Telegram Web Link
የጠሉህን ሳትወድድ፣ መከራ ያከበዱብህን ተቀይመህ፣ ስለ አሳዳጆችህ ሳትጸልይ እንዴት ጣቶችህን አመሳቅለህ የመስቀል ምልክት ትሠራለህ? በጣቶችህ ያለው መስቀል ጠላት የተወደደበት፣ ለሰቃልያን በቃል የማይነገር ትዕግስት የታየበት፣ ተሳዳቢ የተመረቀበት፣ ለሚወጉ ምሕረት የተደረገበት የፍቅር አውድማ ነው። ሰውን ለመወንጀል በቀሰርከው ጣትህ እንዴት መልሰህ የይቅርባነት ምልክት የሆነውን መስቀል ለመሥራት ሌላው ጣትህን አግድም ታስተኛለህ?

እያማተብህ አትጥላ፣ እያማተብህ አትፍረድ፣ እያማተብህ አትቀየም፣ እያማተብህ አትርገም።

"ገብረ ሰላመ በደመ መስቀሉ" - "በመስቀሉ ደም ሰላምን አደረገ"

ዲያቆን አቤል ካሳሁን

https://www.tg-me.com/Dnabel

[email protected]
ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ እና ዮሐንስ ዘደማስቆ ሐዋርያው ጴጥሮስ ጌታ በዐረገ በዓመቱ (34 ዓ.ም.) ቅዱሱን እሳት በመቃብሩ ስፍራ ማየቱን ጽፈዋል። ይህ ተአምር አሁን እስካለንበት ዘመን የቀጠለ ሲሆን፣ ሁል ጊዜም በትንሣኤ በዓል ዋዜማ ቅዳሜ ቀን ይታያል። ስለዚህ የሚያስደንቅ ተአምር ብዙ የማያምኑ ሰዎች በራሳቸው መንገድ ለማጣራት ሞክረዋል። እስኪ ከእነዚህ ውስጥ አንዱን ታሪክ ላጫውታችሁ።

በአንድ ወቅት እንዲህ ሆነ…

ዕለቱ ቅዳሜ ጠዋት 4 ሰዓት የትንሣኤ ዋዜማ ነው። የእስራኤል አይሁድ ፖሊሶች እና የከተማዋ ከንቲባ ይህ እሳት ይፈልቅበታል የተባለውን የጌታን መቃብር እውነትነት ማረጋገጥ ስለ ፈለጉ በውስጡ ለእሳቱ መነሣት ምክንያት የሚሆኑ ተቀጣጣይ ነገሮች ካሉ በሚል ለሁለት ሰዓታት ያህል ሦስት ጊዜ ጥብቅ ፍተሻ አደረጉ። ግን ምንም ሊያገኙ አልቻሉም። ቀጥሎም ሁለት መቃብሩን የሚጠብቁ ሙስሊሞችን በማምጣት ልክ የቀድሞዎቹ አይሁድ የጌታን መቃብር እንዳተሙ እነርሱም መቃብሩን ዘግተው በሰም እንዲያትሙት አደረጉ።

ይህንም ተከትሎ በቦታው የነበሩ አረብ ክርስቲያኖች ቱርክ እስራኤልን በተቆጣጠረችበት በ13ኛው ክፍለ ዘመን ከቤተ ክርስቲያን ውጭ በየትኛውም ቦታ ቢሆን እንዳይዘምሩ የተከለከሉትን ቆየት ያለ ዝማሬ በኅብረት ከፍ ባለ ድምፅ መዘመር ጀመሩ። መዝሙሩም:-

“እኛ ክርስቲያኖች ነን። ለብዙ መቶ ክፍለ ዘመናትም ክርስቲያኖች ነበርን። እስከ ዘላለምም እንዲሁ እንሆናለን፣ አሜን!” የሚል ነበር።

እኩለ ቀንም ሲሆን የግሪኩና የአርሜንያው ፓትርያርክ፣ የግብፁ ሜትሮፖሊታንት እንዲሁም ቀሳውስት እና ዲያቆናት ወደ ታተመው የክርስቶስ መቃብር መጡ። ከብዙ ጸሎት እና ምስጋናም በኋላ የታተመው የክርስቶስ መቃብር እንዲከፈት አደረጉ። ፓትርያርኩም ሞጣህቱን ብቻ አስቀርተው ከላይ የለበሱትን ልብሰ ተክህኖ በማውለቅ በክርስቶስ የዕድሜ ቁጥር ልክ ሦስት 33 ያልበሩ ሻማዎችን ይዘው ጨለማ ወደ ነበረው መቃብር ገቡ። ምእመናኑም ከውጭ ሆነው በአንድ ድምፅ ኪርዬሌይሶን (አቤቱ ይቅር በለን) እያሉ በመዘመር ይጠባበቁ ጀመር። ወደ ቅዱሱ መቃብር ገብተው የነበሩትም የግሪኩ ፓትርያርክ ያን በሰው ያልተቀጣጠለ እና የክርሰ‍ቶስን የትንሣኤ ብርሃን የሚያበሥረውን አምላካዊ እሳት ይዘው ብቅ አሉ። ይህን ጊዜ ጎልጎታ በእልልታ ተሞላች የቤተ ክርስቲያኑም ደወል በሐሴት ይደወል ጀመር።

ትንሣኤከ ለእለ አመነ
ብርሃነከ ፈኑ ዲቤነ

እንኳን አደረሰን!!!

https://youtu.be/OGyzCFZO0VY?si=2ptLkHV_WD5rYRvY

ዲያቆን አቤል ካሳሁን
[email protected]
+++የእስክንድር እንቁላሎች+++

ሕፃኑ እስክንድር እክል ካለበት ሰውነት ጋር የተወለደ ሲሆን፣ መለስተኛ የሆነ የአእምሮ ዕድገት ውስንነት ችግርም ነበረበት፡፡ እስክንድር ዕድሜው አሥራ ሁለት ዓመት ይሁን እንጂ በጊዜው ገና የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ነበር፡፡ ካለበት የጤና እክልም የተነሣ መማር ይቸግረው ነበር፡፡ ታስተምረው የነበረች ሴት መምህርቱም በልዩ እንክብካቤ ያለና በእነርሱ የትምህርት ሥርዓት ውስጥ አብሮ መጓዝ እንደማይችል ተረድታዋለች፡፡ ይሁን እንጂ ጥሩ አስተማሪና እውነተኛ ክርስቲያን ስለነበረች ተማሪዋ እስክንድርን በትኩረት ትከታተለው ነበር፡፡ የፀደይ ወቅት በመድረሱ እንዲሁም የፋሲካም በዓል ከፊታቸው እየመጣ ስለሆነ ከእስክንድር ጋር የሚማሩት ሕፃናት ተማሪዎች በተደሰቱበት በአንዱ ቀን እንዲህ ሆነ፡፡

መምህርቷ ለተማሪዎቿ ሁሉ ትላልቅ የፕላስቲክ እንቁላል በመስጠት ‹ይህን የፕላስቲክ እንቁላል ወደ ቤታችሁ ወስዳችሁ ነገ መልሳችሁ እንድታመጡት እፈልጋለሁ፡፡ ነገር ግን ስታመጡ በውስጡ አዲስ ሕይወትን ሊያሳይ የሚችል ነገር ማስቀመጣችሁን እንዳትረሱ› ብላ ነገረቻቸው፡፡

በቀጣዩ ቀን ጠዋት ላይ ሕፃናት ተማሪዎቹ የተሰጣቸውን የፕላስቲክ እንቁላል ይዘው ወደ ትምህርት ቤት መጡ፡፡ እየተሳሳቁ እና እየተጫወቱ በክፍላቸው ውስጥ መምህርታቸው ወዳዘጋጀችው ትልቅ ቅርጫት እንቁላሎቻቸውን ወረወሩ፡፡ ከዚያም እንቁላሎቹ ተከፍተው የሚታዩበት ጊዜ ሲደርስ አስተማሪያቸው አንድ በአንድ ከቅርጫቱ ማውጣት ጀመረች፡፡

የመጀመሪያውን እንቁላል ስትከፍተው በውስጡ አበባ አገኘች፡፡ ለሕፃናቱም “በትክክል፤ በርግጥም አበባ የአዲስ ሕይወት ምልክት ነው!” ስትል ግርምቷን ገለጸች፡፡ የዚህ እንቁላል ባለቤት የሆነችውም ተማሪ እጇን በማውጣት የእርሷ መሆኑን ስትገልጽ “ጥሩ አድርገሻል!” ብላ አመሰገነቻት፡፡ በቀጣይ ያነሣችው እንቁላልም በውስጡ ቢራቢሮ ነበረው፡፡ መምህርቷም እንቁላሉን ወደ ላይ ከፍ በማድረግ “አባ ጨጓሬ መሳዩ (ካተርፒለር) ነገር በመቀየር ወደ ውብ ቢራቢሮነት እንደሚሸጋገር እናውቃለን፡፡ በእውነትም ይህም አዲስ ሕይወት ነው” አለች፡፡

ቀጥላም ሦስተኛውን እንቁላል ከፈተችው፡፡ በውስጡ ግን ምንም የሌለው ባዶ ነበር፡፡ በእርግጠኝነት የእስክንድር እንቁላል መሆኑን አሰበች፡፡ በጊዜው የተናገረችውን ነገር በደንብ ስላልተረዳ ይህን ያደረገ መሰላት፡፡ ልትረብሸውም ስላልፈለገች እንቁላሉን ቀስ ብላ በማስቀመጥ ሌላኛውን ከቅርጫት ሳበች፡፡ ነገር ግን በሁኔታው የተደነቀው እስክንድር በድንገት “መምህርት፣ ስላመጣሁት እንቁላል ምንም አትይም እንዴ?” ሲል ጠየቃት፡፡ መምህርቷም ፊቷ ላይ የመረበሽ ምልክት እየታየባት ‹”እስክንድር፣ ግን እኮ እንቁላልህ ባዶ ነው” አለችው፡፡ እርሱም ዓይን ዓይኗን እያየ ለስለስ ባለ ድምፅ “አዎ መምህርት፤ የክርስቶስ መቃብርም እኮ እንዲሁ ባዶ ነበር” አላት፡፡

አስተማሪዋ የቀሩትን እንቁላሎች ለተማሪዎቹ አሳይታ ስትጨርስ ወደ እስክንድር በመሄድ “ለመሆኑ መቃብሩ ለምን ባዶ እንደሆነ ታውቃለህ?” አለችው፡፡ እርሱም “አዎ፤ ክርስቶስ ተገድሎ በዚያ ውስጥ ተቀብሮ ነበር፡፡ ነገር ግን እርሱ ከሞት ተነሣ፡፡ ታዲያ ይህ ነገር አዲስ ሕይወትን አያሳይምን?” ብሎ መለሰላት፡፡ ያቺም መምህርት በነገሩ ልቧ ተነክቶ ፊቷን ሸፍና አነባች፡፡

ይህም ነገር ከሆነ ከሦስት ወራት በኋላ ተማሪው እስክንድር አረፈ፡፡ የቀብር ሥርዓቱንም ለመከታተል የተሰበሰቡት ሰዎች አንድ እንግዳ ነገር በመቀበሪያው ሳጥኑ ውስጥ ተመለከቱ፡፡ ይኸውም የተከማቹ ሃያ እንቁላሎች ነበሩ፡፡ በክርስቶስ ትንሣኤ ምክንያት ባዶ እንደ ነበረው መቃብር ሃያዎቹ እንቁላሎችም ባዶ ነበሩ፡፡

Source : ‹The Eggs of Alexander› - Orthodox Parables and Stories /ከመለስተኛ ማሻሻያ ጋር

ትርጉም ፡ ዲያቆን አቤል ካሳሁን
[email protected]
በባርነት ስላሉ የእስራኤል ሕዝብ ነጻ መውጣት ሲል ከምቹ ኑሮው የተሰደደ፣ ስለዚያ አመጸኛ ሕዝብ ብዙ ስቃይ የታገሰ፣ መና ከሰማይ ውኃ ከዓለት እንኪፈልቅ ድረስ ወደ አምላኩ የለመነ ሙሴ “ቤዛ” ከተባለ፥ ከእናቷ ማኅፀን ጀምሮ የተሳደደች፣ “ይሁንልኝ” በማለት የማይነገር ጸጋን ሊታሰብ ከማይችል መከራ ጋር የተቀበለች፣ ዓለሙን ሊያድን ከእርሷ የተወለደውን ሕፃን ይዛ ብቻዋን እንደ ወፍ የተንከራተተች፣ ለሰው ሁሉ ሕይወት ሊሆን ከሰማይ ለወረደው ኅብስት የወርቅ ሙዳይ የሆነች ድንግል ማርያምማ ቤዛዊተ ዓለም ብትባል ያንስባት እንደ ሆነ እንጂ አይበዛባትም።


ኦርቶዶክሳዊውን ትምህርት ከክህደት ጋር ማሸማገል አያስፈልግም። ትክክለኛውን የቤተ ክርስቲያን ትርጓሜ በመቃወም ብዙዎች ራሳቸውን የለዩበትን ጥቅስ “አያጣላም” ብሎ ለማቃለል መሞከር ጤናማ ወግ አይደለም።

በሙሴ ወንበር ተቀምጦ የሙሴን ትምህርት አለማስተማር “የተቀመጡበት ወንበር የማን ቢሆን ነው?” ያሰኛል፤ ያስጠረጥራል። እነ አትናቴዎስ በተቀመጡበት ወንበር ተሰይሞ፣ በራሳቸው ላይ የደፉትን አስኬማ ጭኖ የእነርሱ የእነርሱን የማይል ትምህርት ማስተማር ቆንጥጠው የያዙትን ወንበር ጥያቄ ውስጥ ያስገባል። ጥያቄም ብቻ ሳይሆን “አንሰማችሁምም” ያስብላል!

ለካስ “በዕውቀት የሃይማኖትን ቃል ያቀኑ ዘንድ…” የሚለው ቤተ ክርስቲያን ለሊቃነ ጳጳሳት የምታቀርበው ጸሎት ትልቅ ትርጉም አለው!

ዲያቆን አቤል ካሳሁን
[email protected]
+++ ‹ወዴት ነው የምናየው?› +++

ለጌታ ቅዱስ ሥጋ ይሆን ዘንድ ያዘጋጀችውን ሽቱ በመያዝ የጨለማውን ግርማ ሳትፈራ መግደላዊት ማርያም በሌሊት ገስግሳ ወደ መቃብሩ መጥታለች፡፡ አይሁድ ያቆሟቸው ወታደሮች ጥቂት ርኅራኄ ካደረጉላት እንደ ልማዱ የጌታዋን ሥጋ ሽቱ ለመቀባት ትፈልጋለች፡፡ ነገር ግን በቦታው ደርሳ የተመለከተችው ነገር በድንጋጤ ሐሞቷን አፈሰሰው፡፡ ጎመድ የታጠቁ ብርቱዎቹ የመቃብሩ ጠባቂዎች የሉም። አይሁድ በሰንበት በመቃብሩ ያተሙትም ማኅተም ከነመዝጊያ ድንጋዩ ወዲያ ተንከባሏል፡፡ በስፍራው አንዳች መልእክት ያለው ዝምታ ነግሧል፡፡ ይህን ጊዜ መግደላዊት ማርያም ኃዘን ባደቀቀው አቅሟ እየወደቀች እየተነሣች ሐዋርያቱ ወደ ተሰበሰቡበት ቤት ሄደች፡፡ ለስምዖን ጴጥሮስ እና ለዮሐንስም ‹ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም› ስትል እንባ እየተናነቃት ነገረቻቸው፡፡

ይህን የሰሙ ሁለቱ ደቀ መዛሙርትም ወደ ጌታ መቃብር መንገድ ጀመሩ፡፡ አብረውም ሮጡ፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ዮሐንስ በወጣትነት ጉልበት ከፊት ከፊት እየፈጠነ ቀድሞ ከመቃብሩ ደረሰ፡፡ አረጋዊው ቅዱስ ጴጥሮስ ግን ቢሮጥም እንኳን እንደ ዮሐንስ ሊሆን አልቻለም፡፡ በእርግጥ ለክርስቶስ ከነበረው ፍቅር የተነሣ በእርጅና ጉልበቱ ቢሮጥም የሐሙስ ምሽቱ ክፉ ትውስታ (ዶሮ ሳይጮህ መካዱ) ግን ከዕድሜው ጋር ተደምሮ ጥቂት ሳያዘገየው አልቀረም፡፡ ወደ መቃብሩም ቀድሞ የደረሰው ሐዋርያው ዮሐንስ ከመጓጓት ብዛት ራሱን ዝቅ ቢያደርግ የመግነዙን ጨርቅ ተመለከተ፡፡ ወደ ውስጥ እንዳይገባ ግን ‹አክብር ገጸ አረጋዊ› - ‹ሽማግሌውን አክብር› የምትለው ደገኛይቱ ሕግ ከለከለችው፡፡ ዘግይቶ የመጣው ቅዱስ ጴጥሮስ ወደ መቃብሩ ቀድሞ በመግባት በመልክ በመልክ የተቀመጡትን የተልባ እግር ልብሱንና ፣ የራስ ጨርቁን አየ፡፡  ነገር ግን በመጽሐፍ የተጻፈውን የክርስቶስን ትንሣኤ አላመነም ነበርና ማየቱ ከኃዘን በቀር የጨመረለት ነገር የለም፡፡ ለካስ ማወቅ ብቻ ሳይሆን አለማወቅም ትካዜን ይጨምራል?! (ቅዱስ ዮሐንስ ግን በሚያስደንቅ ሁኔታ አይቶ አምኗል። ዮሐ 20፥8)

ሐዋርያቱ ‹አይሁድ የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋ ለማንገላታትና ለማዋረድ ከዚህ አውጥተው ሌላ መቃብር ውስጥ አድርገዉት ይሆናል› የሚል ግምት ቢኖራቸውም፣ ነገር ግን እነርሱን ‹የት አደረጋችሁት?› ብሎ የመጠየቅ ድፍረቱ ስላልነበራቸው አንገታቸውን እንደ ሰበሩ በዝምታ ወደ መጡበት ቤት ተመለሱ፡፡ ማርያም መግደላዊት ግን ከመቃብሩ ውጭ ቆማ የፍቅር እንባን ታፈስ ነበር፡፡

በኋላም ወደ መቃብሩ ውስጥ ዝቅ ብላ ብትመለከት ሁለት ነጫጭ የለበሱ መላእክትን የክርስቶስ ሥጋ ተኝቶ በነበረበት ራስጌና ግርጌ ተቀምጠው አየች፡፡ ቅዱስ ማቴዎስና ቅዱስ ማርቆስ ግን በወንጌላቸው ያናገራትን መልአክ ብቻ በመቁጠር መግደላዊት ማርያም አንድ መልአክ እንደታያት ይጽፋሉ፡፡ ይህችም ሴት ከደረሰባት የኃዘን ጽናት የተነሣ እንዳትሰበር የሚያረጋጉ መላእክት ተላኩላት፡፡ እነዚህም መላእክት ቀድሞ በጥል ዘመን (በኦሪት) እንደ ነበረው የምትገለባበጥ ሰይፍ ይዘው በዓይነ መአት (በቁጣ ዓይን) እያዩ ሳይሆን፣ የደስታ ምልክት የሆነውን ነጭ ልብስ ተጎናጽፈው ደስ በተሰኘ ብሩህ ገጽ ተገለጡላት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ከነፋስ የረቀቁ፣ ሥጋዊ ጉልበት የሌላቸውን መላእክት በመቃብሩ ውስጥ ‹ተቀመጡ› ሲል ይነግረናል፡፡ ይህም አንደኛ መቆም መቀመጥ በሚስማማው ሰው አምሳል መገለጣቸውን የሚያሳይ ሲሆን፤ ሁለተኛ ደግሞ መቀመጥ ዕረፍትን፣ መረጋጋትን እንደሚያሳይ የመቃብር አስፈሪነት ፣የሞትም ጣር እንደ ጠፋ ሲያመለክቱ በመቃብር ውስጥ ተቀምጠው ታዩአት፡፡

ከሁለቱ አንዱም መልአክ ‹አንቺ ሴት ለምን ታለቅሻለሽ?› ሲል ጠየቃት፡፡ ላዘነነ እና ለተጨነቀ ሰው በቀዳሚነት ሸክሙን የሚያቀሉለት በነጻነት ችግሩን እንዲናገር እድል በመስጠት ነውና መልአኩም አላዋቂ መስሎ ጥያቄውን አቀረበላት፡፡ እርሷም ‹ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም› ስትል መለሰችለት፡፡ ከዚህ በኋላ ግን ማርያም መግደላዊት በእነዚያ መላእክት ፊት ላይ የተመለከተችው ነገር እጅግ ትኩረት የሚስብ ነበር፡፡ ልክ ሕፃን ልጅ ገበያ ቆይታ የመጣች እናቱን ሲመለከት በጉጉት እንደሚንሰፈሰፈውና በደስታ የሚሆነውን እንደሚያጣ ፣ መላእክቱም እንደ እናት እንደ አባት የሚመግባቸውን ፣ ዘወትር ‹ሊያዩ የሚመኙትን› የፈጣሪያቸው የኢየሱስ ክርስቶስን ገጽ ባዩ ጊዜ እንደ እነዚያ ሕፃናት ሆኑ፡፡ ገጻቸውን ከእርሷ መለስ አደረጉባት፡፡ ይህን ጊዜ በአንድ አቅጣጫ የተተከለውን የእነርሱን ዓይን ተከትላ ወደ ኋላዋ ብትመለከት ‹ኢየሱስን ቆሞ አየችው›፡፡ ምንም ለጊዜው ባታውቀውም በስሟ ሲጠራት ግን ወዲያውኑ ለይታዋለች፡፡ ከዚህ ሁሉ በፊት ግን መጀመሪያ ክርስቶስን ያየችው የመላእክቱን የእይታ አቅጣጫ ተከትላ ነበር፡፡

እኛስ የእግዚአብሔር ቃል ባለ አደራ የሆንን የወንጌል መልእክተኞች ወዴት ነው የምናየው? ከፊታችን አስቀምጠን ለምናጽናናቸው ምእመናን የዓይናችን አቅጣጭ ወዴት እንዲመለከቱ ይመራቸዋል? አሁን ሕዝብ ሁሉ ጭልጥ ብሎ ወደ ፖለቲካው በመግባት ለሃይማኖቱ ግድ የለሽ ሆኗል፡፡ የእኛን የዓይን አቅጣጫ ተከትለው ይሆን?

በዘመናችን ሰውን ማክበር ፣እግዚአብሔርን መፍራት ብርቅ ሆኗል፡፡ ፍቅር ቀዝቅዞ ጥላቻ ነግሧል፡፡ ግድ የላችሁም ዓይናችን የፍቅር አምላክ የሆነው ክርስቶስን ሳይስት አልቀረም? ምክንያቱም የእኛን የእይታ አቅጣጫ ተከትለው የተመለከቱት ምዕመናን ከጥላቻ እና ይህን ከመሳሰሉት ክፋቶች በቀር ምንም አላተረፉምና? እስኪ አንዳፍታ ቆም ብለን ራሳችንን እንመርምረው? ግን ወዴት ነው የምናየው?

ዲያቆን አቤል ካሳሁን
[email protected]
+++ ቶማስን አድርገኝ +++

ሞት ያጠላበት ነው ኑሮዬ ዘወትር
ገና አልተከበረም ትንሣኤህ እኔ ጋር
ስቃይህን ዘንግቷል ብኩን ኅሊናዬ
ደምህ እንዳልዋጀው ነው ነገረ ሥራዬ
መነሣትህን ያዩ ተነሥቷል ቢሉኝም
እኔ ዓይነ ስውሩ ምንም አላየሁም

ይኸው ነው ሕይወቴ ምንም እንዳላየ
በትንሣኤው ብርሃን እንዳልተጎበኘ

እባክህ ጌታዬ!

ቶማስን አድርገኝ እጆችህን ልዳብስ
አምኜ ለመኖር" የእኔም ተራ ይድረስ
ጣቶቼ ይንኩና የጎን ውግታትህን
ስዘከረው ልኑር ሕማም ትንሣኤህን

ዲያቆን አቤል ካሳሁን
[email protected]
+++‹‹አትፍረዱ አይፈረድባችሁምም›› ሉቃ 6፡37+++

ብዙ ጊዜ ምንም ዓይነት የጥፋተኝነት ስሜት ሳይሰማን ከምንሠራቸው ኃጢአቶች መካከል አንዱ ‹‹በሌሎች ላይ መፍረድ›› ነው፡፡ ደግሞ ነገሩን ከባድ የሚያደርገው የምንፈርድባቸው የወንድሞቻችንን ውድቀት በዓይናችን ማየታችን በጆሯችን መስማታችን ነው፡፡ ያዩትን አይተው፣ የሰሙትን ሰምተው ሲጨርሱ ወዲያው አለመፍረድ እንደ ተራራ የረጋ ትልቅ ሰብዕናን ይፈልጋል፡፡ ትሑት የሆነ ሰው የሌሎች ሰዎችን ድክመት ለማየት የሚገለጥ ዓይን የለውም፡፡ ዘወትር ራሱን እየመረመረ ድክመቶቹን በመቁጠር ላይ ይጠመዳል፡፡ ዓይኖቹም እንደ አሸዋ በበዛው በገዛ ኃጢአቱ ላይ ብቻ ናቸው፡፡ ደግሞ ወደ ሌላው ከተመለከቱ ሊያመሰግኑ እና ሊራሩ እንጂ ሊንቁና ሊፈርዱ አይደለም፡፡

በወንድሞች ላይ መፍረድ የእግዚአብሔር የሆነውን የጌትነቱን ንብረት እንደ መስረቅ፣ በክርስቶስም የፍርድ ዙፋን ላይ ራስን እንደማስቀመጥ ይቆጠራል፡፡ ታዲያ ከዚህ በላይ ድፍረት፣ ከዚህ የሚበልጥ ኃጢአትስ ከየት ይገኛል? አበው ‹ሌሎች ላይ መፍረድ› የትዕቢት ታማኝ ልጅ ሲሆን፣ መጋቢና አሳዳጊውም እርሱው (ትዕቢት) እንደ ሆነ ይናገራሉ፡፡ ራስን መውደድ እና በራስ አስተዋይነት ላይ መደገፍ ሌላው ላይ ጨክኖ ከመፍረድ እንደሚያደርስም ያስተምራሉ፡፡ በርግጥ በሌሎች መፍረድ የሚወድ ሰው ‹‹ክፉ ሲደረግ ተመልክቼ ማለፍ አልችልም!›› እያለ ለከሳሽነቱ ምክንያት ይደረድር ይሆናል፡፡ ይሁን እንጂ በሰዎች ላይ የመፍረድ ኃጢአት ምንጩ የሌሎች ደካማ ምግባር ሳይሆን የተመልካቹ (የፈራጁ) የልብ ክፋት መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ የልብ ቅንነቱ ቢኖርማ በተሳሳተ ወንድሙ ፊት ቆሞ ወይ የራሱን ድክመት እያሰበ የሚያለቅስ፣ አልያም ደግሞ ለወደቀው ወንድሙ እየራራ የሚመክርና የሚጸልይ ይሆን ነበር፡፡

በሌሎች መፍረድና አቃቂር ማውጣት የለመደ ሰው ዓለሙ ሁሉ በእርሱ ፊት ሞኝ ሆኖ ይታየዋል፡፡ ሰው ሁሉ አስተዋይነት በጠፋበት ሰፊ ጎዳና ሲርመሰመስ፣ እርሱ ግን ከፍ ካለው የብስለት ሰገነት ላይ እንደ ቆመ ስለሚሰማው፣ ቁልቁል እያየ የሚሰጠው እርማትና የትዝብት እይታው አይጣል ነው፡፡ ፈራጅ ‹እኔ ተሳስቼ ይሆን?› የሚል ትሑት ሕሊና የለውም፡፡ ልክ በአገጩ ላይ ያለው ሪዝ (ጽሕም) ከመቆሸሹ የተነሣ በፈጠረው መጥፎ ጠረን በሄደበት ሁሉ አፍንጫው ሲረበሽ (መጥፎ ጠረን ሲሸተው) ‹ዓለሙ ሁሉ ሸቷል› እንዳለው ሰው፣ በራሱ ድክመት ምክንያት በተፈጠረበት የእይታ መንሸዋረር ሁሉን ሲተች በሁሉ ሲፈርድ ይኖራል፡፡ የሥነ ልቡና ሳይንሱም እንደሚናገረው አንዳንድ ጊዜ በራስ ውስጥ ያለ የዕውቀት እና የልምድ ክምችት እያነሰ ሲመጣ፣ በሰው ፊት ዝቅ ብሎ ላለመታየት ሲባል በሁሉን ፈራጅና ነቃፊነት መጋረጃ ራሳችንን ልንከልል እንሞክራለን። ይህም አንዱ የሰብዕና መቃወስ (personality disorder) ምልክት ነው።

ቅዱስ አንስታስዮስ ዘሲና ‹‹ማንም ላይ አለመፍረድ››ን በተመለከተ በአንድ ወቅት በገዳሙ ይኖር ስለ ነበረ ደግ መነኩሴ ታሪክ የተናገረውን አንሥተን ጽሑፋችንን እንቋጭ፡፡ ይህም መነኩሴ እርሱ በሚኖርበት ገዳም እንዳሉት ሌሎች መነኮሳት ከፍ ያለ ትጋት አልነበረውም፡፡ ታዲያ የሚሞትበት ቀን ደርሶ በአልጋው ላይ ሳለ ከሞት ፍርሐት ይልቅ በፊቱ ላይ የሚነበበው ታላቅ ደስታ ነበር፡፡ በሁኔታው የተገረሙት በዙሪያው የተቀመጡ መነኮሳትም ‹‹ወንድማችን ሆይ! ሕይወትህን በስንፍና (ትጋት ሳታበዛ) እንዳሳለፍክ እናውቃለን፡፡ አንተስ ይህን ስታውቅ በዚህ በመጨረሻው ሰዓት ስለ ምን ደስተኛ ሆንክ? ምሥጢሩን ልናውቅ አልተቻለንም›› ሲሉ ጠየቁት፡፡ ያም ደግ መነኩሴ ‹‹አዎን! ክቡራን አባቶቼ! ሕይወቴን ሁሉ በስንፍና እና በእንቅልፍ ነው ያሳለፍኩት፡፡ ነገር ግን አሁን በዚህች ሰዓት መላእክት መነኩሴ ከሆንኩበት ጊዜ ጀምሮ የሠራኋቸው ሥራዎች ሁሉ የተመዘገቡበትን አንድ መጽሐፍ አምጥተውልኛል፡፡ ይህንንም መጽሐፍ ስመለከት በማንም ላይ እንዳልፈረድኩ፣ ማንንም እንዳልጠላኹ፣ በማንም እንዳልተቆጣኹ ተረዳኹ፡፡ ስለዚህም ‹አትፍረዱ አይፈረድባችሁምም› የሚለው የጌታዬ ቃል በእኔ ላይ እንደሚፈጸም ተስፋ አደረኩ፡፡ በዚህም ቅጽበት ይህችን ትንሽ ሕግ ስለፈጸምኩ ሌላው ሁሉ የዕዳ ጽሕፈቶቼ ተቀደዱልኝ›› አላቸው፡፡ ይህንንም ከተናገረ በኋላ ነፍሱ ከሥጋው ተለየች፡፡ መነኮሳቱም በምክሩ ተምረው የእግዚአብሔርን ሥራ እያደነቁ በምሥጋና ቀበሩት፡፡

በእውነትም ‹‹አትፍረዱ አይፈረድባችሁም›› የሚለው የመድኃኒታችን ቃል በዚህ ታሪክ ውስጥ ትክክለኛ ትርጉሙን አግኝቷል፡፡ በወንድሞች ድክመት አለመሳለቅና በውድቀታቸው አለመፍረድ ወደ ዘላለማዊው እሳት ከመጣል ያድናል፡፡

+++እግዚአብሔር በሰው ያልፈረዱ ቅዱሳን ካሉበት ገነት በቸርነቱ ያግባን!+++

ዲያቆን አቤል ካሳሁን
[email protected]
+++ የማርያም መንገድ +++

ድሮ በልጅነት ከባልንጀሮች ጋር
በየጎዳናው ላይ ስንበር ስንባረር

አባራሪው ደርሶ መንገዱን ከዘጋ
ከግራና ከቀኝ ማምለጫ ካሳጣ

ተባራሪ ምስኪን መንገድ የጠበበው
በጭንቁ 'ሚጠራት አንዲት ዋስ አለችው

የእርሷን ስም ካነሣ የጠበበ ይሰፋል
የተዘጋው ሁሉ መንገድ ይከፈታል

ቀን በጎደለበት ባገኘው መከራ
በጨነቀው ስዱድ ስሟ የሚጠራ
ማርያም እርሷ ነች ሁሉን 'ምታራራ።


ጭንቅ እና መከራ በተሞላ ዓለም ውስጥ ከክፋ ቀን ሁሉ የምንወጣበትን "የማርያም መንገድ" የሰጠን አምላካችን ስሙ የተመሰገነ ይሁን!

ዲያቆን አቤል ካሳሁን
[email protected]
አዲስ አበባ
ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን
በአማን ተንሥአ!

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሳችሁ፤

ክፍል ስምንት ትምህርታችንን ዛሬ ልክ በኢትዮጵያ አቆጣጠር ከምሽቱ 4:00 ሰዓት ላይ በዚህ https://www.tg-me.com/Dnabel የቴሌግራም ቻናል በlive stream ትምህርቱ ይሰጣል።

እንደ አማራጭ ይህን ከታች የተቀመጠውን ሊንክ በመጠቀም ደግሞ በzoom ልትቀላቀሉን ትችላላችሁ።

https://us05web.zoom.us/j/84709079682?pwd=obn6Rc8YrJjSTaAAeRwKmNbMC2kY8n.1
ያለፈው ክፍል ሰባት ትምህርት በYouTube የተለቀቀ ቢሆንም፣ የዛሬው ጉባኤያችንን ግን የምንጀምረው የክፍል 7ቱን በመከለስ ይሆናል። ትምህርቱን ከtelegram channel በተጨማሪ በYouTube live stream ለማስተላለፍ እንሞክራለን።

እስከዚያው ይህን ቻናል እየተወዳጃችሁ (Subscribe የሚለውን እየጠቃቀሳችሁ) ቆዩን።

https://www.youtube.com/@Dnabelkassahun
አጭር ጥያቄ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የተጠራበት ቀን በቤተ ክርስቲያናችን መቼ ይከበራል?
Live stream started
Live stream finished (1 hour)
የእግዚአብሔር ሰው ሰሎሞን ለአምላኩ ሕንፃ መቅደስን ሊያንጽ በተነሣ ጊዜ ፤ "በጥበብና በማስተዋል በብልሃትም የተሞላ" የናሱን ሠራተኛ ኪራምን ከጢሮስ አስመጥቶ ነበር። ከዚህም ጥበበኛ ጋር ሆኖ እጅግ አስደናቂ የሆነውን መቅደስ በታላቅ ጥንቃቄ አንጿል። በእውነት ይህን ሰሎሞን ያሳነጸውን ውብ መቅደስ ማየት ምንኛ ያጓጓ ይሆን? በእርግጥም መቅደሱንና የመሥዋዕቱን ሥርዓት የተመለከተች ንግሥተ አዜብ ማክዳ "ነፍስ አልቀረላትም" ነበር (1ኛ ነገ 10:5)።

ሆኖም ግን እግዚአብሔር በነቢዩ ኢሳይያስ አድሮ "ሰማይ ዙፋኔ ነው ምድርም የእግሬ መረገጫ ናት፤ ለእኔ ምን ዓይነት ቤት ትሠራላችሁ?" ብሎ መጠየቁ አልቀረም (ኢሳ 66:48)። ለጊዜው በረድኤት የሚያድርበትን መቅደስ ንጉሥ ሰሎሞን ውብ አድርጎ ቢያንጽለትም ፤ በኋላ ግን የሰውን ልጆች ለመቤዠት በአካል የሚያድርበትን ሕያው መቅደስ ማንም ማዘጋጀት አልቻለም ነበር። ስለዚህም "ልዑል የሰው እጅ በሠራችው አይኖርም" ተብሎ ተጻፈ (ሐዋ 7:50)። በመሆኑም መቅደሱን ላነጹ ለሰሎሞን እና ለኪራም ጥበብን የሰጠው ጥበበኛ "ለራሱን ቤት ሊሠራ ፣ሰባት ምሰሶዎችንም ሊያቆም" ፈቃዱ ሆነ። የመቅደሱንም መሠረት እንቁ አደረገ። ቤቱንም እጅግ በከበሩ ድንጊያዎች አነጸ።

ይህች በአምላክ እጅ የታነጸች ፣እግዚአብሔር በረድኤት ሳይሆን በአካል የሚያድርባት ሕያው መቅደሱ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት። የተመሠረተችባቸውም አዕናቁ (እንቁዎች) ቅዱሳን ቤተሰቦቿ ናቸው። የታነጸችበትም የከበሩ ድንጊያዎች ንጽሕና ፣ቅድስና ናቸው።

"ይህች ዓለም አይቶ የማያውቃት በተስፋ ትጠበቅ የነበረችው ድንቅ አማናዊት መቅደስ ለመጀመሪያ ጊዜ በዚህች ምድር ላይ የታየችው በዛሬው ቀን ነበር"

ኪራም ያነጸው የሰሎሞንን መቅደስ መጎብኘት "ነፍስ የማያስቀር" ፣ልብን በሐሴት የሚሞላ ከሆነ ፤ በእግዚአብሔር እጅ የታነጸች ፣የአምላክ ጥበብ የፈሰሰባት እውነተኛ መቅደሱን የእመቤታችንን መወለድ የማየትና የመስማት የደስታ ጥጉ ምን ያህል ይሆን?

እንኳን ደስታን ወደ ዓለም ይዞ ለመጣ ተናፋቂው ለድንግል ማርያም ልደት አደረሳችሁ!!!

ዲያቆን አቤል ካሳሁን
[email protected]
ሰላም ክቡራን፣
እንኳን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም በዓለ ልደት በሰላም አደረሳችሁ። የዛሬው ማታ የትምህርት መርኃግብራችን በሌሎች አገልግሎቶች መደራረብ ምክንያት አይኖረንም። በድጋሚ መልካም በዓል!
2025/06/29 19:06:16
Back to Top
HTML Embed Code: