Telegram Web Link
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
እረሳለሁ እንጂ ባልረሳ ኖሮ ብዙ መርሳት የማልፈልገው ነገር ነበር!
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
የሃይስኩል ተማሪ እያለሁ በአጥር የመግባት ሱስ ነበረብኝ፡፡ጎበዝ ተማሪ ስለኾንኩ ብዙ ጊዜ ሽልማት አግኝቻለሁ፡፡ግን ምን ያደርጋል? ሽልማቴንም ልቀበል ስሔድ በአጥር ዘልዬ ካልገባሁ የተሸለምኩ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱን አላውቅም ግን በአጥር መግባት ያስደስተኝ ነበር፡፡ ምናልባት ትምህርት ቤቱ መግቢያ በር እንዳለው ስለምረሳ ይኾናል፡፡
.
አንድ ቀን እንደ ልማዴ የትምህርት ቤቱ በር ክፍት ሳለ በአጥር ዘልዬ ልገባ ስል ከአጥሩ ሥር የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር ሁለት እጁን ዘርግቶ ተቀበለኝ፡፡ ተሸክሞ ካወረደኝ በኋላ ወላጅ ሳታምጣ እንዳትመጣ ብሎ አሰናበተኝ፡፡
.
ቤት ሔጄ ወላጅ አምጣ እንደተባልኩ እንዴት ብዬ ልናገር? ምክንያቱም ወደ ቤቴም የምገባው በአጥር ዘልዬ ነው፡፡ ትምህርት ቤት በዛ ከተባለ ወላጅ አምጣ ነው ሚለው. . .ወላጆቼስ ምን አምጣ ይሉኛል? ብዬ ፈራሁ፡፡ በርግጠኝነት አባቴ ‹‹ቀበቶዬን አምጣ!›› ነው ሚለኝ፡፡
.
ስለዚህ አንድ ወጣት አጎት አለኝ… እሱን ወላጅ ሁነኝ ብዬ ለሱ ነገርኩት፡፡ ወደ ሥራ ስሔድ በዛው እመጣለሁ ብሎኝ ቃል ገባልኝ፡፡ ሰኞ ሲደርስ ዳይሬክተሩ ቢሮ ቁጭ ብዬ አጎቴን መጠበቅ ጀመርኩ፡፡ ትንሽ አርፍዶ መጣ፡፡ ዳይሬክተሩ ንግግር ጀመረ፡፡
‹‹ልጁ ጎበዝ ተማሪ ነው…ግን ጋጠ-ወጥ የኾነ ተግባር ሲፈፅም ነው እጅ ከፍንጅ ወይም በሱ ኬዝ እጅ ከግንብ የያዝኩት፡፡ሁሌ በአጥር የሚገባ ስለኾነ ነው የጠራንዎት….ከዚህ በኋላ በአጥር ቢገባ ከትምህርት ቤት ነው እንደ ምናባርረው ልንነግርዎት እንወዳለን!››
አጎቴ በጣም ተቆጣ፡፡ ‹‹አንተ ስድ! ያምሃል? አንተ ትልቅ ሰው ነህ እኮ እንዴት እንደዚህ ታደርጋለህ? አጥሩ እኮ አርጅቷል…እኔ ራሱ አሁን በዚያ በኩል ነው ዘልዬ የገባሁት….ቢደረመስ እኮ ትጎዳለህ! ከአሁን በኋላ በጓሮ በኩል ሌላ አጥር ካለ ዳይሬክተሩ ያሣይህና በዛ ትገባለህ!››
.
ዳይሬክተሩ የመርሳት ችግሬን ከግምት ሳያስገባ "በአጥር እየዘለልክ ሕልምህን አታሳካም!" ብሎ እያፌዘ መከረኝ።
.
እውነት ለመናገር…..እዚህ ሐገር ውስጥ አጥር ዘለልክም አልዘለልክም ሕልምህን ማሳካት ቀላል ነገር ነው እንዴ? እኛ ሐገር ውስጥ በቀላሉ ሕልምህን ምታሳካው አጥሩ አንተ ከኾንክ ብቻ ነው፡፡
በዚህ ሰዓት እንኳን ሕልምህን ማሳካት ሕልምህን ማስፈታት ራሱ ከባድ ኾኗል፡፡
በፊት እንደዋዛ ቡና እየጠጡ ሕልማችንን የሚፈቱ ሰዎች አሁን የኾነ ሕንፃ ላይ ቢሮ ተከራይተው ‹‹ሕልምህን ኑር!›› የሚል የማነቃቂያ ቪድዮ እየቀረፁ ነው፡፡ በዚህ ዘመን ምንም ነገር በነፃ የለም፡፡ እንደውም አንዳንዴ ‹‹ነፃነት›› ያጣነው ‹‹ነፃነት›› የሚለው ቃል ላይ ‹‹ነፃ›› የሚል ነገር ስላለ ይመስለኛል፡፡ ምንም ነገር ለማድረግ ወይ ገንዘብ ወይ ሰው ሊኖርህ ይገባል፡፡ እስር ቤት ራሱ በሰው በሰው ነው ምትገባው፡፡ እስር ቤት ገብተው ዝነኛ ኾነው የወጡ ሰዎችን አላያችሁም? እንደውም ሮናልዶ ራሱ ሳዑዲ የገባው ሳዑዲ ውስጥ ሰው ስላለው ነው፡፡
.
እኔ ሕልሜ ትልቅ ነበር፡፡ቤተሰቦቼ የዘይት ሥራ ላይ ስለተሠማሩ በአፍሪካ ትልቁን የዘይት ፋብሪካ ለመመሥረት ሕልም ነበረኝ፡፡ ለሕልሜ ሚበቃ ጥሩ ውጤትም ነበረኝ፡፡ ‹‹እና ለሕልምህ ምን ያህል ቅርብ ነህ?›› ብላችሁ ከጠየቃችሁኝ ‹‹በወር አንድ ጊዜ ዘይት እንዳያመልጠኝ ሸማቾች እሰለፋለሁ!›› የሚል ነው መልሴ። ይኼን ያህል ብቻ ነው ለሕልሜ የቀረብኩት፡፡
.
አሁን ሌላ አዲስ ሕልም አለኝ፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ››የሁሉም ነገር ሥያሜ ከእኛ ነው የተወሰደው›› የምንለውን ዐመል አቁመን ማየት ነው ሕልሜ፡፡ ዛሬ ታክሲ ውስጥ አንድ መሸምገላቸውን ካላመኑ አንድ አዛውንት አጠገብ ተቀመጥኩ፡፡ገና ከመቀመጤ ‹‹እንኳን አደረሰህ ልጄ!›› አሉኝ፡፡ ‹‹ለምኑ?›› ስላቸው ‹‹ዛሬ እኮ ጃንዋሪ 1 ነው! አዲስ ዓመት ነው…ለአዲሱ ዓመት እንኳን አደረሰህ!›› ትንሽ ፈገግ ብዬ ‹‹አይ! እኔ በፈረንጅ አቆጣጠር አልቆጥርም›› ብዬ ዞር ልል ስል…..‹‹የለም! የለም! የፈረንጆች አይደለም፡፡ ጃንዋሪ የሚለው ሥያሜ ከእኛ ከኢትዮጵያውያን እንደተወሰደ አታውቅም?››(ጭራሽ ተቆጥተው ነው እንዲህ ሚሉኝ)፡፡

"በጥንት ጊዜ ሐበሾች ምንጠራራው ‹ጃል›› እየተባባልን ነው፡፡ እና በጣም ዝነኛ የነበረ አንድ ጦር ወርዋሪ ነበር፡፡ታዲያ ይኼ ሰው ሥሙ በጣም ረዥም ስለነበር ሰው ሁሉ ‹‹ወርዋሪ! ወርዋሪዬ!›› እያለ ነበር የሚጠራው፡፡ በሙሉ ሥሙ ሲጠራ ‹‹ጃል ወርዋሪ!›› ኾነ አትለኝም?! ከዚያ ንግሥት ኤልዛቤት ይኼን ሰው ወደ ኢንግሊዝ ጋብዘውት ከፈረንጅ ወርዋሪዎች ጋር ያወዳድሩታል፡፡ በውድድሩ ወቅት የፈረንጅ ኮሜንታተሮች ‹‹ጃል ወርዋሪ!›› ማለት ከብዷቸው ‹‹ጃን ዋሪ!›› አሉት፡፡ ከዚያ ጊዜ አንሥቶ በየዓመቱ ይኼ ውድድር የሚካሔድበት ወቅት ‹‹ጃንዋሪ›› ተባለ፡፡ የኛ ነው! ያለፈው ወር ‹‹ዲሴምበር›› ራሱ ‹‹ደሴ በር›› ከሚል አማርኛ የተወሰደ ነው፡፡
.
ራሳቸው የፈጠሩትን ተረት እውነት አድርገው ማውራታቸው ስላበሳጨኝ ስልኬ ላይ ተደፍቼ ጆሮ ነፈግኳቸው፡፡ ሰውዬው ግን ኮሮና ኾኑብኝ…‹‹አልተውህም!›› በሚል ዓይነት ወደ ስልኬ ስክሪን ተጠግተው ምን እያየህ ነው አሉኝ፡፡‹‹ክርስቲያኖ ሮናልዶ አል ናስር ለሚባል ክለብ መፈረሙን እያነበብኩ ነው›› አልኳቸው፡፡ ‹‹በነገራችን ላይ…›› ብለው ተረታቸውን ጀመሩ፡፡ ‹‹በነገራችን ላይ አል ናስር የሚባለው ሥም ከእኛ ከኢትዮጵያውያን የተወሰደ ነው! በድሮ ጊዜ ናስር የሚባል አንድ ወጣት ነበር፡፡ይኼ ቡናን ያገኘው ካሊድ ሚባለው ሰው አለ አይደል…የእሱ ታናሽ ወንድም ነው!››
.
ታሪክ መፍጠራቸው ብቻ አይደለም የገረመኝ፡፡ ‹‹የጃል ወርዋሪ አድናቂዎች ሕብረት›› ብለው ማኅበር እያቋቋሙ ነው፡፡ በዚህ ግርምቴ መሐል ሰውዬው ተሰናብተውኝ ከታክሲ ወረዱ፡፡ ከወረዱ ከደቂቃዎች በኋላ ስልኬ እንደሌለ ዐወቅኩ፡፡ ለ‹‹ጃል ወርዋሪ አድናቂዎች ሕብረት›› መቋቋሚያ ስልኬን አዋጣሁ ማለት ነው፡፡
.
የመርሳት በሽታዬን ለአሜሪካና ለቻይና እመኛለሁ፡፡ ዕዳችንን እንዲረሱልን፡፡በርግጥ ለአከራዬም እመኛለሁ፡፡ግን ለሐገሬ በደንብ እመኛለሁ፡፡ሐገሬን ይኼን ያህል ነው የምወዳት፡፡ ግን በሚያሳዝን ሁኔታ ሐገሬ እንደኔ የመርሳት ችግር ላለባቸው ዜጎች አትመችም፡፡ ልክ ለዓይነ ሥውራን መንገድ እንደማይስተካከለው ሁሉ፣ ለዊልቸር ተጠቃሚዎች መግቢያ እንደማይሠራው ሁሉ የመርሳት ችግር ያለባቸውም ዜጎች ይጉላላሉ፡፡
ለምሳሌ እያንዳንዱ ሕንፃዎች ላይ ስክሪን ተገጥሞ መርሳት የሚያጠቃቸው ሰዎች ለምን ወደ ሕንፃው እንደመጡ ቢያስታውስ…..ቀበሌ ላይ ‹‹ወዴት መሔድ ይፈልጋሉ?›› ከሚለው ጽሑፍ አጠገብ ‹‹ወዴት እንደሚሔዱ ማስታወስ ይፈልጋሉ?›› የሚል ጽሑፍ ቢኖር!...ለነገሩ መጀመሪያ ለቀበሌው ሠራተኞች ነው ምን ሊሠሩ እንደመጡ ማስታወስ ያለበት፡፡
.
@huluezih
@huluezih
የማለዳ ማስታወሻ #148
.
አህያ ፀባይ አላት!
አህያ ጉልበት አላት!
አህያ ታዛዥ ናት!
አህያ ቻይ ናት!
.
ነገር ግን. . . ሁሉ ነገር ያላት አህያ የራሴ የምትለው ነገር የላትም። የምትሸከመው ሸክም የራሷ አይደለም። ፀባይዋ ከዱላ አያስጥላትም። ታዛዥነቷ ፍትሕ አያስገኝላትም። እሷ ያላት ሁሉ የአህያውን ባለቤት ብቻ ነው የሚጠቅመው።
.
አህያ ከባለቤቷ የምታገኘው ብቸኛው ነገር ከለላ ነው።የአህያው ባለቤት አህያውን ጅብ እንዳይበላት ይጠብቃታል። ይኼን የሚያደርገው አህያዋ ስለሚገ'ባት ሳይኾን የሚያገኘውን ጥቅም እንዳያጣ ብቻ ነው። አንድ ቀን አህያዋ ጉልበቷ ሲሟጠጥ፣እርጅና ሲጫናት ግን ባለቤቷ ራሱ አውጥቶ ለጅብ ይሠጣታል።
.
አህያ ብታኮርፍ፣አህያ ሐሳብ ብትሠጥ፣ አህያ ቀንና ሌት ብትሠራ፣ ከተሸካሚነት ነጥሎ የሚያያት የለም። መነሻ መድረሻዋ በአለቃዋ ፍላጎት ላይ የተመሠረተ ነው። አህያ የራሷ አለቃ ራሷ መኾን አትችልም። ዕድሜ ዘመኗን የተሸከመችው ሸክም፣ በቃል የማይገለፅ ታታሪነቷ እና ታዛዥነቷ ማምሻ ላይ ከጅብ አያስጥላትም።
.
ብዙዎቻችን እንደዚህች አህያ ነን። የሰው ሸክም ስንሸከም፣ ጅብ ፈርተን ስንጠራ አቤት፣ስንላክ ወዴት እያልን የራሳችን የኾነ አንዳች ነገር ሳይኖረን መጨረሻችን የጅብ ማዕድ ላይ ነው። ለእኛ የማይተርፍ ሸክም ለምን እንሸከማለን? የማያሳድገን አፈር ላይ ለምን እንቀበራለን? ራሳችንን የምናጣበት ሥፍራ ላይ ለምን እንከርማለን? በዚህም በዚያም ከጅብ ካልተረፍን ጉልበት ሳለን ከጅቡ ብንገናኝ አይሻለንም? ጉልበታችን ሲደክም በሌላ አህያ ለምንተካበት ሥፍራ ለብዙ የሚተርፍ ኃይላችንን እናባክናለን? የራሴ የምትለው ምንም ከሌለህ አንተ ማነህ? ማንም!
.
እርግጥ ነው. . .ብዙዎቻችን እንደዚያች አህያ ነን። ነገር ግን አህዮች አይደለንም። ብልጦችን ከነ ነውራቸው አንሸከምም።
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
@huluezih
@huluezih
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
ድሮ እንደ አሁኑ የዴይ ኬር አገልግሎት በከተማው ሳይስፋፋ የዴይ ኬር አገልግሎት እሠጥ እንደነበር ሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ አያውቅም። እኔ ራሴ የዴይ ኬር አገልግሎት በሚያስፈልገኝ ዕድሜ ላይ ሕፃናትን በብሔርና በፖለቲካ አቋማቸው ሳልለይ ሽንት ጨርቅ ከመቀየር ሙዳቸውን እስከመቀየር የሚደርስ አገልግሎት በነፃ እሠጥ ነበር።(በጎ ሰው ነበርኩ. . በግ ሰው ሳልኾን በፊት😔)
.
ይኼ ዐመሌ አብሮኝ አድጎ ዛሬ ከሕፃናት ጋር ሳናወራ በዓይን እንግባባለን። ልጆች የተለየ የፊት ገጽታ ያሣዩኛል። ሕፃናት ገና ሲያዩኝ "He is one of us!" የሚሉ ይመስለኛል። ሰሞኑን ታክሲ ውስጥ አንዲት ወጣት እናት ልጇን ከአሜሪካ በመጣ ማዝያ ደረቷ ላይ ሰቅላው፣ ፊቱ ላይ ደግሞ ለወጉ የሐበሻ ሻርፕ ጣል አድርጋበት አጠገቤ መጥታ ተቀመጠች። ልጁ ጠንቋይ መምሰሉ በእጅጉ አበሳጭቶታል። ዝም ብሎ ያለቅሳል። ልጁን ዝም ለማስባል ያልፈነቀለችው ጡት የለም። ርቦት እንዳልኾነ ሲገባት ምናልባት ዳይፐሩ አቃጥሎት ነው ብላ ከኋላ ያሉትን አራት ትርፍ ሰዎች አስነስታ ዳይፐሩን ቀየረችለት። በርግጥ ልጁ ለደቂቃዎች ለቅሶውን አቆመ። ጠረኑ ግን ሹፌሩን ጨምሮ ሙሉ ተሳፋሪውን አስለቀሰ።
.
ብዙም ሳይቆይ ልጁ ሁለተኛ ዙር ማልቀስ ጀመረ። ይኼ በመንመን ላይ ያለ ክህሎቴን ተጠቅሜ ልጁን ተቀብዬ ማጫወት ጀመርኩ። ወደ እናቱ ዞር ብዬ "ሥሙ ግን ማነው?" አልኳት የልጁ እኔ ላይ መለጠፍ አስግቶኝ።
"አዶናይ በለጠ" ወይ ደሞ "አዶናይ ደረጀ"
"ሁለት አባት ነው ያለው እንዴ?"🙄
"አዎ...መቼም ከሁለቱ አያልፍም!"
"ወራጅ አለ!" ሦስተኛው ተጠርጣሪ ከመኾኔ በፊት ሰላሳ ብር የታክሲ ከፍዬ የሦስት ብር እንደሔድኩ ለመውረድ ተገደድኩ።
.
እና ምን ለማለት ነው . . .ለምን ዴይ ኬር አልከፍትም?
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
@huluezih
@huluezih
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
. . .of the day!😎
መክረውኝ ነበረ!
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
መክረውኝ ነበረ. . .
"ምንም እንኳ ቢራቢሮ. . .
በጉራማይሌ ቀለም ልብን ብትሰቅዝም፣
አትረጋም!
አታርፍም!
የእሷ ልብ አይያዝም!"
.
መክረውኝ ነበረ. . .
"የፈጣሪን ያክል የሰውን ልጅ ብትወደው፣
የክፉ ቀን ንፋስ ነው፣
ከጫንቃህ 'ሚያወርደው!
ዐወቅኩት አትበል. . .
ሲሞላህ፣
ሲደላህ፣
ሲተርፍህ ቀርበኸው፤
የሰው ልጅ ድብቅ ነው፤
ጎብጠህ ካላየኸው!
.
"ራስህን ብቻ እመን፣ልብህን አሰናዳ፤
አያያዝ አያውቅም ልቡ ያልተጎዳ!"
ብለው...መክረውኝ ነበረ. . .
ልቤ መጠርጠሩን ከእነሱ ጀመረ!
.
@huluezih
@huluezih
2025/07/13 18:49:43
Back to Top
HTML Embed Code: