Telegram Web Link
"በስመ #አብ_ወወልድ_ወመንፈስ_ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

 #ጥቅምት ፳፱ (29) ቀን እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ_ኤርትራ_አገር የሚገኘውን #ገዳመ_ደብረ_ኣንገብ ለመሰረቱት እንደ ሙሽራው #ቅዱስ_ገብረ_ክርስቶስ መናኔ መንግሥት ወብእሲት ለሆኑት ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ዕንቈ_ብርሃን ለዕረፍታቸው እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።

#የአቡነ_ዕንቈ_ብርሃንን፦ ገድላቸውን በሰፊው ማግኘት ባንችልም ከኤርትራ አባቶች ያገኘነው ማስታወሻ እንደሚናገረው ጻድቁ የንጉሥ ልጅ ናቸው። የአባታቸውን ንግሥና ንቀው ዓለምን ከነግሳንግሷ እንደትቢያ ቆጥረው በመተው በረኀብ በጥም በጾም በጸሎት በታላቅ ተጋድሎ መኖርን ስለመረጡ እንደሙሽራው ገብረ ክርስቶስ መናኔ መንግሥት ወብእሲት ናቸው።

አቡነ ዕንቈ ብርሃን በምንኩስና #እግዚአብሔርን ለማገልገል ከአባታቸው ቤተ መንሥት ወጥተው ወደ ሰሜን ኢትዮጵያ ሔደው ገዳም ገብተው ትምህርተ ሃይማኖትን ተማሩ። በገዳም ውስጥ አባቶችን በጉልበት ሥራ እያገለገሉ በትምህርታቸውም ብሉይንና ሐዲስን እንዲሁም የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ሁሉ አጠናቀው ተማሩ። ከዚኸም በኋላ የገዳሙ አበ ምኔት አባታችንን "ስምህ ማን ይባላል? ሲሏቸው አባታችንም ስማቸው ዕንቈ ብርሃን እንደሚባል ነገሯቸው። አበ ምኔቱም "በእኛ ዘንድ እንደ ደማቅ ብርሃን ደምቀህ አብርተሃልና ከዚኽም በኋላ እንደ ድሮው ስምህ ዕንቈ ብርሃን ይባል፣ አማን በአማን ዕንቈ ብርሃን ነህ" አሏቸው። አቡነ ዕንቈ ብርሃን ከመነኰሱ በኋላ በገድል ላይ ገድል በመጨመር በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ። እርሳቸውም በነበሩበት አካባቢ በጣዖት አምልኮ ውስጥ የነበሩትን ብዙ ሰዎች የከበረች ወንጌልን አስተምረው #ክርስቶስን ወደማመን መለሷቸው።

ከዚኽም በኋላ አቡነ ዕንቈ ብርሃን በ16ኛው መ.ክ.ዘ ወደ ኤርትራ በመምጣት ልዩ ስሙ "ደብረ ኣንገብ ደቂ ሻሓይ" በሚባል ቦታ ተቀመጡ፣ ይኸም ቦታ ከአስመራ 30 ኪሜ ርቀት ላይ በምዕራብ ዞን ጋሽ ባርካ በንዑስ ዞን ሎጎ ዓንሰባ ላይ ይገኛል። አቡነ ዕንቈ ብርሃን በዚኸ ቦታ ላይ ብዙዎች ቅዱሳንን አስተምረው ከብቃት ደረጃ ያደረሱና በምንኲስና በርካታ ቅዱሳን የወለዱ አንጋፋ አባት ናቸው። ከልጆቻቸውም ውስጥ የፀዓዳ ዓምባው ታላቁ ጻድቅ አቡነ ሰይፈ ሚካኤል አንዱ ናቸው።

ጻድቁ በገዳማቸው በደብረ ኣንገብ ውስጥ በርካታ ተኣምራትን በማድረግ የሚታወቁ ሲሆን ምድርን ባርከው ያፈለቁት ፈዋሽ ጠበል በርካታ ሕሙማንን እየፈወሰ ይገኛል። ዳግመኛም ለሰውም ለእንስሳትም የሚሆን ውኃን አፈለቁ።

የአቡነ ዕንቈ ብርሃን የዕረፍታቸው ጊዜ ሲደርስ #ጌታችን_መድኀኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከእልፍ አእላፍ ቅዱሳን መላእክቱ ጋር ተገለጠላቸውና "ስምህን የጠሩትን፣ ዝክርህን የዘከሩትን ደብርህን ያነጹትን፣ ገድልህን የጻፉትንና ያነበቡትን የሰሙትን ሁሉንም እምርልሃለሁ" የሚል ታላቅ የምሕረት ቃልኪዳን ገባላቸው። ከዚኽም በኋላ የጸሎት በኣታቸው ተከፈተችና አባታችንም እዚያው ሲያርፉ ከሰማይ ብርሃን ወረደላቸው፤ ወዲያውም በኣታቸው እንደቀድሞው ተዘጋች።

ከአቡነ ዕንቈ ብርሃን ዕረፍት በኋላም ገዳማቸው ለብዙ ባሕታውያን መኖሪያ ሆነ። እንዲሁም በግራኝ አህመድ የ15 ዓመት የመከራ ዘመን ወቅትም ለ79 ታቦታትና ለበርካታ ቅዱሳት መጻሕፍት መሠወሪያ (መሽሽጊያ) ቦታ ሆኖ አገልግሏል። የመከራውም ዘመን ካለፈ በኋላ ታቦታቱ ወጥተው ለተለያዩ ገዳማትና አድባራት ተሰጡ። አሁን ላይ ግን በዚህ ታሪካዊ ገዳም ውስጥ የሚኖሩት መነኰሳት ጥቂት ከመሆናቸውም በላይ ገዳሙ እየተዳከመ ስለሆነ መነኰሳቱ የገዳሙን ክብር ለመጠበቅ ብዙ እየደከሙ ይገኛሉ። የአቡነ ዕንቈ ብርሃን የዕረፍታቸው መታሰቢያ በዓል ጥቅምት 29 ቀን በገዳማቸው ደብረ ኣንገብ በታላቅ ድምቀት ይከበራል። #ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን ለዘላለሙ አሜን!!!


ምንጭ፦ በእንተ ኅሩይ ቅዱሳን ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ።
"በስመ #አብ_ወወልድ_ወመንፈስ_ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

#ጥቅምት ፳፱ (29) ቀን እንኳን #ለኢትዮጵያኑ_ጻድቃን ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ታዴዎስ_ዘጽላልሽ_ግመልን_በመርፌ_ቀዳዳ አሳልፈው ሙት አስነስተው ብዙ ሕዝብ ላሳመኑበት ለተአምራት በዓላቸው፣ እግዚአብሔር በሰላምና በጤና አደረሰን።

                          
#አቡነ_ታዴዎስ_ያደረጉት_ተአምር_ይህ_ነው፦ በአቡነ ታዴዎስ አላምንም የሚል ኢሳ የሚባል አንድ የእስላም ንጉሥ ተነሳ እና እንዲህ አላቸው "ስም ታዴዎስ ነው ሐዋርያው ታዴዎስ ግመል በመርፌ ቀዳዳ አስወጥቷል ይባላል አስወጣና ልመንብህ" አላቸው። ይህን ቃል ሲናገራቸው አቡነ ታዴዎስ ሳቁበት "በል ግመልና መርፌ አምጣ እኔ አሳይሃለው" ሲሉት ሠላሳ ግመል አመጣ አቡነ ታዴዎስም "በል መርፌውን በእጅህ ያዘው ቀዳዳውን ወደ ግመሊቱ አዙረህ" አሉት ወደ ግመሊቱ ቀርበው "በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም አዝዝሻለሁ" ሲሏት አንገቷን በመርፌው አስገብታ ከልጇ ጋር ወጣችና ሃያ ስምንቱን መጀመሪያ የወጣችቱ ግመል እንደ ሰው እየጠራቻቸው ወጡ ይህንን ድንቅ ስራ ያየ መርዩጥም ሆነ ሰራዊቱ የደብረ ማርያም ህዝብ ሲያደንቁ።

በዚያን ጊዜ የኢሳ ልጅ ሙሳ ሳቀ "በምትሃት እንጂ በብቃት አላወጣም" ብሎ ሲጠራጠር አንዲቱ ግመል ሆዱን በእርግጫ ስትመታው ሞተ አንጀቱ ተጎለጎለ በዚያን ጊዜ ሰው ሁሉ ደነገጠ ንጉሡም ደነገጠ ወዲያ ወዲህ እየሮጠ "አባቴ ሆይ እማፀንሃለው ማረኝ እንደ ሙሳ አልሳቅሁም" አቡነ ታዴዎስም "መዩጥ ሆይ ከልብህ እመን ከዚህ በላይ ታያለህ ከ #እግዚአብሔር የሚሆንን ነገር ምንም የሚያገኝህ ነገር የለም አትፍራ ከልብህ ካመንክ የሞተው ይነሳል ስላንተ አምላኬ ያነሳዋል" በዚህ ጊዜ መዩጥ አቡነ ታዴዎስን "እንዴት ሆኖ የሞተ ሰው ይነሳል በል አንተ አስነሳው የደራ ህዝብ ያምን ዘንድ በአምላክህ" አቡነ ታዴዎስ መዩጥን "ይቅበሩት እዘዝ ነገ ያነሳዋል ከተቀበረ በኋላ ነገ ሁሉ ሰው ከዳር እስከ ዳር ወንድ ሴት ትልቅ ትንሽ ሳይባል ይሰብሰብ ይህ ሬሳ የተነሳ እንደሆነ በአምላኬ እንድታምኑ ካልተነሳ እኔን ግደለኝ ከዚህ በኋላ ቅበሩት በዚች ቀን ጠዋት ከደብረ ማርያም ያልተገኘ ክፉ ሞት ይሞታል" አለ በዚች ሌሊት አቡነ ታዴዎስ ከደብረ ማርያም ቤተ ክክርስቲያን ውስጥ ከቅድስት ሆነው በየሰዓቱ መቶ መቶ ስግደት እየሰገዱ "ከመቃብር አላዓዛርን እንዳስነሳህ ይህንንም ሙት አንሳው" መዩጥ እንዲምን ብሎ እየጸለዩ ሳሉ ከሌሊቱ 11ሰዓት ጥቅምት 29 ቀን መልአከ #እግዚአብሔር ወርዶ "የሞተው ይነሳል ስለ አንተ ጸሎት ብሎ ይችን ደብረ ማርያምን አሥራት አድርጌ ሰጥቸሃለሁ በእኔም ስም ስላገኘህ ችግር በጾም በጸሎት ሃይማኖትን በማስተማር ከአጋንንት ጋር በመጋደልህ ከክፉ ሰዎች ጋር በመጋደልህ ደብረ ማርያምን የልጆችህ ርስት አድርጌ ሰጥችሀለሁ እስከ መጨረሻው ድረስ" ብሎት መልአከ #እግዚአብሔር ወደ ሰማይ አረገ።

አቡነ ታዴዎስም እስከ ከቀኑ ሦስት ሰዓት ሲጸልዩ አደሩ ህዝቡ ተሰብስበው ሳለ መዩጥ መጣና ከሰራዊቱ መካከል ተቀመጠ አቡነ ታዴዎስም ጠራቸው "አባቴ ሆይ ትናት እዳልከኝ አድርግ በህዝቤ መካከል የሰበሰብኋቸው ስላንተ ነውና" ሲላቸው "በል የሙቱን አባት አምጣው ወደ እኔ" ሲሉ አቀረቡላቸው አቡነ ታዴዎስም ለአባቱ #መስቀላቸውን ሰጡትና እንደ "አላዓዛር ተነስ በለው ይነሳልሃል" አሉትና የአቡነ ታዴዎስን #መስቀል ይዞ ተነሳ ሲለው ሙቱ ተነስቷል ከዚህም በኋላ የደራ ህዝብ በመላው አምኖ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም አጥምቀው ሃይማኖትን አስተምረው 12 ቤተ ክርስቲያን አሳነጹ።

ከአባታችን አቡነ ታዴዎስ #እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸውም ይማረን።

ምንጭ፦ የጣና ሐይቅ ደብረ ማርያም ገዳም አጭር ታሪክ ከምትላው መጸሐፍ።
🌹 #የጥቅምት_29_ግጻዌ 🌹

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጥቅምት_29_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
2ኛ ቆሮ 7
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ እንግዲህ፥ ወዳጆች ሆይ፥ የዚህ ተስፋ ቃል ካለን፥ በእግዚአብሔር ፍርሃት ቅድስናን ፍጹም እያደረግን ሥጋንና መንፈስን ከሚያረክስ ሁሉ ራሳችንን እናንጻ።
² በልባችሁ ስፍራ አስፉልን፤ ማንንም አልበደልንም፥ ማንንም አላጠፋንም፥ ማንንም አላታለልንም።
³ ለኵነኔ አልልም፤ በአንድነት ለመሞትና በአንድነት ለመኖር በልባችን እንዳላችሁ አስቀድሜ ብዬአለሁና።
⁴ ስለ እናንተ እምነቴ ታላቅ ነው፥ በእናንተ ምክንያት ትምክህቴ ታላቅ ነው፤ መጽናናት ሞልቶብኛል፤ በመከራችን ሁሉ ደስታዬ ከመጠን ይልቅ ይበዛል።
⁵ ወደ መቄዶንያም በመጣን ጊዜ፥ በሁሉ ነገር መከራን ተቀበልን እንጂ ሥጋችን ዕረፍት አልነበረውም፤ በውጭ ጠብ ነበረ፥ በውስጥ ፍርሃት ነበረ።
⁶ ነገር ግን ኀዘንተኞችን የሚያጽናና አምላክ በቲቶ መምጣት አጽናናን፤
⁷ በመምጣቱም ብቻ አይደለም ነገር ግን ናፍቆታችሁንና ልቅሶአችሁን ስለ እኔም ቅንዓታችሁን ሲናገረን በእናንተ ላይ በተጽናናበት መጽናናት ደግሞ ነው፤ ስለዚህም ከፊት ይልቅ ደስ አለን።
⁸ በመልእክቴ ያሳዘንኋችሁ ብሆን እንኳ አልጸጸትም፤ የተጸጸትሁ ብሆን እንኳ፥ ያ መልእክት ጥቂት ጊዜ ብቻ እንዳሳዘናችሁ አያለሁና አሁን ለንስሐ ስላዘናችሁ ደስ ብሎኛል እንጂ ስላዘናችሁ አይደለም፤
⁹ በምንም ከእኛ የተነሣ እንዳትጎዱ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ አዝናችኋልና።
¹⁰ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የሆነ ኀዘን ጸጸት የሌለበትን፥ ወደ መዳንም የሚያደርሰውን ንስሐ ያደርጋልና፤ የዓለም ኀዘን ግን ሞትን ያመጣል።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ዮሐንስ 3
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁷ ልጆች ሆይ፥ ማንም አያስታችሁ፤ እርሱ ጻድቅ እንደ ሆነ ጽድቅን የሚያደርግ ጻድቅ ነው።
⁸ ኃጢአትን የሚያደርግ ከዲያብሎስ ነው፥ ዲያብሎስ ከመጀመሪያ ኃጢአትን ያደርጋልና።
⁹ ስለዚህ የዲያብሎስን ሥራ እንዲያፈርስ የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ። ከእግዚአብሔር የተወለደ ሁሉ ኃጢአትን አያደርግም፥ ዘሩ በእርሱ ይኖራልና፤ ከእግዚአብሔርም ተወልዶአልና ኃጢአትን ሊያደርግ አይችልም።
¹⁰ የእግዚአብሔር ልጆችና የዲያብሎስ ልጆች በዚህ የተገለጡ ናቸው፤ ጽድቅን የማያደርግና ወንድሙን የማይወድ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም።
¹¹ ከመጀመሪያ የሰማችኋት መልእክት፦ እርስ በርሳችን እንዋደድ የምትል ይህች ናትና፤
¹² ከክፉው እንደ ነበረ ወንድሙንም እንደ ገደለ እንደ ቃየል አይደለም፤ ስለ ምንስ ገደለው? የገዛ ሥራው ክፉ፥ የወንድሙም ሥራ ጽድቅ ስለ ነበረ ነው።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 9
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁰ ወዲያውም ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ በምኵራቦቹ ሰበከ።
²¹ የሰሙትም ሁሉ ተገረሙና፦ ይህ በኢየሩሳሌም ይህን ስም የሚጠሩትን ያጠፋ አይደለምን? ስለዚህስ ታስረው ወደ ካህናት አለቆች ይወስዳቸው ዘንድ ወደዚህ አልመጣምን? አሉ።
²² ሳውል ግን እየበረታ ሄደ፥ በደማስቆም ለተቀመጡት አይሁድ ይህ ክርስቶስ እንደ ሆነ አስረድቶ መልስ ያሳጣቸው ነበር።


²⁴ ሳውል ግን አሳባቸውን አወቀ። ይገድሉትም ዘንድ በሌሊትና በቀን የከተማይቱን በር ሁሉ ይጠብቁ ነበር፤
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_29_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇🌹

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወታቀንተኒ ኃይለ በጸብእ። ወአዕቀጽኮሙ ለኵሎሙ እለ ቆሙ ላዕሌየ በመትሕቴየ"። መዝ.17፥39-40።
"ለሰልፍም ኃይልን ታስታጥቀኛለህ፤ በበላዬ የቆሙትን ሁሉ በበታቼ ታስገዛቸዋለ የጠላቶቼን ጀርባ ሰጠኸኝ፥ የሚጠሉኝንም አጠፋሃቸው"። መዝ. 17፥39-40።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_29_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማርቆስ 8
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³⁴ ሕዝቡንም ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦ በኋላዬ ሊመጣ የሚወድ ቢኖር፥ ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ።
³⁵ ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታልና፥ ስለ እኔና ስለ ወንጌል ነፍሱን የሚያጠፋ ሁሉ ግን ያድናታል።
³⁶ ሰው ዓለምን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል?
³⁷ ሰውስ ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል?
³⁸ በዚህም በዘማዊና በኃጢአተኛ ትውልድ መካከል በእኔና በቃሌ የሚያፍር ሁሉ፥ የሰው ልጅ ደግሞ በአባቱ ክብር ከቅዱሳን መላእክት ጋር በመጣ ጊዜ በእርሱ ያፍርበታል።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️ 🌹
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #እመቤታችን_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም #የአምላካችን_የጌታችን_የመድኃኒታችን_የኢየሱስ_ክርስቶስ የልደቱ መታሰቢያ በዓል፣ የአቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ፣ የአቡነ ዕንቆ ብርሃን፣ የቅዱስ ድሜጥሮስ ሰማዕት የዕረፍት በዓል፣ የአቡነ ታዴዎስ የተአምራት በዓልና መልካም የጽጌ ጾም ለሁላችንም ይሁንልን።
🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጥቅምት_30

#አንድ_አምላክ_በሆነ_በአብ_በወልድ_በመንፈስ_ቅዱስ ስም
ጥቅምት ሠላሳ በዚህች ቀን ወንጌልን የጻፈ ሐዋርያው #ቅዱስ_ማርቆስ የተወለደበት ነው፣ #የመጥምቁ_ዮሐንስ ቅድስት ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በግልጽ የታየችበት ነው፣ በገድል የተጸመደ #ቅዱስ_አባት_ባሕታዊ_አብርሃም ያረፈበት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ማርቆስ_ወንጌላዊ

ጥቅምት ሠላሳ በዚህች ቀን ለእስክንድርያ ሊቃነ ጳጳሳት አለቃ የሆነ ወንጌልን የጻፈ ሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ የተወለደበት ነው።

የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አርስጦቡሎስ ነው እርሱም ከአምስቱ አገሮች የሆነ የእናቱም ስም ማርያም ነው እርሷም በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ተጽፋለች እርሱም አስቀድሞ ስሙ ዮሐንስ ነው። በግብረ ሐዋርያት ማርቆስ በተባለ በዮሐንስ እናት ቤት ሐዋርያት ይጸልዩ ነበር ተብሎ እንደ ተጻፈ። እርሷም ባለጸጋ ነበረችና የዮናናውያንን የሮማይስጥን የዕብራይስጥን ትምህርት ለልጅዋ ለማርቆስ አስተማረችው።

በአደገም ጊዜ በርናባስ ወንጌልን ለመስበክ ከጳውሎስ ጋራ ሲሔድ ይዞት ሔደ በእነርሱም ላይ የሚደርስባቸውን መከራ አይቶ በጵንፍልያ ከተማ ሳሉ ትቷቸው ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ።

ሐዋርያትም በተመለሱ ጊዜ የክብር ባለቤት የሆነ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስን ወደ ማመን አሕዛብ እንደ ተመለሱ #እግዚአብሔርም በእጆቻቸው ላይ ድንቅ ተአምራትን እንዳደረገ ተናገሩ። ይህ ብላቴና ማርቆስም ከእርሳቸው ስለ መለየቱ አዘነ ተጸጸተ።

ከዚያም አብሮአቸው ሊሔድ ፈለገ አስቀድሞ ትቷቸው ስለተመለሰ ቅዱስ ጳውሎስ ሊአስከትለው አልወደደም በርናባስ ግን ወሰደው አጎቱ ነውና። በርናባስም ከአረፈ በኋላ ወደ ሮሜ አገር ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ሒዶ ለእርሱ ደቀ መዝሙሩ ሆነ በዚያም ቅዱስ ጴጥሮስ የተረጐመለትን ወንጌልን ጻፈ በሮሜ አገርም አስተማረበት። ከዚያም በክብር ባለቤት በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ትእዛዝና በሐዋርያትም ትእዛዝ ወደ እስክንድርያ አገር ሔደ። በውስጥዋም የከበረ ወንጌልን አስተማረ ደግሞም በአፍራቅያና በአምስቱ አገሮች በርቃ በሚባልም አገር ወደ እስክንድርያ ከተማ በገባ ጊዜ ጫማው ተቆረጠ።

በዚያም በከተማው መግቢያ ጫማ ሰፊ ነበረ። ቅዱስ ማርቆስም እንዲሰፋለት ለርሱ ሰጠው ሲሰፋም ጣቱን ወግቶ ሰነጠቀው ከእርሱም ደም ፈሰሰ በዮናኒም ቋንቋ ኢታስታዖስ አለ ትርጓሜውም አንድ #እግዚአብሔር ማለት ነው። ቅዱስ ማርቆስም ስሙን የምትጠራው አውቀኸው ነውን አለው እንጠራዋለን እንጂ አናውቀውም አለ።

#እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ከፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ አባታችን አዳም ትእዛዙን እንደተላለፈ የጥፋት ውኃም እንደ መጣ ሙሴንም እንደላከውና እስራኤልን ከግብጽ እንዳወጣቸው ሕግንም እንደ ሠራላቸው ናቡከደነጾርም ወደ ባቢሎን ማርኮ እንደወሰዳቸውና ከሰባ ዓመት በኋላ ወደ አገራቸው ኢየሩሳሌም እንደ ተመለሱ #ክርስቶስ ሥጋ በመልበስ ወደ ዓለም ስለ መምጣቱ ነቢያት ትንቢት እንደ ተናገሩ ያስተምረው ዘንድ ጀመረ።

ከዚያም በኋላ ወደ ምድር ምራቁን ትፍ ብሎ ጭቃ አድርጎ ጣቱን ቀባው ወዲያው ዳነ በ #ጌታችንም አመነ። ያም ሰፊ ስሙ አንያኖስ ነው። ቅዱስ ማርቆስንም ወደ ቤቱ ወስዶ ልጆቹን ዘመዶቹንም ወደ ርሱ አቀረበ እርሱም አስተምሮ አንድ አምላክ በሆነ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው።

በክብር ባለቤት በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ያመኑ ሰዎች በበዙ ጊዜ የቅዱስ ማርቆስን ዜና ሰምተው የአገር ሰዎች ሊገድሉት ተሰበሰቡ እርሱም አንያኖስን ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሹሞ ልጆቹን ቄሶችና ዲያቆኖች አድርጎ ከዚያም ወደ በርቃ ወደ አምስቱ አገሮችም ወጥቶ አስተማረ። በቀናች ሃይማኖትም አጸናቸው በእርሳቸውም ዘንድ ሁለት ዓመት ኖረ ኤጲስቆጶሳትን ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው።

ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ተመለሰ ምእመናንም ተጨምረው በዝተው በታወቁ ቦታዎች ሁሉ በባሕሩም ዳር በላሞች መካበቢያ በሚባለውም አብያተ ክርስቲያን ሠርተው አገኛቸው።

ከሀድያንም የከበረ ሐዋርያን ይገድሉት ዘንድ በብዙ ድካም ፈለጉት እርሱም አምስቱን አገሮች ሲጐበኝ በሥውር ወደ እስክንድርያ ከተማ ይገባ ይወጣ ነበር። በአንዲትም ዓመትም ከአምስቱ አገሮች ተመልሶ ሚያዝያ ዐሥራ ሰባት ቀን በ #መድኃኒታችን የትንሣኤ በዓል ወደ ቤተክርስቲያን ገባ ሕዝቡም ሁሉ በዙሪያው አሉ። ከሀድያንም ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተው በአንገቱ ውስጥ ገመዶችን አድርገው በከተማው ሁሉ ጎተቱት። እነርሱም ገና እንደፍየል ሙክት እንጎትተዋለን እያሉ ይጮኹ ነበር ። በላሞች መካበቢያና በሀገሪቱ አደባባይ በከተማውም ዙሪያ በየቀኑ ሲጎትቱት ኖሩ።

ሌሊትም በሆነ ጊዜ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከሐዋርያት ጋራ በነበረበት አርአያ ሁኖ ተገለጠለት ሰላምታም ሰጥቶ አጽናናው ቃል ኪዳንም ሰጠው። እነሆ አንተ ከወንድሞችህ ሐዋርያት ጋር ተካከልህ አለው። እርሱም በልቡናው ፈጽሞ ደስ አለው። በማግሥቱም ሁለተኛ ገመዶችን በአንገቱ አድርገው በአገሮች ሁሉ ጎተቱት በቀኑም መጨረሻ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ።

ከሀዲዎችም ታላቅ እሳትን አንድደው የቅዱስ ማርቆስን ሥጋ ከውስጡ ጨመሩ ። በክብር ባለቤት #ጌታችን ፈቃድም ንውጽውጽታ ጨለማ ቀዝቃዛ ነፋስ መብረቅና ነጐድጓድ ሆነ። ፀሐይም ጨለመ ከሀዲዎችም ሸሹ ምእመናንም መጥተው የሐዋርያ ቅዱስ ማርቆስን ሥጋ ወሰዱ ምንም ጥፋት ሳይደርስበት ደኀና ሆኖ አገኙት በመልካም ልብስም ገንዘው በጥሩ ቦታ አኖሩት መታሰቢያውንም አደረጉ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቀ_መለኮት

ዳግመኛም በዚህች ቀን የመጥምቁ ዮሐንስ ቅድስት ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በአየር ውስጥ እየበረረች 15 ዓመት ስታስተምር ከኖረች በኋላ በዐረቢያ ምድር በግልጽ ታይታለች፡፡

ይኸውም የሆነው እንዲህ ነው፡- ሄሮድያዳ ልጅ ርጉም የሆነ ንጉሥ ሄሮድስን በዘፈኗ በጣም አድርጋ ስላስደሰተችው እርሱም በተራው ሊያስደስታት ፈለገና እስከ መንግሥቱ እኩሌታ ድረስም ቢሆን የለመነችውን ይሰጣት ዘንድ በሕዝቦቹና በመኳንንቱ ሁሉ ፊት እንዳይከዳት በፅኑ ቃልኪዳን ማለላት፡፡ እርሱም አስቀድሞ "የፈለግሽውን ጠይቂኝ፣ የመንግሥቴንም እኩሌታ ቢሆን እሰጥሻለሁ ምን ላድርግልሽ?" እያለ በመሐላ ባላት ጊዜ በእናቷ ምክር የዮሐንስን አንገት ቆርጦ ይሰጣት ዘንድ ለመነችው፡፡ እርሱም ስለማሐላው የዮሐንስን አንገት እንድትቆረጥ አደረገ፡፡ በመጀመሪያም የሄሮድስ ወታደሮች ሠይፍ ይዘው የዮሐንስን አንገት ይቆርጡ ዘንድ ወደ መኅኒ ቤት ሲሄዱ ቅዱስ ዮሐንስም የሄሮድስ ጭፍሮች ሊገድሉት እንደመጡ በ #መንፈስ_ቅዱስ ፀጋ ስላወቀ ከጨለማው ቤት ውስጥ አንገቱን በመስኮት አውጥቶ እንደሚመቻቸው አድርጎ ጠበቃቸው፡፡ የንጉሡም ጭፍሮች የመጥምቁን ራስ በወጪት አድርገው ለንጉሣቸው ሄሮድስ ሰጡት፡፡ ሄሮድስም ለሄሮድያዳ ልጅ ሰጣት፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ግን በወጪት ላይ ሆና ሕዝቦቹና የመንግሥቱ ታላላቅ ሰዎች እየሰሟት በየመኳንንቱ ፊት ንጉሥ ሄሮድስን "የወንድምህን የፊሊጶስን ሚስት ማግባት አይገባህም" እያለች መጀመሪያ ትዘልፈው እንደነበረው ሁሉ አሁንም ዘለፈችው፡፡ መዓዛዋም እጅግ ደስ የሚያሰኝ ነበር፣ ዐይኖቹም እንደፀሐይ ያበሩ ነበር፡፡
የሄሮድያዳም ልጅ የመጥምቁን ራስ ወስዳ ለእናቷ ልትሰጣት ስትል ዐይኖቹ እንደፀሐይ ሲያበሩ ብታየው "ንጉሡን አትፈራውምን?" በማለት ተቆጣች፡፡ በመቀጠልም "እነዚህን ዐይኖቹን በወስፌ እያወጣሁ እጥላቸዋለሁ፣ ምላሱንም ደግመኛ እንዳይገሥጽ ቆርጨ እጥላቸዋለሁ" በማለት ፊቱን በጥፊ ለመምታት እጇን ስታነሣ ያንጊዜ የዮሐንስ ራስ ክንፍ አውጥታ በረረች፡፡ በአየር ላይ ሳለችም ዳግመኛ "የተረገምሽ ሄሮድያዳ የባልሽን ወንድም ሄሮድስን ማግባት አይገባሽም፣ ቀድሞ የምዘልፍሽ አሁንም የምዘልፍሽ እኔ ነኝ" እያለች የዮሐንስ ራስ የቤቱን ጣሪያ ሰንጥቃ እንደንሥር በአየር በራ ሄደች፡፡

ከዚህም በኋላ ለጥፊ የዘረጋቻቸው የሄሮድያዳ እጆቿ ከትከሻዋ እየተቆረጡ መሬት ላይ ወደቁ፤ እውነቷንም መሬት አፏን ከፍታ ዋጠቻት፡፡ ዘፋኟ ልጇም አብዳ የቤተ መንግሥቱን ዕቃ ሁሉ መሰባበር ጀመረች፡፡ የንጉሡ አንዱ ጭፍራም የሄሮድያዳን በእሳት እንደተለበለበ የግንድ እሳት የመሰለና የተቆረጠ እጇን አምጥቶ ለሄድሮስ ሰጠውና የሆነውን ነገረው፡፡ ንጉሡም ነገሩ እውነት መሆኑን ሄዶ ባየ ጊዜ በሀፍረት እጅግ ተሸማቀቀ፡፡ ዘፍና በማስደሰት የዮሐንስን ራስ እንዲያስቆርጠው ያደረገችው የሄሮድያዳ ሴት ልጅም አብዳ በቤተ መንግሥቱ ስትለፈልፍ አገኛት፡፡ ሄሮድስም መኳንንቶቹን "በቤተ መንግሥቴ የተደረገውን ይህን ነገር ለማንም አትንገሩ" ብሎ አማላቸው ነገር ግን ያበደችው የሄሮድያዳ ሴት ልጅ ራሷ ሄዳ ሄሮድስን "የወንድምህን የፊሊጶስን ሚስት ማግባት ፈጽሞ አይገባህም" እያለች በመኳንንቶቹ ፊት ገሠጸችው፡፡ ንጉሥ ሄሮድስም ይህን ቃል ከእርሷ በሰማ ጊዜ እጅግ ተናደደና "ቀደሞ ያልሆነ ሥራ ታሠራ በኋላ ደግሞ ምሥጢር ታወጣ ንሣ በሰይፍ ቁረጣት" ብሎ አንገቷን በሰይፍ አስቆረጣት፡፡ ሥጋዋንም ዓሣ አንበሪ ተቀብሎ ዋጣት፡፡ ሄሮድም የወንደሙን ሚስት ሲያገባ አስቀድሞ አግብቷት የነበረችውን ሚስቱን በግፍ አባሯት ነበር፡፡ እርሷም ይህንን ሄሮድስ ያደረሰባትን ግፍ ለአባቷ አርጣ ብትነግረው አባቷ ብዙ ጦር ሰብስቦ መጥቶ ምድረ ገሊላን በኃይል አፈራረሳት፡፡ የበላዩ ንጉሥ ቄሳርም የገሊላን መፍረስና መውድም ሲሰማ ምክንያቱን ቢጠይቅ ሄሮደስ ባደረገው ግፍ ምክንያት መሆኑን ነገሩት፡፡ ቄሳርም ሄሮድስን ከሥልጣኑ ሽሮ አጋዘውና በወህኒ ጣለው፡፡ ሄሮድስም በወህኒ ቤት ሳለ አብዶ ራሱን ስቶ የገዛ አካሉን እየነጨ እየበላ ቷ ብሎ ፈንድቶ ተልቶ ሸቶ እጅግ ክፉ አሟሟት ሞተ።

ከዚህም በኋላ #ጌታችን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ራስ መለስ ብሎ እንዲህ በማለት ሥልጣን ሰጣት፡- "እነሆ መንፈስሽን በራስሽ ውስጥ አድርጌልሻለሁ በሰማይም የምትበሪበት እንደ ንሥር ክንፍ ሰጥቼሻለሁና እንደንስር በሰማይ እየበረርሽ በዓለም ሁሉ እየዞርሽ የሄሮድስንና የሄሮድያዳን ኃጢአት ግለጭባቸው፤ እስከ 15 ዓመት ድረስ ገቢረ ተአምራት የምታደርጊበት ኃይሌን መንፈሴን በእራስሽ ውስጥ አድርጌልሻለሁ" አላት፡፡ ዳግመኛም #ጌታችን ዮሐንስን "እኔም ከ3 ዓመት በኋላ ለአዳም የሰጠሁትን ተስፋ ፈጽሜ በሞቴ ወደ ሲኦል ወርጄ ነፍሳትን ከዲያብሎስ እጅ ማርኬ በ3ኛው ቀን ከሙታን ተለይቼ ተነሥቼ ወደ ባሕርይ ክብሬ ተመልሼ ወደ ሰማይ አርጌ ባባቴ ቀኝ በተቀመጥኩኝ ጊዜ ከ15 ዓመት በኋላ ርጉም ሄሮድስ ካስፈጃቸው ከትንንሾቹ ሕፃናት ጋራ ትሆን ዘንድ በአባቴ ፈቃድ እራስህን ተሸክመው ወደ አባትህ ወደ ዘካርያስ ያመጧት ዘንድ እኔ መላእክትን አዛቸዋለሁ፡፡ ዛሬ ግን ነፍስህን በእኔ ቀኝ ባባትህ በዘካርያስ አጠገብ አኑሬያታለሁ መንፈስህንም እስከ 15 ዓመት በእራስህ ውስጥ እንድትኖር አዝዣታለሁ፣ ሥጋህም ከነቢዩ ከኤልሳዕ ጋር እንዲቀመጥ አድርጌያለሁ" አለው፡፡

ከዚህም በኋላ #ጌታችን እንዳዘዛት የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ እራስ እንደንስር በአየር ላይ እየበረረች የምታስተምር ሆነች፡፡ በምሥራቅ በኩል ሄዳ በዐረብ አገር ውስጥ በሰማይ ላይ ስታስተምር በዚህች ዕለት ጥቅምት 30 ቀን በግልጽ ታየች፡፡ ነጋዴዎች ድምጹዋን ሰምተውና አይተዋት እጅግ ተደስተው ገንዘባቸው ሁሉ ጥለው የቅዱስ ዮሐንስን እራስ ለመያዝ ሰውነታቸውን ብዙ አደከሙ፡፡ ነገር ግን ለመያዝ አልተቻላቸውም፡፡ ከዚህም በኋላ ከሰማይ "የምትያዝበት ጊዜ ስላልደረሰ ሰውነታችሁን አታድክሙ" የሚል ድምጽ ከሰማይ መጣላቸው፡፡ መፈለጋቸውንም ተው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስም እራስ 15 ዓመት ስታስተምር ኖራ ሚያዝያ 15 ቀን በዐረብ ሀገር ዐረፈች፡፡ የታዘዙ ቅዱሳን መላእክትም መጥተው ከቅዱስ ዮሐንስ እራስ ከተባረኩ በኋላ በታላቅ ዝማሬ እያመሰገኑ የቅዱስ ዮሐንስን አንገት ወስደው በነቢዩ ኤልሳዕ መቃብር ውስጥ አብረው ቀበሯት፡፡ ቅድስትን ነፍሱንም እያመሰገኑ ወደ ሰማይ አሳረጓት፡፡ በዚያም በ #ሥሉስ_ቅዱስ ዙፋን ፊት ወድቃ ከሰገደች በኋላ አባቷ ዘካርያስንና እናቷ ኤልሳቤጥን እጅ ነሳቻቸው፡፡ ከዚህም በኋላ በ3ኛው ሰማይ ውስጥ ተቀመጠች፡፡ #ጌታችን ሦስቱን ሰማየ ሰማያት ርስት ጉልት አድርጎ ሰጥቶታልና፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባት_ባሕታዊ_አብርሃም

በዚህች ቀን መኑፍ ከሚባል አገር በገድል የተጸመደ ቅዱስ አባት ባሕታዊ አብርሃም አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ #እግዚአብሔርን የሚፈሩና የሚያመልኩ ናቸው በዚህም ዓለም ገንዘብ እጅግ ባለጸጎች ነበሩ።

ይህም ቅዱስ በአደገ ጊዜ የምንኵስናን ልብስ ሊለብስ ሽቶ በላዕላይ ግብጽ ወደሚገኝ ወደ ሀገረ አክሚም በመርከብ ተጭኖ ሔደ ወደ አባ ጳኵሚስም ደረሰ እርሱም የምንኲስና ልብስን አለበሰው በገድልም በመጸመድ ሥጋውን አደከመ በአባ ጳኵሚስም ማኅበራዊ ኑሮ ውስጥ ሃያ ሦስት ዓመት ያህል በማገልገል ኖረ።

ከዚህም በኋላ በዋሻ ውስጥ ብቻውን ይኖር ዘንድ እንዲአሰናብተው አባ ጳኵሚስን ለመነው እርሱም ፈቀደለት ዓሣ የሚያሠግሩበትን መረብ የሚሠራ ሆነ ክብር ይግባውና #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስም አንድ ሰውን አመጣለት ያም ሰው መረቡን ሽጦ ምግቡን አተር ይገዛለታል የተረፈውንም ለድኆች ይሰጣል የምግቡም መጠን ሁልጊዜ ማታ ማታ አንዲት እፍኝ ከጨው ጋር በውኃ የራሰ አተር ነው።

እንዲህም እየተጋደለ በዚያች ዋሻ ዐሥራ ሰባት ዓመት ኖረ ልብሱም ከገዳም ሲወጣ የለበሰው ከዘመን ርዝመት የተነሣ አርጅቶ ተበጣጠሰ ሥጋውንም በጨርቅ የሚሸፍን ሆነ። በየሁለት ዓመትም ወደ መነኰሳቱ ገዳም በመውጣት ሥጋውንና ደሙን ተቀብሎ ወደ በዓቱ ይመለስ ነበር። በዚያችም ዋሻ መኖር በጀመረባት ዓመት ሰይጣናት ወደ ርሱ በመምጣት ምትሐት እየሠሩ ተፈታተኑት እርሱ ግን ውሻን እንደሚአበር ሰው አበረራቸው።

ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ ያን ሕዝባዊ ሰው ልኮ የአባ ጳኵሚስን ረድእ አባ ቴዎድሮስን አስጠራው በመጣም ጊዜ ሰግዶ ሰላምታ ሰጠው እንዲጸልይለትና በጸሎቱም እንዲአስበው ለመነው። ከዚህም በኋላ ሁለቱም በአንድነት ጸለዩ በዚያንም ጊዜ አባ አብርሃም በርከክ ብሎ ነፍሱን በ #እግዚአብሔር እጅ ሰጠ አባ ቴዎድሮስም ወደ መነኰሳቱ ላከ እነርሱም መጥተው ከሥጋው በረከትን ተቀበሉ ሥጋውንም ወሰደው ከቅዱሳን ሥጋ ጋር በአንድነት አኖሩት።

#እግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘላለሙ ትኑር አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምትና_30_ሚያዝያ
#ከገድላት_አንደበት)
🌹 #የጥቅምት_30_ግጻዌ 🌹

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጥቅምት_30_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ፊልጵስዩስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያዎች የሆኑ ጳውሎስና ጢሞቴዎስ በፊልጵስዩስ ለሚኖሩ ከኤጲስ ቆጶሳትና ከዲያቆናት ጋር በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት ቅዱሳን ሁሉ፤
² ከእግዚአብሔር ከአባታችን ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን።
³-⁵ ሁልጊዜ በጸሎቴ ሁሉ ስለ እናንተ ሁሉ በደስታ እየጸለይሁ፥ ከፊተኛው ቀን እስከ ዛሬ ድረስ ወንጌልን በመስበክ አብራችሁ ስለ ሠራችሁ፥ ባሰብኋችሁ ጊዜ ሁሉ አምላኬን አመሰግናለሁ።
⁶ በእናንተ መልካምን ሥራ የጀመረው እስከ ኢየሱስ ክርስቶስ ቀን ድረስ እንዲፈጽመው ይህን ተረድቼአለሁና፤
⁷ በእስራቴም ወንጌልንም መመከቻና መጽኛ በማድረግ ሁላችሁ ከእኔ ጋር በጸጋ ተካፋዮች ስለ ሆናችሁ፥ በልቤ ትኖራላችሁና ስለ ሁላችሁ ይህን ላስብ ይገባኛል።
⁸ በክርስቶስ ኢየሱስ ፍቅር ሁላችሁን እንዴት እንድናፍቃችሁ እግዚአብሔር ምስክሬ ነውና።
⁹-¹¹ ለእግዚአብሔርም ክብርና ምስጋና ከኢየሱስ ክርስቶስ የሚገኝ የጽድቅ ፍሬ ሞልቶባችሁ፥ ለክርስቶስ ቀን ተዘጋጅታችሁ ቅኖችና አለ ነውር እንድትሆኑ የሚሻለውን ነገር ፈትናችሁ ትወዱ ዘንድ፥ ፍቅራችሁ በእውቀትና በማስተዋል ሁሉ ከፊት ይልቅ እያደገ እንዲበዛ ይህን እጸልያለሁ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ያዕቆብ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ የእግዚአብሔርና የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ ያዕቆብ ለተበተኑ ለአሥራ ሁለቱ ወገኖች፤ ሰላም ለእናንተ ይሁን።
²-³ ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት
⁴ ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም።
⁵ ከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋል።
⁶ ነገር ግን በምንም ሳይጠራጠር በእምነት ይለምን፤ የሚጠራጠር ሰው በነፋስ የተገፋና የተነቃነቀ የባሕርን ማዕበል ይመስላልና።
⁷-⁸ ሁለት አሳብ ላለው በመንገዱም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች እንዲያገኝ አይምሰለው።
⁹-¹⁰ የተዋረደው ወንድም ግን በከፍታው፥ ባለ ጠጋም በውርደቱ ይመካ፤ እንደ ሣር አበባ ያልፋልና።
¹¹ ፀሐይ ከትኵሳት ጋር ይወጣልና፥ ሣርንም ያጠወልጋልና፥ አበባውም ይረግፋልና፥ የመልኩም ውበት ይጠፋልና፤ እንዲሁ ደግሞ ባለ ጠጋው በመንገዱ ይዝላል።
¹² በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ከተፈተነ በኋላ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወትን አክሊል ይቀበላልና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 13
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁶ ደሴቲቱንም ሁሉ እስከ ጳፉ በዞሩ ጊዜ፥ በርያሱስ የሚሉትን ጠንቋይና ሐሰተኛ ነቢይ የሆነውን አንድ አይሁዳዊ ሰው አገኙ፤
⁷ እርሱም አስተዋይ ሰው ከሆነው ሰርግዮስ ጳውሎስ ከሚባለው አገረ ገዥ ጋር ነበረ። ይህም በርናባስንና ሳውልን ወደ እርሱ ጠርቶ የእግዚአብሔርን ቃል ሊሰማ ፈለገ።
⁸ ጠንቋዩ ግን ኤልማስ፥ ስሙ እንዲሁ ይተረጐማልና፥ አገረ ገዡን ከማመን ሊያጣምም ፈልጎ ተቃወማቸው።
⁹ ጳውሎስ የተባለው ሳውል ግን መንፈስ ቅዱስን ተሞልቶ ትኵር ብሎ ሲመለከተው፦
¹⁰ አንተ ተንኰል ሁሉ ክፋትም ሁሉ የሞላብህ፥ የዲያብሎስ ልጅ፥ የጽድቅም ሁሉ ጠላት፥ የቀናውን የጌታን መንገድ ከማጣመም አታርፍምን?
¹¹ አሁንም፥ እነሆ፥ የጌታ እጅ በአንተ ላይ ናት፥ ዕውርም ትሆናለህ እስከ ጊዜውም ፀሐይን አታይም አለው። ያን ጊዜም ጭጋግና ጨለማ ወደቀበት፥ በእጁም የሚመራውን እየዞረ ፈለገ።
¹² በዚያን ጊዜ አገረ ገዡ የተደረገውን ባየ ጊዜ ከጌታ ትምህርት የተነሣ ተገርሞ አመነ።
¹³ ጳውሎስም ከጓደኞቹ ጋር ከጳፉ ተነሥቶ የጵንፍልያ ወደምትሆን ወደ ጴርጌን መጣ፤ ዮሐንስም ከእነርሱ ተለይቶ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ።
¹⁴ እነርሱ ግን ከጴርጌን አልፈው የጲስድያ ወደምትሆን ወደ አንጾኪያ ደረሱ፤ በሰንበትም ቀን ወደ ምኵራብ ገብተው ተቀመጡ።
¹⁵ ሕግና ነቢያትም ከተነበቡ በኋላ የምኵራቡ አለቆች፦ ወንድሞች ሆይ፥ ሕዝብን የሚመክር ቃል እንዳላችሁ ተናገሩ ብለው ላኩባቸው።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_30_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇🌹

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወይከውን ከመ ዕፅ እንተ ትክልት ኅበ ሙሐዘ ማይ። እንተ ትሁብ ፍሬሃ በበጊዜሃ። ወቁጽላኒ ኢይትነገፍ"። መዝ.1÷3-4

#ትርጉም፦ “እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፤ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል።” መዝ.1÷3-4
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_30_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማቴዎስ 6
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁵ ስለዚህ እላችኋለሁ፥ ስለ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት፥ ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን?
²⁶ ወደ ሰማይ ወፎች ተመልከቱ፤ አይዘሩም አያጭዱምም በጎተራም አይከቱም፥ የሰማዩ አባታችሁም ይመግባቸዋል፤ እናንተ ከእነርሱ እጅግ አትበልጡምን?
²⁷ ከእናንተ ተጨንቆ በቁመቱ ላይ አንድ ክንድ መጨመር የሚችል ማን ነው?
²⁸ ስለ ልብስስ ስለ ምን ትጨነቃላችሁ? የሜዳ አበቦች እንዴት እንዲያድጉ ልብ አድርጋችሁ ተመልከቱ፤
²⁹ አይደክሙም አይፈትሉምም፤ ነገር ግን እላችኋለሁ፥ ሰሎሞንስ እንኳ በክብሩ ሁሉ ከነዚህ እንደ አንዱ አልለበሰም።
³⁰ እግዚአብሔር ግን ዛሬ ያለውን ነገም ወደ እቶን የሚጣለውን የሜዳን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከሆነ፥ እናንተ እምነት የጎደላችሁ፥ እናንተንማ ይልቁን እንዴት?
³¹ እንግዲህ፦ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን? ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤
³² ይህንስ ሁሉ አሕዛብ ይፈልጋሉ፤ ይህ ሁሉ እንዲያስፈልጋችሁ የሰማዩ አባታችሁ ያውቃልና።
³³ ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️ 🌹
 የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #የእመቤታችን_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም ዕለተ ሰንበትና የጽጌ ጾም ለሁላችንም ይሁንልን።
🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
👍1
2025/11/08 11:11:17
Back to Top
HTML Embed Code: