Telegram Web Link
የኬንያ መንግስት ከትናንት ጀምሮ በጫት ዋጋ ላይ ጭማሪ ማድረጉ ሱማሌያዊያንን አስቆጣ፡፡ የኬንያ የግብርና ሚኒስቴር ዛሬ ባወጣው መግለጫ የጫት ዋጋን ለመወሰን የተቋቋመ ኮሚቴ እንዳለ ጠቅሶ ኮሚቴው ወደውጭ አገር በሚላክ ምርት ላይ ጭማሪ ለማድረግ መወሰኑን አስረድቷል፡፡

ጭማሪው የተደረገውም ምርቱን በተመለከተ መረጃዎችን በማገናዘብ፣ አምራቾች የሚያደርጉትን ወጪ ከግምት ውስጥ በማስገባት እንዲሁም በአቅርቦትና ፍላጎት መካከል ያለውን ልዩነት በማየት እንደሆነ አስታውቋል፡፡

በዚህ መሰረት በአሁኑ ወቅት በኪሎግራም ሰባት መቶ ሽልንግ የነበረው ደረጃ አንድ የሚባለው ጫት አንድ ሺ ሶስት መቶ ብር መግባቱን የገለፀ ሲሆን ሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ከሶስት መቶ ሀምሳ ሽልንግ ወደሰባት መቶ መጨመሩን አስታውቋል፡፡

እንዲሁም አለሌ የሚባለው ደግሞ ከአምስት መቶ ወደአንድ ሺህ መግባቱን ጠቅሶ ከዛሬ ጀምር ይህ ጭማሪ ተግባራዊ እንዲሆን ውሳኔ ማሳለፉን አስረድቷል፡፡ ይህ ይፋ መሆኑን ተከትሎ ሱማሊያዊያን በማህበራዊ ሚዲያዎች በኬንያ መንግስት ላይ ተቃውሞ ሲያሰሙ ውለዋል፡፡ ኬንያ ጫትን ለውጭ ገበያ የምታቀርበው ለሱማሊያ ብቻ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡
በጋምቤላ ክልል በአራት ወረዳዎች በተከሰተ የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት የዘጠኝ ሰዎች ህይወት ማለፉ ተነገረ።

የጋምቤላ ክልል የጤና ቢሮ የህብረተሰብ ጤና ዳይሬክተር አቶ ኝኪዎ ጊሎ ለኢትዮ ኤፍ ኤም እንደተናገሩት፤ለክልሉ አጎራባች በሆነው ደቡብ ሱዳን በሽታው ተከስቶ እንደነበር ተናግረዋል።

በክልሉ ኑዌር ብሔረሰብ ዞን በአኮቦ፣ ዋንቱዋ፣ ማኩዌይ እና ላሬ ወረዳዎች የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት መከሰቱን እና ኮሌራ መሆኑን ለማረጋገጥ ዉጤቱ እየተጠበቀ መሆኑን ነግረዉናል፡፡

በበሽታው ከተያዙት 1መቶ36 ሰዎች መካከል የዘጠኝ ሰዎች ህይወት ሲያልፍ፤31 ሰዎች በህክምና ላይ እንደሚገኙም ነዉ አቶ ኝኪዎ የገለጹት፡፡

96 ሰዎች ደግሞ ከበሽታው ማገገማቸውንም ዳይሬክተሩ ለጣቢያችን ተናግረዋል፡፡

በሽታው በተከሰተባቸው አራቱ ወረዳዎች መድኃኒቶችና የህክምና መገልገያ ቁሳቁሶችን ማድረስ መቻሉንም ነዉ የገለጹት፡፡

አቶ ኝኪዎ በሽታው ወደሌሎች አካባቢዎች እንዳይስፋፋ ሕብረተሰቡ አካባቢውን እንዲያጸዳ እና ንጽህናውን እንዲጠብቅም ተናግረዋል።

ሊዲያ ደሳለኝ
👍1
የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት 54 ዓይነት የካንሰር መድኃኒቶች በ600 ሚሊየን ብር ወጪ በማድረግ ማስገባቱ ተገለፀ

የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት የጤና ተቋማትን ፍላጎት መነሻ በማድረግ 54 ዓይነት የካንሰር መድኃኒት በማቅረብ የማህበረሰቡን ፍላጎት ለማሟላት እየሰራ ይገኛል ሲሉ የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰሎሞን ንጉሴ ለብስራት ሬዲዮ እና ቴሌቭዥን ገልፀዋል።

የካንሰር ህክምና አገልግሎት አሁን ላይ በ31 ጤና ተቋማት ላይ እንደሚሰጥ ገልፀው የፍላጎት መጠን መጨመር ምክንያት በማድረግ አጠቃላይ ፍላጎታቸውን መነሻ በማድረግ 600ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ ትልልቅ ግዢ መፈፀሙን አቶ ሰለሞን ገልፀዋል። እነዚህ መዳኒቶች በአብዛኛው ወደ ሀገር ውስጥ ገብተው ወደ ጤና ተቋማት መሰራጨታቸውን አክለዋል እንዲሁም ከፊሉ መድሀኒት በመግባት ላይ ይገኛሉ ብለዋል። ስለሆነም በክምችት የመገኘት ምጣኔ ከ 80 በመቶ ገዳማ ላይ እንደሚገኝም አክለዋል።

የአቅርቦት መቆራረጥ እንዳይከሰት እንዲሁም የህዝቡ የፍላጎት መጠን መጨመር ጋር ተያይዞ የጤና ሚኒስትር በአንድ ፕሮግራም መልክ በመያዝ የካንሰር መድኃኒት የሚደጎሙበትን አግባብ የሶስትዮሽ ስምምነት በመፍጠር ጤና ተቋማት ከጤና ሚኒስትር እና የመድሀኒት አገልግሎት በመሆን ስምምነት መፈራረማቸውን ግልፀዋል። ስለሆነም በስምምነቱ መድሀኒት በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ የዋጋውን 50 በመቶ ጤና ሚኒስትር ይሸፍናል እንዲሁም መድኃኒቱን ለማጓጓዝ እና የባንክ አገልግሎት እንዲሁም የጉምሩክ እና ሌሎች ክፍያዎችን ወደ 13 በመቶ ገደማ ጤና ሚኒስትር በመሸፈን ለተገልጋዮች ድጎማ ለማድረግ አቅደን እየሰራን ነው ያሉት የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰሎሞን ንጉሴ ለብስራት ሬዲዮ እና ቴሌቭዥን ጨምረው ገልፀዋል።
👍1
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከኤር ባስ ኩባንያ ጋር የጥገና አገልግሎት ስምምነት ተፈራረመ

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከኤር ባስ ኩባንያ ጋር የሰባት አመት የጥገና እና ተያያዥ አገልግሎቶች ስምምነት ተፈራረመ።


ኩባንያው 24 ለሚሆኑ A350 እንዲሁም A350-900 እና A350-1000 ሞዴል ኤር ባስ አውሮፕላኖች የጥገና አገልግሎቶችን እንደሚሰጥ ተነግሯል፡፡

ስምምነቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዓለምን ለማገናኘት ለሚያደርገው ጥረት ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግለት ተጠቁሟል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የኦፕሬሽን ዘርፍ ዋና ሃላፊ አቶ ረታ መላኩ፤ ስምምነቱ አየር መንገዱ የሚሰጠውን አገልግሎት እንዲያሳድግ እና የጥገና አገልግሎት መዘግየትን በማስቀረት በኩል ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል፡፡

የኤር ባስ የአፍሪካ እና መካከለኛው ምስራቅ የደንበኞች አገልግሎት ምክትል ፕሬዚዳንት ላውረን ኔግሬ ተቋማቸው የኢትዮጵያ አየር መንገድ የጥገና አገልግሎትን ለመደገፍ ሃላፊነት በመውሰዱ ከፍተኛ ኩራት እንደሚሰማው ገልጸዋል፡፡

ስምምነቱ በኢትዮጵያ አየር መንገድ እና ኤር ባስ መካከል ያለውን መልካም ግንኙነት ይበልጥ እንደሚያጠናክርም ተነግሯል።
ያለደረሰኝ ሲገበያዩ የተገኙ ከ2,900 በላይ ግለሰቦችና ተቋማት በገንዘብ ተቀጡ!

የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ ያለደረሰኝ የሚደረግ ግብይትን መልክ ለማስያዝ በሚል በጀመረው የቁጥጥር ስራ #ያለደረሰኝ ሲገበያይ ያገኘሁትን 100 ሺህ ብር እቀጣለሁ ባልኩት መሰረት ቅጣቱን ተግባራዊ እያደረግኩ ነው ብሏል፡፡

በዚህ መሰረት በመንፈቅ ጊዜ ውስጥ 3,000 በላይ የንግድ ድርጅቶችና ግለሰቦችን አብዛኞቹን ማለትም 2,970ዎቹን እያንዳንዳቸውን 100,000 ብር በመቅጣት  ከ297 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡንና የተቀሩትን 887ቱን ደግሞ የቃል ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል።

ከአስተዳደራዊ እርምጃው ባሻገር ሌሎች 839 ግለሰቦች ደግሞ ጉዳያቸው በህግ እየታየ መሆኑን የገቢ አሰባሳቢ ቢሮው የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ሰውነት አየለ ተናግረዋል፡፡

በ3 ወራት ጊዜ ውስጥ ሳይከፈል ለረጅም ጊዜ ተከማችቶ ከነበረ 11 ቢሊዮን ብር የግብር እዳ ከ6 ቢሊዮን ብር በላዩን ከፋናንስ ኢንቴሌጀንት አስተዳደር ጋር በመሆን አስከፍለናል ብለዋል፡፡
በመንፈቅ ጊዜ ውስጥ 111 ቢሊዮን ብር ከገቢ ግብር መሰብሰቡን የሚናገረው ቢሮው በጥር ወር ብቻ ከ12 ቢሊዮን ብር በላይ ሰብስቢያለሁ ብሏል፡፡
#ሸገርኤፍኤም
👍3
የኤርትራው ፕረዚዳንት ኢሳያስ አፈወረቂ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል አዲስ ግጭት ለመቀስቀስ እየሰራ ነው ሲል አልጀዚራ በአስተያየት መስጫው ላይ አስነብቧል

የኢሳያስ የ32 አመት የአገዛዝ ዘመን ኤርትራ ነፃነቷን ካወጀች በኋላ የህገመንግስት መዋቅር የላትም ብሏል። ሕገ መንግሥት የለም፣ ፓርላማ የለም፣ሲቪል ሰርቪስ የለም። ኤርትራ ውስጥ ህግ አስፈፃሚ፣ ህግ አውጭ እና ህጋዊ ተርጓሚ አንድ ብቻ ነው፣እሱም ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ብቻ ነው ያላል አስተያየቱ።

በኤርትራ ወታደራዊ አገልግሎትም በግዴታ እና የአገልግሎት ዘመኑ በጊዜ ያልተገደበ ነው።

ወጣት ኤርትራዊያን ከፕሬዚዳንቱ ጦር ለማምጣት እድሜ ልካቸውን በሽሽት ይኖራሉ።
በዚህም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የኤርትራ ወጣቶቾ በተለይ ወንዶች በህገ ወጥ መንገድ ወደ ጎረቤት ሀገራት እና አውሮፓ የሚሰደዱ እና ህይወታቸውን የሚያጠፉ ብዙ ናቸው።

ጦርነት የኤርትራ መንግስት ዋና የገቢ ምንጩ መሆኑን ዘገባው ያትታል። እዚህም እዚያም የሚቀሰቅስ ግጭት፣ አማፂያንን፣ወይም መንግስታትን በመደገፍ ጦርነትን ያባብሳል።

ዛሬ ኢሳያስ እንደገና ሊገመት በሚችል መልኩ አጥፊ በሆኑ እንቅስቃሴዎች ላይ ተጠምዷል።
በኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት እና በህወሓት መካከል የተፈጠረው ጦርነት በፕርቶሪያ ስምምነት ቢቋጭም ኢሳያስ አፈወርቂ በዚህ ስምምነት ደስተኛ አይደለም።

በዚህም በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል ድጋሚ ግጭት እንዲቀሰቀስ እየሰራ ነው፣አሁኑኑ እርምጃ መውሰድ  ይገባል" ይላል አስተያየት ገፁ።
ወንጂ ሸዋ ስኳር ፋብሪካ በተያዘው የበጀት ዓመት አንድ ሚሊዮን ኩንታል ስኳር አምርቶ ለገበያ ለማቅረብ ማቀዱ ተነገረ

ፋብሪካዉ ታሪክ አንድ ሚሊዮን ኩንታል የተመረተው አንዴ ብቻ ሲሆን በወቅቱም የአገዳ መትከያ መሬት ስፋት 12 ሺህ ሄክታር ነበር፤ አሁን አንድ ሚሊዮን ኩንታል ለማምረት ያለው የመሬት ስፋት ዘጠኝ ሺህ ሄክታር መሆኑ ተጠቁሟል ።

ኢፕድ የፋብሪካው ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ጀማል አማን ነገሩኝ ብሎ እንደዘገበው በ2016 ዓም 300 ሺ ኩንታል ስኳር አምርቷል፤ በተያዘው የበጀት ዓመት አንድ ሚሊዮን ኩንታል ስኳር ለማምረት ዝግጅት ተደርጓል።

አሁን ላይ አመራሩ ሰባቱንም ቀን ተከፋፍሎ፣ አገዳ አስገብቶ ስኳር አውጥቶ ነው የሚውለው፤ በእኔ ቀን ፋብሪካው የተሻለ ማምረት አለበት ብሎ እየሰራ ይገኛል ያሉ ሲሆን እስካሁን በቀን ሰባት ሺ ኩንታል ስኳር ይመረታልም መባሉን ከዘገባው ለመረዳት ተችሏል።
👍3
ተራዘመ‼️

የምክክር ኮሚሽኑ የስራ ዘመን ተራዘመ

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 1ኛ አስቸኳይ ስብሰባው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የሶስት ዓመታት የስራ አፈፃፀም ሪፖርት በመመርመር ለኮሚሽኑ የ1 ዓመት ተጨማሪ የስራ ዘመንን አራዝሟል።

በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግ ጉዳዮች ኮሚቴ የኮሚሽኑን የስራ ሂደት ከገመገመ በኋላ ባደረገው ምልከታ ኮሚሸኑ አጠቃላይ ስራውን ማጠናቀቅ እንዲያስችለው የስራ ዘመኑ ለአንድ ዓመት እንዲራዘም ምክረ ሃሳብ አቅርቦ ነበር፡፡

ምክር ቤቱ ኮሚሽኑ ዋና ዋና እና አንኳር ቀሪ ስራዎች መኖራቸውን በማመን የስራ ዘመኑ ለአንድ ዓመት እንዲራዘም በ3 ተቃውሞ በአብላጫ ድምፅ ማፅደቁ ተነግሯል።

አባላቱ ኮሚሽኑ በተሰጠው ተጨማሪ የስራ ዘመን ተጠባቂ ቀሪ ስራዎችን እንዲያጠናቅቅ ሲሉም ጠይቀዋል።

የኮሚሽኑ ማቋቋሚያ አዋጅ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ የኮሚሽኑ የስራ ዘመን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማራዘም እንደሚቻል ይደነግጋል።
👍2
በቅናት የባለቤቱን የግራ ዓይን በቢላ ወግቶ ያፈሠሠው ግለሰብ በእስራት ተቀጣ

የወንጀል ድርጊቱ የተፈፀመው በምስራቅ ቦረና ዞን ጎሮ ዶሎ ወረዳ ውስጥ ነው። የዞኑ ፖሊስ መምሪያ የኮምኒኬሽን ፅህፈት ቤት ኃላፊ ኮማንደር በቃሉ በለጠ ለብስራት ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን እንደተናገሩት ተከሳሽ ዱላና ቴሳ ሮባ የተባለው የ55 ዓመት ግለሰብ በቅናት ተነሳስቶ የስድስት ልጆቹ እናት የሆነችው ባለቤቱን በቢላ የግራ አይኗን ወግቶ ጉዳት እንዳደረሰባት ገልፀዋል።

ተከሳሹ በትዳር ከባለቤቱ ጋር በርካታ አመታትን አብረው ያሳለፉ ሲሆን ታህሳስ 5 ቀን 2017 ዓ.ም ከለሊቱ 6 ሰዐት ተኩል ላይ ከተኛበት ተነስቶ በእንቅልፍ ላይ ያለችውን ባለቤቱ ላይ በቢላዋ የግራ ዓይኗ ላይ ጉዳት በማድረሱ ሙሉ በሙሉ የግራ ዓይኗ እንዲጠፋ ማድረጉን በማስረጃ ተረጋግጧል።  ተከሳሹ በስድስት ልጆቹ እናት እና የትዳር አጋሩ ላይ ይህንን ድርጊት ሊፈፅም የቻለው ባለቤቱን በመጠራጠሩ እና በከፍተኛ የቅናት ስሜት በመነሳሳት መሆኑን ለፖሊስ በሰጠው ቃል ማረጋገጥ ተችሏል።

ፖሊስ የድርጊቱን ፈፃሚ በቁጥጥር ስር በማዋል ተጎጂዋን ወደ ሆስፒታል የላከ ሲሆን በተከሳሹ ላይ አስፈላጊውን የምርመራ መዝገብ በማጣራት ከሆስፒታል ያገኘውን ማስረጃ በማከል የምርመራ መዝገቡን ለአቃቤህግ ልኳል። አቃቤህግም በወንጀል ህግ ቁጥር 555 ንዑስ አንቀፅ 2 ታስቦ እና ታቅዶ የሚፈፀም ከባድ የአካል ጉዳት ማድረስን ወንጀል በመጥቀስ ክስ መስርቷል።

ክሱን ሲከታተል የነበረው የምስራቅ ቦረና ዞን ከፍተኛ ፍረድ ቤት ጥር 28 ቀን 2017 ዓ.ም በዋለው ችሎት ተከሳሽ ዱላና ቴሳ ሮባ በስድስት ዓመት እስራት እንዲቀጣ የተወሰነበት መሆኑን ኮማንደር በቃሉ በለጠ ጨምረው ለብስራት ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ተናግረዋል።

#ዳጉ_ጆርናል
👍21
በአዳማ ከተማ ከ500 በላይ አባውራዎች መኖሪያ ቤታቸው ለልማት ይፈለጋል በሚል በሦስት ቀናት ውስጥ ውጡ መባላቸውን ተናግረዋል ።

አባዎራዎቹ ከስድስት ወር በኋላ ምትክ ቤት እንደሚሠጣቸው እንደተነገራቸውና ኾኖም ቅሬታቸውንና ስጋታቸውን ለከተማ አስተዳደሩ ማቅረባቸውን ገልጸዋል።

ምትክ ሳይሰጠን አንወጣም ያሉ ነዋሪዎች ወደ ከተማ አስተዳደሩ ተጠርተው ከከንቲባው ጋር ውይይት ማድረጋቸውንም ተናግረዋል። የከተማዋ ከንቲባ ኃይሉ ጀልዴ፣ የመንግሥት ቤቶች ያሉባቸውን የድሮ መንደሮች ለማልማት ከኹለት ዓመት በፊት ዕቅድ መውጣቱንና በቀበሌ ቤቶች ለሚኖሩት ባንድ አካባቢ ምትክ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለመገንባትና ቦታውን ለማልማት ከነዋሪዎቹ ጋር ከስምምነት ላይ እንደደረሱ ለዋዜማ ተናግረዋል።

በቦታዎቹ ላይ ትላልቅ የገበያ ማዕከላትን፣ ትምህርት ቤቶችንና ስታዲዬምን ያካተተ ዘመናዊ መንደር እንደሚገነባም ኃይሉ ጠቁመዋል።

ዋዜማ
የኤርትራ የማስታወቂያ ሚኒስትር አቶ የማነ ገብረመስቀል፤ የኢትዮጵያ መንግሥት "ባለፉት ወራት" በአስመራ ላይ "ምክንያት የለሽ እና የተጠናከረ የትንኮሳ ዘመቻ ከፍቷል" በማለት ከሰሱ።

ኢትዮጵያ፤ ቀጣናውን "የከበቡት" ችግሮች "መፍለቂያ እና ማዕከል ናት" ሲሉ የከሰሱት የኢንፎርሜሽን ሚኒስትሩ፤አገራቸው በኢትዮጵያ "የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ የመግባት ፍላጎት" እንደሌላት ገልጸዋል።

የኤርትራ መንግሥት ቃል አቀባይ የሆኑት አቶ የማነ፤ ይህንን ክስ ያቀረቡት ዛሬ ማክሰኞ የካቲት 11/2017 ዓ.ም. በይፋዊ ኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ ነው።
ዩቲዩብ በቁጥር ⵑⵑ

 ዩቲዩብ መሥራት ከጀመረ ሁለት አስርት ዓመታት ደፈነ ።

 ዩቲዩብ እ.ኤ.አ የካቲት 14/2005 ተመሰረተ ፡፡

 ዩቲዩብ መሥራቾች ጃዌድ፣ ቻድ እና ስቲቭ ይባላሉ ።

 የመጀመሪያው ቪድዮ የተለጠፈው የካቲት 23/2005 ነበር። ይህም ቪዲዮ "ሚ አት ዘ ዙ" በሚል ርዕስ ከዩቲዩብ መሥራቾች አንዱ የሆነው ጃዌድ ከዝሆኖች ፊት ቆሞ የተቀረፀው የ19 ሰከንድ ቪድዮ ነው።

 በአሁኑ ጊዜ ዩቲዩብ በዓለም ዙሪያ 2.7 ቢሊዮን ተጠቃሚዎች አሉት ፡፡

 በዓለማችን በርካታ ሰው ዩቲዩብ የሚጠቀምባት ሀገር ሕንድ ስትሆን 476 ሚሊዮን ሰዎች ተጠቃሚዎች ናቸው ፡፡

 ዩቲዩብ በአውሮፓውያኑ 2024 የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ከማስታወቂያ ብቻ 8.1 ቢሊዮን ዶላር ገቢን አስገብቷል።

 'ሚስተር ቢስት' በተባለ የዩቲዩብ ስሙ የሚታወቀው ጂሚ ዶናልድሰን በርካታ አባላት [ሰብስክራይበር] ያለው ዩቲዩበር ነው። ሚስተር ቢስት 363 ሚሊዮን የዩቲዩብ ተከታዮች በመያዝ ቀዳሚው ግለሰብ ሆኗል።

 በዓለማችን ከፌስቡክ ቀጥሎ በርካታ ተጠቃሚዎች ያሉት ዩቲዩብ ሲሆን በየቀኑ ከአንድ ቢሊዮን ሰዓታት በላይ የሚረዝሙ ቪድዮዎች በዚሁ መድረክ ላይ ይታያሉ።

 የዩቲዩብ ደንበኞች ከሆኑት መካከል ከ60 በመቶ በላይ የሚሆኑት ተጠቃሚዎች ሞባይል ስልካቸውን ተጠቅመው ነው ቪዲዮዎችን በዩቲዩብ በኩል የሚመለከቱት።

 በየቀኑ 720 ሺህ ሰዓታት የሚሆኑ የዩቲዩብ ቪዲዮዎች እንደሚጫኑ መረጃዎች ያሳያሉ። እነዚህ ቪዲዮዎች በአማካይ በየቀኑ 5 ቢሊዮን ጊዜ ይታያሉ።

 ዩቲዩብን በአውሮፓውያኑ 2006 ጉግል በ1.65 ቢሊዮን ዶላር የገዛው።

ዩቲዩብ በኢትዮጵያ

 በኢትዮጵያ ከፌስቡክ ቀጥሎ ዩቲዩብ በርካታ ተጠቃሚዎች እንዳሉት ስታትካውንተር የተሰኘው ድረ-ገፅን ያወጣው መረጃ ያሳያል ።

 በአውሮፓውያኑ ጥር 2024 በተሰበሰበ መረጃ በኢትዮጵያ 7 ሚሊዮን ገደማ ሰዎች ማኅበራዊ ሚድያ ይጠቀማሉ።

 በኢትዮጵያ ኢንተርኔት ተጠቃሚ ከሆኑ ሰዎች መካከል 13.5 ገደማ የሚሆኑት ዩቲዩብ እንደሚጠቀሙ ነው ይህ ድረ-ገፅ የሚገልፀው። ይህም ማለት ዩቲዩብ በኢትዮጵያ 1 ሚሊዮን አካባቢ ተጠቃሚዎች እንዳሉት የቢቢሲ መረጃ ያሳያል ።
የካቲት 12 2017

በኮሪደር ልማት ምክንያት ከግል ይዞታቸው ለተነሱ ነዋሪዎች ከ9.5 ቢሊዮን ብር በላይ ካሳ መክፈሉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተናገረ፡፡

የከተማ አስተዳደሩ ምክር ቤት በ4ኛ የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባኤው፣ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ባቀረቡት የ6 ወር ሪፖርት ካነሷቸው ጉዳዮች መካከል በከተማዋ እተከወነ ያለው የኮሪደር ልማት ስራ አንዱ ነው፡፡

ሁለተኛው ዙር ኮሪደር ልማት የሌሎች ሃገራትን ተሞክሮ በመውሰድ በፍጥነት እየተሰራ መሆኑን የጠቀሱት ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ በአጠቃላይ 3ሺህ 515 ሄክታር ቦታን በሚሸፍነው የኮሪደር ልማት ከግል ይዞታቸው ለተነሱ ነዋሪዎች ከ9.5 ቢሊዮን ብር በላይ ካሳ ተከፍሏል፤የቀበሌ ነዋሪዎች ለነበሩት ደግሞ 9 ሺህ ቤቶች ቀርቦላቸዋል ብለዋል፡፡

በተጨማሪም 1402 የመስሪያ ቦታዎችን፣200 የንግድ ሱቆችን  በምትክ መስጠታቸውን ተናግረዋል፡፡

ግንባታውን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ነው ያሉት ከንቲባዋ ተያዘለት ያሉት ጊዜ መቼ እንደሆነ አልጠቀሱም፡፡

ባለፉት 6 ወራት በከተማዋ በተሰበሰበው የገቢ ግብር 111.5 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን በሪፖርፖርታቸው የጠቀሱት ከንቲባዋ የተገነው ገቢ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲመሳከር የ50 በመቶ ብልጫ አለው፤ ይህም ሆነው የታክስ መሰረትን በማስፋትና ህግን ማስከበርን በመቻላችን እንጂ የጨመርነው የታክስ አይነት የለምም  ብለዋል፡፡

ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በተያዘው በ2017ዓ.ም ተከመደበው የ5.4 ቢሊዮን ብር በጀት 71 በመቶውን ለዘላቂ ልማት፣ድህነትን ለመቅረፍና የህዝቡን ኑሮ ለማሻሻል እንደዋለም ጠቁመዋል፡፡

ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የከተማዋ ነዋሪዎችን ለመደገፍ ተጨማሪ 12 ቢሊዮን ብር ተመድቦ ለተማሪዎች ምገባና የምግብ ቁሳቁስ ለሟሟላት፣ ለትራንስፖርትና ለጤና መድህን አገልግሎት  እየዋለ መሆኑንም አንስተዋል፡፡

በሌላ በኩል በኮሪደር ልማቱ ከመኖሪያቸው ለተነሱ የቀበሌ ቤት ነዋሪ ለነበሩ ሰዎች 9 ሺህ ቤት ቀርቦላቸዋል ብለዋል፡፡

ከንቲባዋ በሌላ በኩል ከግል ይዞታቸው ለተነሱት ደግሞ ከ9.5 ቢሊዮን ብር በላይ ካሣ ተከፍሏል ብለዋል፡፡

ለ2017 አመት ከፌዴራል በጀት ለከተማዋ የተደለደለው የድጎማ በጀት ከ5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር እምብዛም የማይበልጥ ሲሆን ባለፉት 6 ወራት ደግሞ 111 ቢሊዮን ብር ገቢ ሰብስቢያለሁ ብሏል፡፡

በተጨማሪም የከተማ አስተዳደሩ የሚያስከፍለው የጣሪያና የግድግዳ ግብር በፍርድ ቤት መሻሩን በመጥቀስ አንድምታው ምንድነው? የሚል ጥያቄም ለከንቲባዋ ቀርቦላቸዋል፡፡

ለግል ባለይዞታዎችም ለልማት ተነሺዎች የሚሰጠው ካሣስ አሁን ካለው የግንባታ ዋጋ ውድነት አንፃር የሚያስገነባ ነው ወይ? የሚሉና ከፍተኛ ወጭ እየጠየቀ ያለው የኮሪደር ልማት በጀት ምንጩ ከየት ነው የሚል ጥያቄም ከምክር ቤቱ አባላት ቀርቧል፡፡

ሌሎችም ጥያቄዎች እየቀረቡ ሲሆን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ምላሽ ይሰጡባቸዋል ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡

ሸገር ራዲዮ
"የታክሲ ሰልፍ ጠብቄ እየሄድኩ ነው"
ወይዘሮ ኬሪያ ኤብራሂም

የቀድሞው የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤ የሆኑት ወይዘሮ ኬሪያ በአሁኑ ወቅት ከቤተሰባቸው ጋር በአዲስ አበባ እንደሚኖሩ ገልፀው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ውስጥ እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ከቪኦኤ ትግርኛ ቋንቋ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ‹‹እኔ ስልጣን ላይ በነበርኩበት ጊዜ አጃቢና ሹፌሮች ነበሩኝ፡፡ አሁን ግን የታክሲ ሰልፍ ጠብቄ እየሄድኩ እገኛለሁ፡፡ ምንም ችግር የለውም፡፡ ህይወት ይቀጥላል›› ብለዋል፡፡

ስልጣን መልቀቅ የህይወት መጨረሻና ሞት ማለት እንዳልሆነም አስረድተዋል፡፡ ‹‹በረሀ ወርደን መስዋእትነት የከፈልነው ለስልጣን ነበር ወይ?›› የሚል ጥያቄ ያነሱት ወይዘሮ ኬርያ ስልጣን መያዝ የመጨረሻ ግብ መሆን እንደሌለበት አሳስበው እሳቸው ግን እንደማንኛውም ሰው በህዝብ ጋር እየኖሩ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

ወይዘሮ ኬርያ ከፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤነታቸው በፈቃዳቸው ከለቀቁ በኋላ በጦርነቱ ወቅት ታስረው የነበረ ሲሆን ከእስር ከተፈቱ በኋላ ከህወሀት መባረራቸው ይታወሳል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የጣራና የግድግዳ ግብርን የመሰብሰብ ስልጣን ያለው መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ አስታወቁ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የጣራና የግድግዳ ግብርን የመሰብሰብ በአዋጅ የተሰጠው ስልጣን ያለው ሲሆን፣ ይህን ግብር ከመሰብሰብ የሚከለክል ምንም አይነት ህጋዊ አካል እንደሌለ ከንቲባ አዳነች አቤቤ አስታውቀዋል።

ይህንን የተናገሩት የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት የ2017 ዓ.ም 4ኛ የስራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባኤውን እየተካሄደ ባለበት ወቅት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ ነው።

ከንቲባዋ የጣራና የግድግዳ ግብርን በተመለከተ የምክር ቤት አባላት ላነሷቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሲሰጡ፣ የጣራና የግድግዳ ግብር አዋጅ በ1968 ዓ.ም የወጣ አዋጅ መሆኑን አስታውሰዋል።

በወቅቱ የነበረው አሰራር አሁንም እንደቀጠለ ነው ያሉት ከንቲባዋ፣ ነገር ግን የተለወጠው ወቅቱን ያገናዘበ የዋጋ ተመን ብቻ ነው ብለዋል።

በተጨማሪም አዋጁ ሲወጣ የነበረው የኪራይ ዋጋ እና አሁን ያለው የኪራይ ዋጋ እኩል ባለመሆኑ አሁን የጨመረው ኪራዩ መሆኑን ጠቁመዋል።

የከተማ አስተዳደሩ የሚያስከፍለው ግብር ግን በትክክለኛ ዋጋው ሳይሆን ለመኖሪያ ቤት የዋጋውን ግማሽ እንዲሁም ለንግድ ቤቶች 75 በመቶ ብቻ እንደሆነ ከንቲባዋ አብራርተዋል።

በከተማዋ በግብር ስርዓት ውስጥ ያልነበሩ በርካታ ነዋሪዎች እንደነበሩ ያስታወሱት ከንቲባ አዳነች፣ በከተማዋ ካሉ 800 ሺህ ህንጻዎችና ቤቶች ግብር ይከፍሉ የነበሩት 120 ሺህ ብቻ እንደነበሩ ገልጸዋል።
Capital newspaper
ሼህ መሀመድ አልአሙዲ እያንሰራሩ ነው

2 ወራት ባልሞላ ጊዜ ከግማሽ ቢሊዮን ዶላር በላይ አገኙ

ኢትዮጵያዊው ቁጥር አንድ ባለሀብት ሼህ መሀመድ አልአሙዲ ሁለት ወራት ባልሞላ ጊዜ ከግማሽ ቢሊዮን ዶላር በላይ አገኙ፡፡ ባለሀብቱ ከሁለት አመት በፊት ያጋጠማቸውን ከፍተኛ ኪሳራ በማካካስ አሁን ወደቀደመው መስመራቸው መግባት መቻላቸውን ቢሊየነርስ አፍሪካ ዘግቧል፡፡ እንደዘገባው ጃንዋሪ 1 ቀን 2025 የአልአሙዲ ሀብት መጠን 8 ነጥብ 73 ቢሊዮን ዶላር ነበር፡፡

አሁን ግን የሀብታቸው መጠን ወደ 9 ነጥብ አራት ቢሊዮን ተመንድጓል፡፡ ይህም ማለት ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ 552 ሚሊዮን ዶላር ማግኘት መቻላቸውን ያሳያል፡፡ ይህ የሀብታቸው መጠን በአለም ላይ 315ተኛው ሀብታም በሚል እንዲቀመጡ ያደረጋቸው ሲሆን አልአሙዲ እዚህ የሀብት መጠን ላይ ሲደርሱም ከብዙ አመታት በኋላ ይህ የመጀመሪያቸው እንደሆነ ዘገባው አስታውቋል፡፡

ለሀብታቸው መጨመር ትልቁን ሚና የተጫወተው በስዊድን የሚገኘው ፕሪም የተሰኘው የነዳጅ ድርጅታቸው ላይ የአክሲዮን ድርሻቸውን ማሳደጋቸው ነው፡፡ በዚህ በስዊድን ትልቁ በሚባለው ነዳጅ ማጣሪያ የነበራቸው አክስዮን 3 ነጥብ 4 ቢሊዮን ዶላር የነበረ ሲሆን በያዝነው አመት ይህን አክሲዮናቸውን ወደ 3 ነጥብ 9 አሳድገውታል፡፡

የአልአሙዲንን የሀብት መጠን በዝርዝር ስንመለከተው ከዚህ ነዳጅ ማጣሪያ በተጨማሪ ስቬንካ ፔትሮሊየም በተባለው ድርጅት ውስጥ አንድ ነጥብ ዜሮ አራት ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ ድርሻ ያላቸው ሲሆን የሚድሮክ ጎልድ ደግሞ 725 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያወጣ ተገልጿል፡፡

እንዲሁም ኦኮቴ ጎልድ አንድ ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ ሲሆን በሚድሮክ ኢንቨስት ስር ደግሞ 185 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣ ሀብት አላቸው፡፡ እንዲሁም በሚድሮክ ስም የተመዘገቡ ሀብቶቻቸው መጠን 237 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኘው ሚድሮክ ኢትዮጵያ ደግሞ ሁለት መቶ ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣ ኢንቨስትመንት አለው፡፡ በተጨማሪም በሳኡዲ አረቢያ የሚገኘው ናፍት የተሰኘው የነዳጅ ማደያቸው 741 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያወጣ ቢሊየነርስ አፍሪካ ዘርዝሯል፡፡

(ዘ-ሐበሻ ፋይናንስ)
👍4
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ100 በላይ ሰራተኞቹ በአንድ ጊዜ በተለያዩ መስሪያ ቤቶች ተቀጥረው ደመወዝ ይከፈላቸው እንደነበር ደርሼባቸዋለሁ አለ
   
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ100 በላይ የሚሆኑ ሰራተኞች “በሁለት እና በሶስት መስሪያ ቤቶች ተቀጥረው” ደመወዝ ሲከፈላቸው እንደነበር የከተማይቱ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናገሩ።

የከተማ አስተዳደሩ እነዚህን ሰራተኞች “ተጠያቂ ማድረጉንም” ከንቲባዋ ገልጸዋል።

አዳነች ይህንን የገለጹት፤ የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት ዛሬ ረቡዕ የካቲት 12፤ 2017 እያካሄደ ባለው መደበኛ ጉባኤ ላይ ባቀረቡት የስድስት ወራት የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ነው።
የደህንነት ደረጃዉ ከቀድሞ ፓስፖርት በ 300 እጥፍ ይበልጣል የተባለው አዲስና ዘመናዊ ፓስፖርት ነገ ይፋ ይሆናል ተባለ

ኢትዮጵያ እጅግ ዘመናዊና ከፍተኛ የደህንነት ደረጃ ያለው አዲስ ፓስፖርት ነገ የካቲት 14፤2017 ዓ.ም. ይፋ ታደርጋለች። አዲሱ ፓስፖርት የግለሰቡን ባዮግራፊክ መረጃ ብቻ ሳይሆን የጣት አሻራውንም የያዘ የኤሌክትሮኒክስ ቺፕስ ይዟል ተብሏል።

የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ጎሳ ደምሴ እንደገለጹት፣ አዲሱ ፓስፖርት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚመረት ሲሆን፣ የደህንነት ደረጃው ከቀድሞው ፓስፖርት በ300 እጥፍ ይበልጣል።

በተጨማሪም፣ የቪዛ ገጾቹ ኢትዮጵያን የሚገልጹ ባህላዊ፣ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ መገለጫዎችን እንደያዙም መናገራቸውን ኤኤምኤን ዘግቧል።

ከዚህ ቀደም የነበረው ፓስፖርት ዲዛይን በውጭ ሀገር የግል ተቋም እጅ የነበረ ሲሆን አዲሱ ፓስፖርት ግን ሙሉ በሙሉ ዲዛይኑ የኢትዮጵያ መንግስት ነዉ ተብሏል።

አዲሱ ፓስፖርት በሀገር ውስጥ ተመርቶ በዶላር ከመግዛት በዶላር ወደ መሸጥ የሚያሸጋግር መሆኑንም ከዘገባው ለመረዳት ተችሏል። #Capital newspaper
👍3👎1
የመንግስት ቤቶች የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ስራ ባለመጠናቀቁ ቤቶቹ በህገወጥ መልኩ ወደ ግለሰቦች እየዞሩ ይገኛል ተባለ

የአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ
የመንግስት ቤቶች የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ስራ አለመጠናቀቁ ቤቶችን በህገወጥ መልኩ ወደግለሰቦች እንዲዞሩ በር እየከፈተ እንደሚገኝ አስታውቋል።

የአከራይ ተከራይ ውል ምዝገባ ሙሉ በሙሉ
ባለመጠናቀቁና አዳዲስ ውል ምዝገባዎች መረጃ እየተለዩና እየተደራጁ ባለመሆኑ ስራዎችን በተቋሙ የመረጃ ቋት ላይ ለመጫን ክፍተት እየፈጠረ እንደሚገኝ ቢሮዉ ገልጿል።

ለካፒታል የደረሰዉ መረጃ እንደሚያመላክተዉ አሁን ላይ ከ150 ሺህ በላይ የመንግስት መኖርያና የንግድ ቤቶች መረጃ በለማው ቴክኖሎጂ ወደ መረጃ ቋት ማስገባት እንደተቻለ እና ከነዚህ ውስጥ 93 ሺህ 350 የሚሆኑ ቤቶች የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ እንደተሰራላቸው ተጠቁሟል።

የተቋሙ የ 6 ወር ሪፖርት እንደሚያሳየዉ እስከአሁን ባለው ጊዜ ከ 495 ሺህ 745 በላይ ቤቶችን የአከራይ ተከራይ ውል ምዝገባ ተከናዉኗል። Capital
2025/07/14 00:37:07
Back to Top
HTML Embed Code: