሥር "ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ [ዋጋን በምድር የሚያስቀር ውዳሴም ሆነ ሌላ] ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ" (ኤፌ 4:29)
+ ከአፍ የሚወጣ እሳት +

"አፌ ይለፈልፋል እንጂ ውስጤ እኮ ንጹሕ ነው"
አለች አባ ፊት ቀርባ - በክፉ ንግግርዋ ብዙ ሰው ያስቀየመች ሴት::

አባ መለሱላት :-
ልክ ነሽ ልጄ እባብም እኮ መርዙን ከተፋ በኁዋላ ውስጡ ንጹሕ ነው!

ምላስ አጥንት የለውም ነገር ግን አጥንት ይሰብራል:: እግዚአብሔር ምላስን እንደጆሮ ክፍት አላደረገም:: በከንፈርና በጥርስ ሸፍኖታል:: ትንሽ አሰብ አድርገን እንድናወራ ነው:: "ሰው ለመናገር የዘገየ ለመስማት የፈጠነ ይሁን" የሚለው ቅዱስ ያዕቆብ ስለ አንደበት ሲናገር "ትንሽ እሳት እንዴት ያለ ትልቅ ጫካ ያቃጥላል" እንዳለ የምላስ ኃይል እጅግ ከባድ ነው:: ከአፍ የሚወጣ እሳት ብዙ ጉዳት ሊያደርስ ይችላል::

ሰው በዱላ ቢደበደብ ታክሞ ቁስሉ ያገግማል:: ክፉ ንግግር የሚያቆስለው ቁስል ግን በቀላሉ አይሽርም:: ዱላ የሚያርፈው ሥጋ ላይ ሲሆን መጥፎ ንግግር ግን ነፍስ ላይ ነው:: ክፉ ንግግሮች ሰውን ለጊዜው ብቻ ሳይሆን ለዘላለም ሊያመርሩት ይችላሉ::

(ሌላ ነገርዋን ትተነው) ሚሼል ኦባማ በአንድ ቃለ መጠይቅ ላይ በጣም ልብ የሚነካ ነገር ስትናገር ሰማሁ:: ስለወረደባት ስድብ ስታስታውስ "አንዳንድ ክፉ ቃላት የነፍስን ቅርፅ ይቀይራሉ" ብላ ነበር::

እውነት ነው በመራር ቃላት የነፍሳቸው ቅርፅ ከተቀየረ ስንቶች ናቸው:: የማይዘነጉት ንግግር እድሜ ልክ የሚያቆስላቸው : የአንድ ሰው ከባድ ስድብ በራስ መተማመናቸውን የነጠቃቸው : የአንድ ሰው "አትችልም" የሚል ድምፅ እጅና እግራቸውን ያሰራቸው እጅግ ብዙ ናቸው:: ሰው ለማሳቅ ተብለው የተሰነዘሩ "ትረባዎች"ና አጥንት ሰባሪ ቀልዶች ቂመኛ ያደረጉዋቸው ሰውን ሁሉ ያስጠሉአቸው ስንት ናቸው? በስድብ ብቻ የፈረሱ ቤቶች አሉ:: ስለተሰደቡ ብቻ በሕዝብ ላይ የሚፈርዱ ዘር እስከማጥፋት የተነሡ አሉ:: ተናጋሪው በጥፋታቸው ውስጥ ትልቅ ድርሻ እና ተጠያቂነት እንዳለው ግን ይዘነጋል::

እግዚአብሔርም "እንደ ዋዛ ለተናገራችሁት ቃል በፍርድ ቀን መልስ ትሠጡበታላችሁ" ብሎአልና ለሰዎች የምንሰነዝረው እያንዳንዱ ቃል ያስጠይቀናል::

በተቃራኒው ለሰዎች ጥሩ ቃል መናገርን ብዙ ዋጋ አንሠጠውም:: ለስድብ የማናቅማማ ሰዎች ለምስጋና ሲሆን ግን እንሽኮረመማለን::
ፊት ለፊት አሳምረን የምንሳደብ ሰዎች ለማመስገን ሲሆን "በፊትህ ማመስገን እንዳይሆንብኝ" እንላለን::

ሆኖም ብናወጣው ሰዎች የሚነገራቸው ጥቂት በጎ ቃል ሰብእናቸውን ይገነባል:: ፈጣሪ "ብርሃን ይሁን" ብሎ በቃሉ እንዳበራው ማድረግ ባይቻልህ እንኩዋን በጥቂት በጎ ቃላት የአንድን ሰው ቀን ማብራት ትችላለህ::
ከምንም ሥጦታ በላይ መልካም የምስጋና ቃላት በሰው ልብ የሚቀር ውድ ሥጦታ ነው::

ባል ለሚስቱ ከሚገዛው ሥጦታ በላይ "ባልዋም ያመሰግናታል" የሚለውን ቃል ቢፈጽምላት ደስታ ይሆንላታል:: ልጆች ከብዙ ሥጦታዎች በላይ ከወላጆቻቸው የሚሰሙት የፍቅር ቃል ይሠራቸዋል::

የእስክንድርያው ፊሎ ለልጅ አባትና እናቱ ከሀገሪቱ ንጉሥና ንግሥት በላይ ናቸው ይላል:: የንጉሥ ቃል የሹመት ቃል ነውና ልጆች በወላጆቻቸው የሚሰሙት "ጎሽ" የሚል ቃል ከፍ ያደርጋቸዋል::

"ልጅሽ ትምህርት የማይገባው ደደብ ስለሆነ ትምህርት ቤት አትላኪው" የሚልን ደብዳቤ "ልጅሽ በጣም ጎበዝ ስለሆነ እሱን ማስተማር ስለማንችል በቤት አስተምሪው" ብላ ያነበበች እናት ትልቅ ሳይንቲስት አፍርታለች::

ብርሃን ይሁን ! ምድር ታብቅል! ብሎ የፈጠረን አምላክ በአርኣያው ፈጥሮናልና በቃላችን የምናሳምም ሳይሆን የምንፈውስ እንሁን::

መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ "ወንድሙን የሚሰድብ ነፍሰ ገዳይ ነው" ብሎአል:: ስድብ ከመግደል እኩል ነው ሲል ነገሩን ለማግነን የተጠቀመው አገላለጽ ሳይሆን በእርግጥም መሳደብ ከመግደል ብዙም ስለማይለይ ነው:: ሀገራችን ላይ ያንዣበበው የዘር ጭፍጨፋ ብዙዎቻችንን ያሳስበናል:: እንደ ሩዋንዳ ልንሆን ነው? እንላለን:: ወዳጄ የሩዋንዳ የዘር ማጥፋት መነሻው እኮ የሚዲያ የጥላቻ ንግግር ነበር:: እውነት ለመናገር ዘር ነክ ስድቦችና በቀልድ መልክ የሚነገሩ የንቀት ንግግሮች ሁሉ የዘር ማጥፋት ዋዜማ ናቸው:: የጥላቻ ንግግር (hate speech) የዘር ማጥፋት እጅግ ወሳኙ መቆስቆሻ ነው:: ስለዚህ "በለው በለው" ብለህ በምትጽፈው comment ወንድሙን ከገደለው እኩል በፈጣሪ ፊት ትጠየቃለህ:: ቅዱሱ እንዲህ ይላል "እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፤ ወንድሙንም ጨርቃም የሚለው ሁሉ የሸንጎ ፍርድ ይገባዋል፤ ደንቆሮ የሚለውም ሁሉ የገሃነመ እሳት ፍርድ ይገባዋል" ማቴ 5:22

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ሰኔ 11 2012 ዓ ም

ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ዘንድ ጸልዩ! ሌሎች እንዲያነቡትም የሚከተሉት አድራሻዎች Like እና Share ያድርጉ
FB: https://www.facebook.com/officialHenokhaile/
Telegram: https://www.tg-me.com/deaconhenokhaile
Instagram: https://www.instagram.com/p/CBnMF0nnhcQ/?igshid=549jvl607bv4
Youtube: https://www.youtube.com/channel/UCOaVsWC05aUjeqIEW3fWj7g
ደመራ የምትሠሩ ሰዎች እባካችሁን ጫፉ ላይ መስቀል አታድርጉ:: መስቀልን መስቀል በማቃጠል አናከብርም::
(ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ)
በዕለተ ምጽአት ጌታችን በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት ከአእላፋት መላእክቱ ጋር ሲመጣ የሚሆነውን ሲናገር :-

"የሰማያትም ኃይላት ይናወጣሉ። በዚያን ጊዜም የሰው ልጅ ምልክት በሰማይ ይታያል፥ በዚያን ጊዜም የምድር ወገኖች ሁሉ ዋይ ዋይ ይላሉ፥ የሰው ልጅንም በኃይልና በብዙ ክብር በሰማይ ደመና ሲመጣ ያዩታል" ብሎአል:: ማቴ. 24:30

የሰው ልጅ የተባለው መድኃኔዓለም ክርስቶስ በብዙ ክብር በሰማይ ደመና ከመምጣቱ በፊት ፣ የምድር ወገኖች ዋይታ ከመሰማቱ በፊት አንድ ነገር ይከሰታል?

"የሰው ልጅ ምልክት በሰማይ ይታያል!"

ይህ የሰው ልጅ ምልክት ምንድር ነው?

"ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው" ተብሎ የተነገረለት ቅዱስ መስቀሉ ነው::

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን የወንጌል ክፍል ሲተረጉም ከጌታችን መምጣት ቀድሞ በሰማይ ስለሚታየው የሰው ልጅ ምልክት (መስቀል) እንዲህ ይላል:-

"መስቀል ከፀሐይ ይልቅ ብሩሕ ይሆናል:: ፀሐይም ትጨልማለች ብርሃንዋንም ትሰውራለች:: ከዚያም በተለምዶ በማትታይበት ሰዓት ትታያለች:: ይህም የአይሁድ ጠማማነት ይቆም ዘንድ ነው" (Homily on Matthew 24)

ጌታችን በምድር ላይ ከተመላለሰ በኋላ ለመጨረሻ ጊዜ የታየው መስቀል ዳግም ሊፈርድ ሲመጣ ግን መስቀሉ ሐዋርያ ሆኖ ቀድሞ በሰማይ ላይ ያበራል::

"መስቀል አብርሓ በከዋክብት አሰርገወ ሰማየ"
"መስቀል በከዋክብት [ዘንድ] አበራ ሰማይንም አስጌጠ" ብሎ ከቅዱስ ያሬድ ጋር መዘመር ያን ጊዜ ነው::

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 17 2015 ዓ.ም. ተጻፈ
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን አጥብቃችሁ ስለ እኔ ጸልዩልኝ!
በኮሜንት መስጫው ሥር "ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ [ዋጋን በምድር የሚያስቀር ውዳሴም ሆነ ሌላ] ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ" (ኤፌ 4:29)
+ የመስቀሉ ደም +

መስቀል ደም አለው ወይ? ከእንጨት የተሠራ ነገር ቢወጉት ይፋፋቅ ይሆናል እንጂ አይደማም::

ስለ ክርስቶስ መስቀል ቅዱስ ጳውሎስ ሲናገር ግን "በመስቀሉ ደም ሰላምን አደረገ" አለ:: (ቆላ. 1:20)
"ወገብረ ሰላመ በደመ መስቀሉ"

የመስቀሉ ደም የሚለው ቃል መስቀሉ ደምቶአል ለማለት አይደለም:: ጌታ የተሰቀለበት መስቀል ጠዋት ሦስት ሰዓት ሊቶስጥራ ላይ ጌታን ሲያሸክሙት የመስቀሉ ቀለም የእንጨት ብቻ ነበረ:: ክርስቶስ መስቀሉን ተሸክሞ ለሦስት ሰዓታት ከወጣና ለሦስት ሰዓት ተሰቅሎ ነፍሱን ከሠጠ በኋላ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ሥጋውን ከመስቀሉ ሲያወርዱት የመስቀሉ መልክ የእንጨት አልነበረም:: በጥሩ ባለሙያ ቀይ ቀለም የተቀባ እስኪመስል ድረስ መስቀሉ በክርስቶስ ደም ታጥቦ ነበር:: እሾህ ከደፋው ራሱ ፣ ከተቸነከሩት እጆቹ ፣ ከተገረፈው ጀርባው ፣ ሚስማር ከያዛቸው እግሮቹ እንደ ውኃ የፈሰሰው ደም በመስቀሉ ላይ ፈስሶ ነበር::

መፍሰስን ለመግለፅ በግእዝ ሁለት ቃላት አሉ "ክዒው" እና "ውኂዝ" የሚሉ:: ወደ አማርኛ ሲመለሱ ሁለቱም መፍሰስ ቢሆኑም ግን ልዩነት አላቸው:: አንድ ሰው በብርጭቆ ውኃ ቢያፈስስ ውኃው ፈሰሰ ይባላል:: የወንዝ ውኃ ሲፈስስም ፈሰሰ ይባላል:: ግእዙ ግን ከአንድ ብርጭቆ ለሚፈስሰው ውኃ "ተክዕወ" ሲል እንደ ወንዝ ላለው ብዙ ፈሳሽ ደግሞ "ውኅዘ" ብሎ ይለየዋል::

ቅዱስ ኤፍሬም ሰማዕታት ስለ ክርስቶስ ብለው አንገታቸው ተሰይፎ እንደሞቱ ሲናገር "ወከዓዉ ደሞሙ በእንተ መንግሥተ ሰማያት" "ስለ መንግሥተ ሰማያት ደማቸውን አፈሰሱ" ይላል::

ይኸው አባት ቅዱስ ኤፍሬም ስለ ክርስቶስ ደም መፍሰስ ሲናገር ግን "በውኂዘ ደሙ ቅዱስ አንጽሖሙ ለመሃይምናን" "በከበረ ደሙ ፈሳሽነት ያመኑትን አነጻቸው" ብሎአል:: የጌታችንን ደም መፍሰስ ለወንዝ ፈሳሽ በሚነገርበት ቃል ውኂዝ የተባለው ከጌታችን የፈሰሰው ደም ከመላው ሰውነቱ ስለነበረ ነው::

መስቀሉን ለዓመታት መፈለግ ፣ ማክበር ግድ የሆነውም መስቀሉ ዓለም በተገዛበት በከበረ ደም ስለተቀደሰ ነው:: (እስመ ተቀደሰ በደመ ክርስቶስ መድኅን)

ወዳጄ ሆይ በደም የታጠበ መስቀል ስታይ ምን ይሰማሃል? በደም የተቀደሰው የመስቀሉ ክብር አይታይህም? አዎ መስቀል ክቡር ነው::

የመስቀሉ ደም ሌላ የሚያሳየው ክብርም አለ:: እርሱም የእኔና የአንተን ክብር ነው:: ምክንያቱም ያ ሁሉ ደም የፈሰሰው ለእኔና ለአንተ ነው:: በሰዎች የመጠሪያ ስምህ ማን ነው? ማን ብለው ሲጠሩህ አቤት ትላለህ?

ቅዱስ ጳውሎስ ግን ለእኔም ለአንተም ስም አውጥቶልናል:: ጳውሎስ አንተን ለሰዎች ሲያስተውቅህ እንዲህ ብሎ ነው :-

"ክርስቶስ የሞተለት ወንድም ነው" 1ቆሮ.8:11
ወዳጄ የአንተ ክብር እዚህ ድረስ ነው:: አንተ ክርስቶስ የሞተልህ ወንድም ነህ:: አንቺ ክርስቶስ የሞተልሽ እኅት ነሽ::

ቅዱስ ጴጥሮስ ጨምሮበታል :-

"በሚያልፍ ነገር በብር ወይም በወርቅ ሳይሆን፥ ነውርና እድፍ እንደ ሌለው እንደ በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ" 1ኛ ጴጥ. 1:18-19 ቅዱስ ያሬድም "አኮ በወርቅ ኃላፊ ዘተሳየጠነ አላ በደሙ ክቡር ቤዘወነ" ብሎ ዘምሮታል::

የእኔና አንተ ዋጋ በወርቅ በብር የሚመዘን አይደለም:: ዋጋችን በመስቀል ላይ የፈሰሰው ክቡር ደም ነው::
ጌታ "መላእክቶቻቸው የአባቴን ፊት ያያሉና ማንንም እንዳትንቁ" ብሎ ነበር:: (ማቴ.18:10) ሰውን ስለ መልአኩ ብለን እንዳንንቅ ከተነገረን ስለፈሰሰለት ደምማ ምንኛ ልናከብረው ይገባን ይሆን?

ውድ ክፍያ ተከፍሎ ልብስ የተገዛለት ልጅ ልብሱን ስለተከፈለበት ዋጋ ሲል ተጠንቅቆ ይለብሰዋል:: በውድ የተገዛ ዕቃ የተሠጠው ሰው በጥንቃቄ ይጠቀምበታል:: የእኛ ሰውነት ግን የተገዛው በአምላካዊ ደም ነው:: እንደተከፈለልን እየኖርን ይሆን?

ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ብሔራዊ ቴአትር ጋር ያለውን ሐውልት እጅግ በውድ ዋጋ አሠርተው ነበር ይባላል:: ንጉሡ የአንበሳ ሐውልት ሊመርቁ ሲከፍቱ ግን ሐውልቱ አንበሳ አይመስልም:: የአንበሳና ቀጭኔ ዲቃላ መስሎ ጉብ ብሎአል:: ንጉሡ አንጀታቸው እያረረ ከመረቁ በኋላ ንግግር ሲያደርጉ "ይህ አንበሳ አንበሳ ባይመስልም የወጣበት ገንዘብ ግን አንበሳ ያደርገዋል" አሉ ይባላል::

የእኛም ሕይወት እንደዚያ ነው:: ስንታይ ምናችንም ክርስቶስን አይመስልም:: አንዳንዴም በክፋት ከሰውነት ተራ እንወርዳለን:: ሆኖም እንዲህ ብንበድልም "ክርስቶስ የሞተልን ነን"
ምንም እንኳን ክርስቲያን ባንመስል የተከፈለልን ደም የክርስቶስ ያደርገናል:: ምንም እንኳን የከበረ ሕይወት ባይኖረንም የፈሰሰልን ክቡር ደም ክቡራን ያደርገናል::

"በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ"
1ኛ ቆሮ.6:19

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 17 2016 ዓ.ም.
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን አጥብቃችሁ ስለ እኔ ጸልዩልኝ!
በኮሜንት መስጫው ሥር "ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ [ዋጋን በምድር የሚያስቀር ውዳሴም ሆነ ሌላ] ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ" (ኤፌ 4:29)
+ መርጦ መወለድ +

ከእገሌ ልወለድ ብሎ መርጦ የተወለደ የለም:: ምረጡ ብንባል ምን ዓይነት ወላጅ እንመርጣለን? ቀድመን የመገምገም ዕድል ቢኖረን ምን ዓይነት ወላጆች እንመርጣለን። መቼም በወላጆቼ ደስተኛ ነኝ የሚል ሰው "እኔ ደግሜም ብወለድ ከአባዬ ከእማዬ ነው መወለድ የምፈልገው" ማለቱ አይቀርም። ግን ደግሞ ዕድሉን ቢያገኝ መቼም ትንሽም ቢሆን የሚያስተካክለው ነገር አይጠፋም። መርጦ መወለድ አይቻልም እንጂ ቢቻል የምንመርጠው ልዩ ምርጫ ይሆናል።

መርጦ የተወለደ ክርስቶስ ብቻ ነው። በምድር ወደሚኖሩት ሁሉ ተመልክቶ መዓዛዋን መርጦ ፣ በቅድስናዋ ውበት ተማርኮ ከእርስዋ ሊወለድ የመረጣት የተመረጠች እናት ድንግል ማርያም ብቻ ናት። የፈጣሪ ምርጫ እንደ ሰው አይደለም። ሰው ፊትን ያያል እርሱ ግን እስከ ልብ ድረስ ዘልቆ ይመለከታል። እንዴት ብትነጻ ፣ እንዴት ብትቀደስ ነው? እስከ ውስጥዋ ዘልቆ አይቶ ከእርስዋ ሊወለድ የመረጣት? ንጉሥ ውበትዋን የወደደላት ፣ ለእናትነት የመረጣት ቅድስት እንዴት የከበረች ናት?
አዎ መርጦ የተወለደ የለም ፣ ክርስቶስ ግን መርጦ ብቻ ሳይሆን ፈጥሮ የተወለደ ነው። መቅደሱን አንጾ የገባባት እርሱ ነው። መርጦ ለተወለደብሽ ለአንቺ በጸጒራችን ቁጥር ምስጋና እናቀርባለን።

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 21 2012 ዓ ም
የግሸንዋን ንግሥት በረከት በመናፈቅ
ሜልበርን አውስትራሊያ
+ ረቢ ወዴት ትኖራለህ? +

ከመጥምቁ ዮሐንስ ተማሪዎች መካከል ሁለቱ "የእግዚአብሔር በግ እነሆ" የሚለውን የመምህራቸውን ስብከት ሰምተው ጌታን ተከተሉት::

"ኢየሱስም ዘወር ብሎ ሲከተሉትም አይቶ፦ ምን ትፈልጋላችሁ? አላቸው። እነርሱም፦ ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ? አሉት፤ መጥታችሁ እዩ፡ አላቸው። መጥተው የሚኖርበትን አዩ፥ በዚያም ቀን በእርሱ ዘንድ ዋሉ፤ አሥር ሰዓት ያህል ነበረ" ዮሐ. 1:37-39

ጌታን ተከትለው የሚኖርበትን ካዩት ደቀ መዛሙርት አንደኛው ስም እንድርያስ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የራሱን ስም በወንጌሉ ላይ እኔ የማይጽፈውና ቤተ ክርስቲያን ግን የራሱን ነገር ሲገልፅ በሚጠቀመው ቋንቋ የምታውቀው ወንጌላዊው ዮሐንስ ነበረ::

"ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ? አሉት፤ መጥታችሁ እዩ፡ አላቸው። መጥተው የሚኖርበትን አዩ" የሚለው ቃል በእርግጥ በጣም አስገራሚ ነው:: የክርስቶስን መኖሪያ ማየት መፈለጋቸው ፈልገው እንዳያጡት አድራሻውን ለማወቅ ካላቸው ጉጉት የተነሣ ነበረ::
ሆኖም ክርስቶስ በምድር ላይ ሲኖር ቋሚ አድራሻ አልነበረውም:: ራሱ እንደተናገረ :-ለቀበሮዎች ጉድጓድ ለሰማይም ወፎች መሳፈሪያ አላቸው፥ ለሰው ልጅ ግን ራሱን የሚያስጠጋበት የለውም" (ማቴ. 8:20)

እነዚህ ሁለት ደቀ መዛሙርት የጠየቁት "ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ?" የሚለው ጥያቄ አድራሻ ከመጠየቅ ከፍ ያለ ጥልቅ ጥያቄ ነው:: ነቢያቱ "የጥበብ ሀገርዋ ወዴት ነው? ማደሪያዋስ ወዴት ነው?" ብለው የተጨነቁለት የጥበብ ክርስቶስ ማደሪያ የት እንደሆነ ማወቅ የነፍስ ዕረፍት ነውና ተራ ጥያቄ አይደለም?
ይህ ጥያቄ ዳዊት ለዓይኖቹ እንቅልፍ ለሽፋሽፍቶቹ ዕረፍት ያልሠጠበት "የያዕቆብ አምላክን ማደሪያ እስኪያገኝ ድረስ" የለመነበት ጥያቄ ነው::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? የሚለው ጥያቄ እንድርያስና ዮሐንስ በአንድ ቀን ብቻ የሚመለስ ጥያቄ መስሎአቸው አብረውት ሔደው አብረውት ዋሉ እንጂ የጌታ መኖሪያ ግን ያን ቀን የዋለበት ብቻ አይደለም::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ?
"ብርሃንህንና እውነትህን ላክ፤ እነርሱ ይምሩኝ፥ ወደ ቅድስናህ ተራራና ወደ ማደሪያህ ይውሰዱኝ" መዝ. 43:3

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? "ወደ ሰማይ ብወጣ፥ አንተ በዚያ ነህ፤ ወደ ሲኦልም ብወርድ፥ በዚያ አለህ። እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ፥ እስከ ባሕር መጨረሻም ብበርር፥ በዚያ እጅህ ትመራኛለች፥ ቀኝህም ትይዘኛለች" መዝ. 139:8 ለአድራሻ የሚያስቸግረው የረቢ መኖሪያው ብዙ ስለሆነ የት ትኖራለህ ለሚለው ጥያቄ መልሱ "መጥታችሁ እዩ" ብቻ ነው::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? ብለው ለጠየቁት ደቀ መዛሙርቱ ቦታውን ከመናገር ይልቅ "መጥታችሁ እዩ" ያለው ጌታ እርሱን ጸንተው እስከተከተሉ ድረስ በሕይወታቸው ዘመን ሁሉ አልፎም ከሞቱ በኋላ የሚያዩት ብዙ መኖሪያ ስላለው ነበር::

የረቢ መኖሪያው ብዙ ነው:: "የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን" እንዳለ ቃሉን የሚጠብቅ ሰው ሰውነትም የእርሱ ማደሪያ ነው:: (ዮሐ. 14:23)

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? " በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፤ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና" ስትል ሰምተንህ ነበር:: (ዮሐ. 14:2) የአንተ መኖሪያ መንግሥተ ሰማያት አይደለምን? ቅዱስ ጳውሎስ "ልሔድ ከክርስቶስ ጋር ልኖር እናፍቃለሁ" ሲል እንደሰማነው እስከ ዐሥር ሰዓት ድረስ እንደመዋል ዐሥሩ መዓርጋት ላይ የደረሱ በጽድቅ መንገድ የሔዱ የሚያዩት ማደሪያህ መንግሥተ ሰማያት አይደለምን? መጥተን ለማየት "እናንተ የአባቴ ቡሩካን ወደ እኔ ኑ" እስክትለን በተስፋ እየጠበቅን አይደለምን?

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? ካሉት ጠያቂዎች መካከል አንዱ ዮሐንስ መሆኑን ሳስብ ደግሞ ዮሐንስ ያያቸው የረቢ መኖሪያዎች ከገሊላ እስከ ታቦር ተራራ ፣ ከሊቶስጥራ እስከ ቀራንዮ ፣ ከወንጌል እስከ ራእይ እጅግ ብዙ እንደነበሩ ታየኝ::

"ወዴት ትኖራለህ?" ብሎ ጠይቆ ጌታን የተከተለው ዮሐንስ "መጥተህ እይ" በተባለው መሠረት የጌታን መኖሪያ የእርሱን ያህል ያየም ሰው የለም::

ዮሐንስ "ረቢ ወዴት ትኖራለህ?" ለሚል ጥያቄው ግን አንጀት የሚያርስ ልብ የሚያሳርፍ መልስ ያገኘው አርብ ዕለት መስቀሉ ሥር ነበር:: ወዴት ትኖራለህ? ላለው ዮሐንስ የዘጠኝ ወር ከተማውን የዘላለም ማረፊያውን "እነኋት እናትህ" ብሎ ሲሠጠው መጥቶ ካያቸው የረቢ መኖሪያዎች ሁሉ የምትበልጠውን መኖሪያ አየ:: "እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፥ ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወድዶአታልና፥ እንዲህ ብሎ፦ ይህች ለዘላለም ማረፊያዬ ናት፤ መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ" ብሎ የመረጣትን ማደሪያ ከማየት በላይ ምን ክብር አለ? (መዝ. 132:13)

ዮሐንስ ይህችን የረቢ መኖሪያ ወዲያው ወደ ቤቱ ወሰዳት:: ዮሴፍ ሊወስዳት ስላልፈራ ምን እንዳገኘ ያውቃልና እርሱም ይህችን የዕንቁ ሳጥን ወደ ቤቱ ወስዶ ቢዝቁት የማያልቅ ጸጋን ተጎናጸፈ::

ጌታ እናቱን ለዮሐንስ መሥጠቱ የሁለት ድንግልናዎች ማስረጃ ሆነ:: የድንግል ማርያም ዘላለማዊ ድንግልናም የዮሐንስ ድንግልናም በጌታ ንግግር ታወቀ::

አንዳንዶች እንደሚመስላቸው ድንግል ማርያም ከጌታ ሌላ ልጆች ቢኖሩአት ኖሮ "እናቴን ከልጆችዋ ነጥለህ ወደ ቤትህ ውሰዳት" "አንቺም ልጆችሽን ይዘሽ ወደ ሰው ቤት ሒጂ" ብሎ ለዮሐንስ አይሠጣትም ነበር:: ድንግል ማርያም የአብን አንድያ ልጅ አንድያ ልጅዋ አድርጋለችና አምላክ ባደረበት ዙፋን ሌላ ፍጡር ያላስቀመጠች የአምላክ ብቸኛ ዙፋን ፣ እግዚአብሔርን አስገብታ በርዋን የዘጋች ዘላለማዊት ድንግል መሆንዋ ለዮሐንስ በመሠጠትዋ ታወቀ:: ዮሐንስም ቤት ንብረት የሌለው መናኝ ባይሆንና ሚስት ድስት ያለው ሰው ቢሆን ድንገት ወደ ቤቱ ይዞአት እንዲሔድ እናቱን ባልሠጠው ነበር::

የሰው ልጅ ድኅነት ታሪክ በሁለት "እነሆ"ዎች መሃል መከናወኑ እጅግ ይደንቃል:: የሰው መዳን የተጀመረው "እነሆኝ የጌታ ባሪያ" ብላ ራስዋን ለፈጣሪ በሠጠችው ድንግል ቃል ሲሆን የተጠናቀቀው ደግሞ "እነኋት እናትህ" ብሎ በደም በታጠበ አንደበቱ በነገረን የኑዛዜ ቃል ነው::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? ለእኛም አታሳየን ይሆን? እስከ ዐሥር ሰዓት መዋል ፣ ዐሠርቱን ትእዛዛትህን ፣ ዐሥሩን የቅድስና ደረጃዎችን መውጣት ላቃተን ለእኛስ መኖሪያህን ታሳየን ይሆን? መጥታችሁ እዩ የሚለውን ጥሪ ሰምተን ለማምጣት አቅም ላነሰን መጻጉዕዎች ፣ ዓይን ላጣን በርጤሜዎሶች ተነሡ እዩ ብለህ መኖሪያህን አታሳየን ይሆን? መቅደስህን እንመለከት ዘንድ ፣ መኖሪያህን መንግሥትህን እናያት ዘንድ ፣ ዮሐንስ ያያትን መኖሪያህ እናትህን እናይ ዘንድ እንመኛለን::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ?

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 21 2016 ዓ.ም.
ለእመብዙኃን ዝክር የተጻፈ

"ንዒ ማርያም ለዕውር ብርሃኑ
ወንዒ ድንግል ለጽሙዕ አንቅዕተ ወይኑ
ኦ ኦ ተኃድግኒኑ ኦ ኦ ትመንንኒኑ
ኀዘነ ልብየ እነግር ለመኑ"
ወተዘከርኒ ለኃጥእ ገብርኪ ተክለ ማርያም
"እግዚአብሔር ብፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን"

ባሕርያት (Elements) ለዚህ ዘመን ክርስቲያን ወጣቶች የተበረከተ እጅግ ውብ የሥነ ጽሑፍ ሥራ ነው:: ይህ ውድ መጽሐፍ አምስት ቅጽ ያላቸው እጅግ የተዋቡ መጻሕፍት ውሕድ ሲሆን በዘመናዊው ዓለም እግዚአብሔርን በመምሰል ሕይወትን እንዴት መለማመድ እንደሚቻል የሚያሳይ በዳያስፖራነት የተወለዱ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ሕይወት የለወጠ እና በብዙ ሺህዎች ኮፒ የተሸጠ መጽሐፍ ነው::

የዚህን መጽሐፍ የመጀመሪያ ቅጽ በእግዚአብሔር ፈቃድ ወደ አማርኛ የተረጎምሁት ሲሆን እስከ ኅዳር ማርያም የአርታኢያንን ዱላ ቀምሶ በኅትመት ቤት አልፎ ከእጃችሁ ይገባል:: የቀሩትም መጻሕፍት በወራት ልዩነት ውስጥ ይከተላሉ::

N.B. የዛሬ ዓመት ገደማ ሊወጣ መንገድ ጀምሮ የነበረው "ሉተርና ሚካኤል" የተሰኘ መጽሐፍ በታላላቅ አባቶቼና ወንድሞቼ በሳል ምክር ምክንያት ከይዘቱ የተነሣ የሚወጣበትን ምቹ ጊዜ እየጠበቀና ተከድኖ እየበሰለ ያለ መሆኑን እገልጻለሁ::

"ነገር ግን በክርስቶስ ሁልጊዜ ድል በመንሣቱ ለሚያዞረን በእኛም በየስፍራው ሁሉ የእውቀቱን ሽታ ለሚገልጥ ለአምላክ ምስጋና ይሁን" 2ኛ ቆሮ. 2:14
+ አባቶቻችን እንዲህ አሉ +

"እሳትና ውኃን ማዋሐድ እንደማይቻል በሌሎች ኃጢአት መፍረድም በራስ ኃጢአት ከመጸጸት ጋር አብሮ አይሔድም" ቅዱስ ዮሐንስ ዘሰዋስው

"የማያማትብ እጅ ቀኙም ግራውም አንድ ነው" አባ ፓስዮስ ዘደብረ አቶስ

"እግዚአብሔር ለኃጢአተኛ ሰው ያለው ፍቅር
ጻድቅ ሰው ለእግዚአብሔር ካለው ፍቅር ይበልጣል"
አባ አርሳኒ

"ሕፃን ልጅ እናቱ ስታጥበው ያለቅሳል:: ሕፃን እምነት (ትንሽ እምነት) ያላቸው ሰዎችም ነፍሳቸውን የሚያጥብ መከራ ሲመጣባቸው እግዚአብሔርን ያማርራሉ" አባ ስምዖን

"ዕለትን የሠጠህ እርሱ ለእለት የሚበቃህንም ይሠጥሃል" ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ

"እጅግ ምርጡ ጸሎት "ጌታ ሆይ አንተ ሁሉን ታውቃለህ የፈቀድከውን አድርግልኝ" ማለት ነው"
ባሕታዊ ቴዎፋን

"ሲያመነዝር ያየኸውን ሰው አንተ ንጹሕ ብትሆንም አትናቀው:: ምክንያቱም አታመንዝር ያለው ጌታ አትፍረድም ብሏል" አባ ቴዎዶር

"አንድ ሰው ኃጢአት ሲሠራ ብታይ እንኳን አትፍረድበት:: አንዳንዴ ዓይንህም ሊሳሳት ይችላል"
ቅዱስ ዮሐንስ ዘሰዋስው

"ለኃጢአተኛው ክንፍህን ዘርጋለት:: ኃጢአቱን ልትሸከምለት ባትችል እንኳን ሸፍንለት"
ቅዱስ ይስሐቅ ሶርያዊ

ከአበው አንዱን ትሕትና ምንድርን ነው? ብለው ጠየቁት:: እርሱም "ትሕትና ማለት ወንድምህ በበደለህ ጊዜ እርሱ ይቅርታ ሳይጠይቅህ በፊት ቀድመህ ይቅር ማለት ነው" አለ::

"ይቅር ካላልክ ገነትም ይቅርብህ" አባ ኤፍሬም አረጋዊ [ If you don’t forgive, forget heaven]

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 22 2013 ዓ ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ዘንድ ጸልዩ! ሌሎች እንዲያነቡትም የሚከተሉት አድራሻዎች Like እና Share ያድርጉ
FB: https://www.facebook.com/officialHenokhaile/
Telegram: https://www.tg-me.com/deaconhenokhaile
Instagram: https://www.instagram.com/p/CBnMF0nnhcQ/?igshid=549jvl607bv4
Youtube: https://www.youtube.com/channel/UCOaVsWC05aUjeqIEW3fWj7g
"ውበት ሐሰት ነው ደም ግባትም ከንቱ ነው:: እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት ግን እርስዋ ትመሰገናለች" ምሳ. 31:30

ቅድስት አርሴማን የምናመሰግናት ለዚህ ነው:: ቅድስት አርሴማ (St. Hripsime) በውበትዋ ምክንያት እስከ ሰማዕትነት ድረስ የደረሰች ቅድስት ናት:: በውበትዋ ከተማረከው ከንጉሥ ዲዮቅልጢያኖስ ሸሽታ ወደ አራራት ተራራ ስትሸሽ የአርማንያው ንጉሥ ድርጣድስ (Drtad) ያሳደዳትና እስከ ሰማዕትነት የበቃችው በሚያልፈው ውበት የማያልፈውን አምላክ ላለማጣት ነበር::

ቅዱስ ጳውሎስ ለዕብራውያን

"ከኃጢአት ጋር እየተጋደላችሁ ገና ደምን እስከ ማፍሰስ ድረስ አልተቃወማችሁም" ያለው ቃል ቅድስት አርሴማን አይመለከትም:: ዕብ. 12:4 እርስዋ ከኃጢአት ጋር ደም እስከማፍሰስ ተጋድላለች::
ውበት ሐሰት ነው ደም ግባትም ከንቱ ነው እግዚአብሔር የምትፈራ አርሴማ ግን ትመሰገናለች::
2025/06/30 08:39:53
Back to Top
HTML Embed Code: