Telegram Web Link
የስምንተኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ "መራቂው" የሚለው ከመድረክ የተቀዳ የበውቄ ወግ አባቴ ስልክ ደረሰ። ያኔ ነው ድምጹን ለመጀመሪያ ጊዜ ያወቅኩት። አባቴ ያኮረፈችው እናቴን ለማባበል በ ውቄ በሣቅ ጫሪ ወጎቹ ሳያውቅ ሸምግሏል። እንግዳ መጥቶ ቡና ተፈልቶ ቡና ቁርሱ የበውቄ "መራቂው" ወግ ነበር።
.
ዘጠነኛ ክፍል ስገባ ደግሞ የምንግዜም አስቂኝ መጽሐፍ ብዬ የምመድበው
"መግባትና መውጣት" እጄ ላይ ገባ። ደጋገምኩት። ድግምት ያስነካኝ እስኪመስል ስከፋም፣ስደሰትም የማነበው፣ እንደ ቡዳ መድኃኒት ከራስጌዬ የማላጣው መጽሐፍ ኾነ። ከሴቶች ስልክ ለመቀበል "መራቂው የሚለውን ወግ ሰምተሻል? እሺ መግባትና መውጣትንስ አንብበሻል?" እያልኩ ስልክ ተቀብያለሁ።
.
ሳላውቀው ያወቅኩትን፣ ሳያውቀኝ የወደድኩትን፣ የሥነ-ጽሑፍን ልዕልና ያሣየኝን ታላቅ ሰው ዛሬ አገኘሁት። አንድ ቀን እንደማገኘው ዐውቅ ነበር፣ የማከብረው፣የምወደው፣ የማደንቀው በ ዕውቀቱ ሥዩም። ሕልም አለኝ አንድ ቀን መድረክ እንደምንጋራ፣ ስለ ሥነ-ጽሑፍም እንደምናወጋ!
.
@huluezih
አያድርገውና??
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
በነቁጥ ዓለም ውስጥ. . .
ኾነን ብንገኝ፣የሁለት ዓለም ሰው፣
ረብ-አልባ ጥያቄ፣ መንፈሷን ወረሰው።
ጠየቀችኝ. . .
እንዲህ አለችኝ. . .
.
"አያድርገውና. . .
ተፈጥሮ ቢጨክን፣ፈጣሪ ቢቆጣ፣
የሰው ዘር 'ሚያጠፋ. . .
ውርጅብኝ ቢመጣ፣
እኔ እና አንተ ብቻ
በዚህች ምድር ብንቀር. . .
ይመስልሃል የምንፋቀር?"
.
ጠላሁ ጥያቄዋን. . .
"አያድርገውና.." ብላ
ምኞቴን መቅጨቷን፤
ማን እውነቴን ነግሮ፣በናደው እውነቷን፣
በበረሃው ዓለሜ ብቻዋን መቅረቷን።
.
@huluezih
@huluezih
https://youtube.com/c/asmamawahmed


እስቲ ገብታችሁ እዩልን...😌
. . .of the day!😎
ይኸው ዓመቱ አለቀ። በቁጥር ስንጠራው አሳንሰን "አንድ" እንለዋለን እንጂ ውስጡ ፈርጀ-ብዙ ስሜቶችን፣ እንባና ሣቆችን፣ ከፍታና ዝቅታ፣ ደስታ እና ሐዘን አቁሯል። ዓመቱ አሻራውን ጥሎብናል፤አሻራችንንም አሳርፈንበት እንሸኘዋለን። ረዥም ነው ጉዞው። መቼም በዚህ ጉዞው ውስጥ የቀሰምነው፣የተማርነው እና የተገነዘብነው ትምህርት ይኖራል። እስቲ የተማርነውን እንካፈል...ለቀጣዩ ጉዞው የአንዳችን ትምህርት ለአንዳችን ይጠቅማልና ምን እንደተማርን ጽፈን እንወያይበት።
እኔ ልጀምር...በዚህ ዓመት የተማርኩት ትልቁ ትምህርት. . .ከራሳችን በቀር ማንም ሊያቆመን እንደማይችል ነው። እስራችን የራሳችን እጅ ነው፣ የጀመርነው ነገር ሁሉ መድረሻ አለው...እኛ እስካልሰነፍን እና ተስፋ እስካልቆረጥን ድረስ። ችግር ሁሉ መፍትሔ አለው፣በተለያየ መንገድ እስከሞከርነው ድረስ። እና የምናየው የምንሰማው ሁሉ አዎንታዊ ከኾነ፣ ፍርሃታችንን ማድመጥ ካቆምን ጥሩ ነገሮች ብቻ ወደ እኛ ይመጣሉ።
.
እናንተስ ምን ተማራችሁ? ሐሳብ እንለዋወጥ።
የዚህ ዓመት የመጨረሻ ፖስት!
.
አመሠግናለሁ!
እወዳችኋለሁ!
አብረን መጥተናል...አብረን እየሔድን ነው። የሕይወትን በለሶች በሥነ-ጽሑፍ እየተጋራን ነው። አስተያየታችሁን ሳትሰስቱ አበርትታችሁኛል። ደግፋችሁኛል። ተቆጥታችሁኛል። የማይረባ ነገር እንዳልጽፍና አክብሮቴን ለማሣየት ብዙ ጽሑፍ ሰርዤያለሁ፣ ደልዤያለሁ። በምንጋራው ስሜቶች በኩል ተቆራኝተናል። አዝነናል፣ሥቀናል፣ቀልደናል፣ ተፈላስፈናል። የሕይወት ታሪኬ አንድ ክፍል ናችሁ። በቀጣይ ዓመት ብዙ ሥራዎች ወደናንተ ይደርሳል። እንዳማረብን በስኬት ላይ ስኬት እንድንደራርብ እመኛለሁ። በአስተያየቶቻችሁ በኩል ብዙዎቻችሁን ዐውቄያለሁ። እንደ ቤተሰብ ናችሁ ለእኔ። በእናንተ ምክንያት ራሴን እንደ ዕድለኛ ስለምቆጥር ደስ ይለኛል።

ምሥጋናዬ ከልብ ነው!!!
.
(#ፈይሠል_አሚን)🙏
መስከረምን እወዳታለሁ 4
.
(በየዓመቱ መስከረም 1 ላይ ብቻ የሚነበበው ታሪክ ክፍል 4 ቀጥሏል)
.
ልክፍት አለብኝ፡፡የማይለቅ የልብ ምች አግኝቶኛል መሰለኝ፡፡ ታዲያ ሰው በጤናው ያለ መስከረም ሴት የሌለ እስኪመስል ይኼን ሁሉ ዓመት ለሷ ይመንናል? ልጅነቴን በሙሉ ቃል አልባ አድናቆት ስችራት እንደ ልጅ ሳልጫወት አፍላነቴ አመለጠኝ፡፡ የትምህርት ዘመኔን እሷን ሳጠና ሰዋሁት፡፡ ደብተሬ ላይ ተጻፈች፣ ብዕሬ በሷ የመልክ፣የአረማመድ፣የአሣሣቅ ቀለም ተቀለመ፡፡ እነሆ ወጣትነቴና መስከረም ፊት ለፊት ተጋፍጠዋል፡፡ በወጣትነቴ ወደ ልጅነት እየመለሰችኝ፤ እንደ እምቦቀቅላ ልጅ ከዓይኔ ሥር ሳጣት እናቱ የሔደች ያህል እየተነፋረቅኩ አለሁ፡፡
.
ለእናንተ እንኳ ታሪኬን ማካፈል ከጀመርኩ አራት ዓመታት ተቆጠሩ፡፡ እነዚህ አራት ዓመታት ለእናንተ ይብዙ እንጂ ለእኔ በፀሐይ መግቢያ እና መውጫ መኻከል እንዳሉት ማለዳ እና ምሽት የተቀራረቡ ናቸው፡፡ ታዲያ ይኼ ‹‹ልክፍት›› ካልተባለ ልክፍት ምን ሊኾን ትርጉሙ? ይኼን ‹‹የልብ ምች›› ብዬ ካልጠራሁት ምን አቻ ሥያሜ ይገኝለታል?
.
በፊት ‹‹ብልሕ፣አርቆ አሳቢ፣ የበሰለ ልጅ፣ አስተዋይ›› የሚለኝ ሁሉ በመስከረም ምክንያት ‹‹ሞኝ፣ ጅል፣ ቂላቂል›› ማለት ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ ስትጠራኝ ‹‹አቤት!›› ስትልከኝ ‹‹ወዴት?›› ስላልኩ ብቻ አድናቆታቸው ወደ ንቀት ተቀይሯል፡፡
.
በርግጥ ሞኝ ኾኜ አይደለም፡፡ መድረሻዋ ላይ ደርሳ መጨረሻዋን እስካላየሁ ድረስ በሷ ተስፋ አልቆርጥም፡፡ የአንድ ዕድለኛ ሰው ኃብት እስካልኾነች ድረስ የእኔ አይደለችም ብዬ አልተዋትም፡፡ ደግሞ ተስፋ እንድቆርጥ እሷም አትፈልግም፡፡ ስርቅ ትከተለኛለች፣ ስደክም የተስፋ ክብሪቷን ጭራ ወደ ነበርኩበት ትመልሰኛለች፡፡
.
መስከረም ምድር ላይ የምፈተንባት ብቸኛዋ ፈተናዬ ሳትኾን አትቀርም፡፡ ዝቅታዬን የእሷን መኖር ዐይቼ እጽናናባታለሁ፡፡ከፍታዬ በእሷ እርግጠኛ ስላልኾንኩ አላጣጥመውም፡፡ የምድር ላይ ግዞቴ ናት፡፡ ወዴትም መንቀሳቀስ አቅቶኛል፤ነፃነቴ ሙሉ አይደለም፡፡
.
እሷን መልዓክ አድርጌ ሳወራላቸው፣ ከአድናቆት በቀር ከአፌ ሲወጣ ባያዩ ‹‹እንዴት ከሰው ጉድፍ ጠፍቶ መልካም ጎኗን ብቻ ትተርካለህ? አይደክምህም ወይ?›› ይሉኛል ወዳጆቼ፡፡ መስከረም እንከን እንዳላት ዐውቃለሁ፡፡ አንድና ብቸኛዋ እንከን ኾኖ ሚታየኝ አባቷ ናቸው፡፡
አባቷ ከወዳደቀ ትራፊ ጭቃ የተፈጠሩ ይመስሉኛል፡፡ ትልቅ ሰው ስለኾኑ እርሳቸውን የሚመጥን ትልቅ ስድብ ያጣሁላቸው የትልቅ ቀላል ናቸው፡፡ ልጃቸውን ለመዳር ሳይኾን ለመሸጥ የሚማስኑ፣ ደስታዋን ሳይኾን ኪሷን ለማደለብ የሚጥሩ ቀላል ሽማግሌ፡፡አባት ለልጁ ዓሣ ማጥመድን ያሣያል እንጂ እንዴት የገነት ባሕር ውስጥ ዓሣ አጥምዶ ማምጣት የሚችል ሰው ይመለምላል?
.
የመስከረም ብቸኛው እንከን ስለመኾናቸው ሥማቸው ብቻውን ምስክር ኾኖ ይቆማል፡፡ ‹‹ጣሰው›› ይባላሉ፡፡ ‹‹መስከረም ጣሰው!›› ሲባል እንከን መኾኑ ዐይታይም? ሥማቸው የእኔን የአፍቃሪነት መብት እንደሚጥሱ አያሣይም? የተፈጥሮን ሕግ ጥሰው የፈካችን መስከረም ጥላሸት እንደሚያከናንቡ አይናገርም? ሥምን መላዕክ ያወጣል ይላል የሐገሬው ሰው…የእርሳቸውን ግን ራሱ የፈጠራቸው አምላክ ያወጣላቸው መኾን አለበት፡፡ ‹‹ሒድና! የዚህን አፍቃሪ ልብ ጣስ!›› ብሎ ሳይፈጥራቸው አይቀርም፡፡
.
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የመስከረም ልብ በአባቷ መርዛማ ምክሮች መጥቆር ጀምሯል፡፡ የነበራት የዋህነት በአባቷ መሰሪነት እየተሸረፈ መንምኗል፡፡ ወደ እናት የሚቀርበው ርህራሄዋ የአውሬነት ቆፈን እየወረረው ነው፡፡ ይታወቀኛል፡፡ቃሏ፣ እንቅስቃሴዋ፣ የከንፈሯ የሽሙጥ ሣቆች ጭካኔን እንደ መዝናኛ እየቆጠረች ስለመኾኑ ምስክር ናቸው፡፡
.
ከትዝታችን ይልቅ ዛሬ በማደርግላት ነገር ትተምነኛለች፡፡ በገዛሁላት ቁስ ልክ አብራኝ ትቆያለች፡፡ መግዛት ካልቻልኩ ‹‹መቆየት አልችልም!›› ብላ ሰበብ ከምራ ትሰለባች፡፡
ዐውቃለሁ፡፡እንደ ዘመኑ ሴት አማራጮቿን ሁሉ እኩል ዕድል እንደምትሠጣቸው፡፡ የተጠጋትን ሁሉ ክፍተት አበጅታ እንደምታስገባቸው፡፡ ደስታ ትልቅ ቦታ፣ትልቅ ኪስና ትልቅ ቤት ውስጥ ብቻ እንዳለ እንደምታስብ ሳትነግረኝ ይገባኛል፡፡ ርዝመቴና ስፋቴ በልቧ ሳይኾን ዙሪያዋ በሚያንዣብቡት መጤዎች መጠን እንደሚታያት ግልጽ ነው፡፡
.
የዛሬ ዓመት የአስተናጋጅነት ሥራዋን እየሠራች ነበር ይኼ ሁሉ የተገለጠልኝ፡፡ ተገልጦልኝ ገሸሽ ማለት አልቻልኩም፡፡ምክንያቱም ‹‹ልክፍቴ›› ናት፤‹‹የልብ ምቼም!!›› ተስተናጋጅ መስሎ የሚመላለሰው ያ ፓይለት አንካሳ ልቧን ሰብሮ፣የማይከርም ተስፋ ሠጥቷት፣ የሌለውን አለኝ ብሎ፣ ያላንቺ ሰው አይታየኝም ብሏት ልቧን ከወረሰው ወዲያ እዚህ ነኝ እዚያ ነኝ ሳይል ተሰወረ፡፡ የኋላ ጉዱን ቆይታ ሰማች፡፡ ልጆቹን በትኖ፣ ፓይለት ሳይኾን ቤት እያከራየ የሚኖር የዚሁ መንደር ሰው ነበር፡፡ እንባዋ ሲፈስ ከረመ፡፡ ያኔ እኔ ብቻ ነበርኩ ከጎኗ፡፡ እንባዋን ማበስ እንኳ ባልችል እንባዋ ሲፈስ ታዘብኩ፡፡ ከዚያ ያ ፓይለት ነኝ ባይ የሥራውን አገኘ፡፡ ፈጣሪ አሳድዶ ያፈሰሰውን እንባ አስከፈለው፡፡ ፈጣሪን አመሥግና እንደ ድሮ ትኾናለች ብዬ ማሰብ ስጀምር የአባቷ መርዝ ተጨምሮበት ያገኘችውን ሁሉ መበቀል ጀመረች፡፡ እኔም የፓይለቱን ግፍ ከፋይ ኾኜ ተሾምኩ፡፡ ያን ግዛልኝ፣ ይኼን አምጣልኝ አበዛች፡፡
.
አሁን ገባኝ፡፡ አዲስ ዓመት ሲመጣ ‹‹መስከረም ጠባ›› የሚባለው፡፡ መስከረም የምትጠባው ኪስ ነው ለካ፡፡
.
ልብ እና ዘመን ለምን እንደማይጣጣም አይገባኝም፡፡ የተሠጠኝ ልብ በዚህ ዘመን ቦታ የለውም፡፡ የማንም መፈንጫ፣ የማንም መቀመጫ ኾኖ ቀረ፡፡ የደግ ዘመን ልብ በክፉዎች መሐል ዛፍ ላይ ኑር ተብሎ እንደተፈረደበት ዓሣ ነው፡፡ ልቤ እስኪሞት በመስከረም ተስፋ አልቆርጥም፡፡ መቼም ይኼን ሁሉ ስቃ ለምታበላኝ መስከረም የደረሰ ጌታ ለእኔ ሲኾን መርጦ ዝም ሚልበት ምክንያት አይኖርም አይደል?
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
@huluezih
@huluezih
. . .of the day!😎
ተዓምር!
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
ራሷን ጥላ ነበር፣
ውስጧን ጠልታ ነበር፣
ከነ አሮጌ ልቧ . . .
ባደፈ አጎበር፤
ተደብቃ ነበር።
.
ይገርማል ለእኔ ግን፣
ይደንቃል ለእኔ ግን፣
የፈጣሪ ጥበብ ለልቧ ሲወግን።
የሷ ዓይነት እንቁ. . .
ከቆሻሻ መሐል. . .
ከእድፎች ክምር. . .
እራሱን ሲጨምር. . .
ለውስጤ ስንቅ ኾነ፣ለዓይኖቼም ተዓምር።
.
የስብዕናዋ ማማ፣
የንፃቷ ካስማ፣
የተፈጥሮ ስካር፣ቀኖና ቢገድፍ፣
ከቆሻሻ ውላ አማረበት እድፍ!!
.
@huluezih
@huluezih
. . .of the day!😎
Audio
‹‹ሣቅሽ እና ነገ››

(#ፈይሠል_አሚን)
.
@huluezih
@huluezih
. . .of the day!😎
የማለዳ ማስታወሻ #142
.
ሩቅ ነኝ። ከቆምኩበት መሬት እንደ ሰማይ የራቅኩ ያክል ይሰማኛል። ከግቤ የተሰደድኩ ያክል እየሸሸሁ፣ ከዓላማዬ የተኳረፍኩ ይመስለኛል። ራሴን የሌለሁበት ቦታ ላይ የምፈልግ፣ አሁን የተገኘሁበት ሥፍራ ላይ እንግዳ የኾንኩ ያክል ባይተዋርነት ይወርረ ኛል። ዓለም የጠበበችኝ አልያም የሰፋችኝ ይመስለኛል። አጥር አልባ ሕይወት ውስጥ፣ ድንበር የለሽ ክበብ ውስጥ ራሴን ደጋግሜ አገኘዋለሁ። ሕጎች ስብዕናዬን የማያከብሩ ያክል ይጨቁኑኛል። የኑሮ ዑደቶች እየዞሩ ወደ ነበርኩበት የውዥቀት ዳስ ውስጥ ይመሉሱኛል። ራሴን እስክጠላው፣ ሰው መኾኔን እንደ መቅሰፍት እስክቆጥር ድረስ እወርዳለሁ። ወድቄ ለመነሣት ስል ደጋግሜ እወድቃለሁ። መሞከር ይደክመኛል። እያንዳንዱ ሙከራዎች ሌላ ህመም የሚፈለፍሉ መንገዶች ኾነው ይሰሙኛል። የትም የለሁም፣ የትም እገኛለሁ። ሁለት ዓይነት መንገዶች በትንሿ መቆሚያዬ ላይ ይታዩኛል። ወዴትም ባልሔድ እንኳ የየትኛውም ጎዳና እሳት ወደ እኔ የተረጨ ያክል ያቃጥለኛል። የቱም የእኔ አይደለም። የእኔ ጉዳይ ያልኾኑ ነበልባሎች ግን ወደ እኔ ከመስፈንጠር አይቦዝኑም። ገፈት ቀማሽ ነኝ።
.
ከዚህ ሁሉ ረመጥ ውስጥ የማይለየኝ አንድ ስሜት ብቻ ተስፋ ይሠጠኛል። የኾነ የማይታየኝ መፍትሔ እንዳለ ውስጤ ይነግረኛል። ከዚህ የእኔ ከማልለው ክበብ ውስጥ እንደምወጣ ይሰማኛል። የኖርኳት እፍኝ የማትሞላ ዕድሜ ሕይወት ላይ እና ታች እንዳላት አስተምራኛለች። ይኼ የሕይወት አንዷ የታች ገጽታ እንጂ የማይናውዝ ቋሚ ምስሏ እንዳልኾነ ይገባኛል። አንድ ቀን "የእኔ" የምለውና የሚመጥነኝ የነፍሴን ሥፍራ አገኘዋለሁ። የገፋኝ ሁሉ በጠመደው ወጥመድ ሊስበኝ ይሞክራል። ትናንቴን ረስቶ የጣለኝ ይሸከመኛል። አሁን ሩቅ ነኝ። ቅርበት ግን ሩቅ እንዳልኾነ ልቤ ይነግረኛል። ጊዜ ከአምላክ በታች ያለ ሌላ አምላክ ነው። የታቹን ወደ ላይ፣ የላዩን ወደ ታች የማድረግ ሥልጣን ተሠጥቶታል። የራቅኩትን ያክል ወደ ራሴ የምቀርብበት ጊዜ ይመጣል። ጊዜ ሁሉን ይለውጣል፣ ራሱ ጊዜም ይለወጣል።
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
@huluezih
@huluezih
ለአዳ'ኝ ሰባሪዎች
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
የድባቴ ገደል ሐዘን እንዲበላኝ፤
የድቅድቅ ጎራዴ፣ ስለት እንዲቀላኝ፤
ጥረው ጡብ አቆሙ. . .
አዋጡልኝ ጠጠር፣
የፍካቴን ዕድሜ፣
ዘመን ለማሳጠር ።
መስበር. . .
ማጨለም፣
ማድቀቅ. . .
ማነከት. . .
ፈገግታ ለውሶ፣ተስፋ ለመፈንከት!
እውነቱ ግን ወዲህ፣
እንቅጩ ግን እንዲህ፣
.
.
.
"ምሬትን ተላምዶ፣የሰው ነፍስ ሲለግም፣
የተሰበረ ልብ አይሠበርም ዳግም!"
.
@huluezih
@huluezih
1
እንቆቅልሽ መፍቻ!
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
ሲዛነፍ ውላችን፣
ያሳለፍነው ጊዜ ጣዕሙ ተረሳ፣
ፀጋ በረከቱ ከእጃችን ተነሣ።
የሉም የነበሩት. . .
ጊዜዬን የገበሩት!
.
አሁን ላይ. . .
ልሙት ወይም ልኑር?
ልውደቅ ወይም ልቁም?
በፍፁም አያውቁም!
.
አልፈርድም በማንም፣
ጊዜ እና ሰው አላምንም!
.
እንቆቅልሽ መፍቻ፣
መች ታደልኩኝ አቅም?
ልሙት? ወይም ልኑር?
እኔ ራሴም አላውቅም።
.
@huluezih
@huluezih
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
"ግመሎች ይሔዳሉ፣ውሾች ይጮኻሉ!"
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
የአጎብዳጅ እውነት. . .
በጩኸት!
የሰርጓጅ እምርታ. . .
በዝምታ!
ግመሎች ይሔዳሉ፣
ውሾች ይጮኻሉ!
ኡኡታም ሲረክስ
በዝንጀሮ ክስ. . .
እስክስ!!!!
ወደ ላይ ሲታገል፣ንፋስን ሲጋፈጥ፣
ወጡን ያባክናል፣ቅመም ለማጣፈጥ!
.
(Inspired by: Ayub Adem)
.
@huluezih
@huluezih
የማለዳ ማስታወሻ #143
.
ሰው ዐይቻለሁ፣ሁሉንም ዓይነት ሰው። ለመልዓክ ከተጠጋ ንፁህ እ ስከ ግብረ-ሰይጣን ድረስ ዐይቻለሁ። ይኼን ሁሉ ዓይነት ሰው ከማየት አንድ ነገር ቀሰምኩ። ጎልተው በአዕምሯችን የሚመጡት፣ ከልሳናችን የማይጠፉት፣ ክፉ ሰዎች ናቸው። ክህደታቸው፣ ውሸታቸው፣ ክፋታቸው፣ ምቀኝነታቸው እና ራስ ወዳድነታቸው ዛሬም ድረስ ስናስበው ቢያልፍም ይጠዘጥዘናል፣ ቁጭት መንፈሳችን ላይ ጠባሳውን ጥሎ ስለሚያልፍ አንረ ሳቸውም። ስለ ጭካኔ፣ ስለ አረመኔነት ሲነሣ ሰርክ ዓይነ-ሕሊናችን ላይ ይውላሉ። ሰዎች ነንና የቱንም ያኽል ይቅርታ አድርገን በምሕረት ብናልፍ እንኳ ከይቅርታ ጋር ከልባችን የሚወነጨፍ የእርግማን ፍላፃ ወደ ሕይወታቸው ይወረወራል።
.
መጥፎ እና አረመኔ ሰዎች ዕድሜያቸው ረዥም ነው። የነኩት የሚበዛ፣ የዳበሱት የሚወዛ መሻታቸውን የሚያገኙ ኾነው እናያለን። ክፋታቸው ወይም መጥፎ ግብራቸው ተረስቶ ሳይኾን ከአወዳደቅ በፊት ለቅጽበት የሚደምቅ አቋቋም ስላለ ነው። ይወፍራሉ፣ ለመገርጠት አንድ ሐሙስ ሲቀራቸው። ያካብታሉ፣ ለመደኽየት እርምጃ ሲቀርባቸው። ደግሞም ይረጋጋሉ፣ ለመተራመስ አንዲት ንጋት እስክትመጣ።
.
ሰዎችን ዐይተናል። ዙሪያችን ያሉ መልዓክትን ግን የረጋ ቦታ አልሠጠናቸውም። በሚነቃነቅ ድልድይ ላይ እጃቸውን የዘረጉልንን፣ በነዲድ በረሃ ውኃ ያ ስጎነጩንን፣ ነገን ለማየት አቅም አንሶን አንጠራርተው የነገን ጀምበር የጠቆሙንን ብዙ አንልላቸውም። ሲያልፍ ካለፈ ቀን ጋራ ባሉበት ጥለን ወደፊት እንጓዛለን። ሰው ነን።
.
ሁሉንም ዓይነት ሰው ስታዩ፣ ሰው መኾንን አትርሱ። በእኛ ሕይወት ውስጥ የሚዘረጋ እጅን ስንፈልግ በሌላው ሕይወት ውስጥ ግን እጅ የሚዘረጋ መልዓክ ነን። የቀረው ይቅር እንጂ ለቅጽበት ሰይጣንን አትኹኑ። ሰዎቹ ይቅር ቢሉን የጊዜ ሚዛን የፍርድ አረሩን ይዞ ያሳድዳችኋል። ሕይወት ቀላል ነው። እንደገና የመጀመር ብዙ ዙሮች ያሏት አጭር ሻማ ናት። መልዓኮቻችንን እያከበርን፣ ከታደልንም መልዓክ እየኾንን ነገን እንጠብቃለን። በእነዚህ አጭር ዙሮች ሊጥሉን የባተሉ ሰይጣናት እንደ ሾላ ሲረግፉ እያየን ጉዟችን ላይ ትንሽ መረማመጃ እናበጃለን። ብሩህ ቀን ከፊታችን እየጠበቀን ለምን በሰይጣን ሰዎች ምክንያት እንቆማለን?
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
@huluezih
@huluezih
2025/07/13 18:45:56
Back to Top
HTML Embed Code: