Telegram Web Link
የኦዳ ቡልቱም ዩኒቨርሲቲ ግቢ_ጉባኤ ያስተማራቸዉን ተማሪዎች ብፁዕ አቡነ እንጦንስ  በተገኙበት አስመረቀ

ሰኔ ፲፮/፳፻፲፯ ዓ.ም

የኦዳ ቡልቱም ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ለአራትና አምስት አመታት  ያስተማራቸዉን 225 ተማሪዎችን የምዕራብ ሐረርጌ ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ  በተገኙበት አስመርቋል።


ብፁዕ አቡነ እንጦንስ   ቃለ እግዚአብሔርን መሰረት በማድረግ ፣  ህገ ቤተ ክርስቲያንን በመጠበቅ  ቤተ ክርስቲያንንና ሀገርን ማገልገል ይጠበቅባችኋል በማለት መልእክት አስተላልፈዋል።

አክለውም አገልግሎታችሁም ሁሉ  በፍቅር መሆን አለበት  ያሉ ሲሆን ማኅበረ ቅዱሳን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት  በሚገኙ ወጣቶች ላይ ሥራ እየሠራ በመገኘቱም  አመስግነዋል።

የጭሮ ማእከል ሰብሳቢ ዲ/ን ዳንኤል ሞገስ እንደገለጹት  ማኅበረ ቅዱሳን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚገኙ ተማሪዎች ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ እደሚገኝ ገልጸዋል።

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ እንጦንስ  ለተመራቂ ተማሪዎች የአደራ መስቀል የሰጡ ሲሆን ከተመራቂዎች መካከል ከፍተኛ ነጥብ በማምጣት  በሜዳሊያ ለተመረቁ አራት ተማሪዎች ዕዉቅናና ሽልማት ተበርክቷል።
ደብረ ማርቆስ ማእከል በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ያስተማራቸውን ተማሪዎች አስመረቀ።

ሰኔ ፲፮/፳፻፲፯ ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን ደብረ ማርቆስ ማእከል በመደበኛውና በማታው መርሐ ግብር በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ያስተማራቸውን ተማሪዎች አስመርቋል።

የማእከሉ ሰብሳቢ ድረስ እንዳላማው  ተመራቂ ተማሪዎችን “የድካማችሁን ፍሬ ለማየት ስለበቃችሁ እንኳን ደስ አላችሁ”  ያሉ ሲሆን  የማኅበሩ ርእይ ቤተ ክርስቲያን የመሪነት ሚናዋን ስትወጣ ማየት እንደመሆኑ መጠን  እናንተም የሚጠበቅባችሁን በማድረግ፣ በቤተ ክርስቲያን መዋቅር በመግባት፣ በጉልበታችሁ፣ በገንዘባችሁና በዕውቀታችሁ ማገልገል እንዲሁም  ከማኅበሩ ጋር በጋራ መሥራት ይጠበቅባችኋል ብለዋል።

በመርሐ  ግብሩ ተማሪዎች በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ ሆነው ለመውጣት በግቢ ቆይታቸው የተሻለ ትጋት ለነበራቸውና በዓለማዊ ትምህርታቸው የሜዳሊያ ተሸላሚ ለሆኑ የግቢ ጉባኤ ፍሬዎች በምሥራቅ ጎጃም ሃገረ ስብከት ዋና ጸሐፊ መልአከ ምሕረት መ/ር ይትባረክ ክንዴና በሃገረ ስብከቱ ሕዝብ ግንኙነት ኀላፊ መልአከ ገነት ቆሞስ አባ ፍቅረሥላሴ አማካኝነት ከግቢ ጉባኤው ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።

በመጨረሻም ተመራቂ ተማሪዎች "ኢየሩሳሌም ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ ባላስብሽ ምላሴ ከትናጋየ ጋር ትጣበቅ" ብለው ቃል በመግባት የአደራ መስቀል ተቀብለዋል።
ማኅበረ ቅዱሳን እንጅባራ ማእከል 496 የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን አስመረቀ።

ሰኔ ፲፮/፳፻፲፯ ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን እንጅባራ ማእከል በእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ በመደበኛ እና በኤክስቴንሽን እንዲሁም በተለያዩ  ኮሌጆች በጥምር ግቢ ጉባኤ  ከዓለማዊ ትምህርታቸዉ ጎን ለጎን የቤተክርስቲያን ትምህርት ሲያስተምራቸዉ የነበሩ 496 ተማሪዎችን ሰኔ 15 ቀን 2017 ዓ.ም አስመርቋል።

ከተመራቂዎች መካከል 11 ተማሪዎች ከፍተኛ ዉጤት በማምጣት 10 የሜዳልያና 1 የዋንጫ ተሽላሚ  እንደሚገኙ ተጠቁሟል።

በመርሐ ግብሩ ትምህርተ ወንጌል በመምህራን፣ ወረብና የበገና መዝሙር በተመራቂ ተማሪዎች የቀረበ ሲሆን  ከፍተኛ ዉጤት ላስመዘገቡ ተማሪዎች ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።

በመጨረሻም የእንጅባራ ማእከል ሰበሳቢ በሆኑት በአቶ ይበልጣል አበጀ የማኅበረ ቅዱሳን መልእክት የተላለፈ ሲሆን ለተመራቂ ተማሪዎች የአደራ መስቀል በየኔታ ፍሬዉ ስሜነህ ተሰጥቷል።
ደብረ ታቦር ማእከል  106 የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን ማስመረቁ ተገለጸ፡፡

ሰኔ ፲፮/፳፻፲፯ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን ደብረ ታቦር ማእከል ከ4 እስከ 5 ዓመት ሲያስተምራቸው የነበሩ 106 የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን  ሰኔ 15 ቀን 2017 ዓ.ም ማስመረቁ ተገልጿል።

በማኅበረ ቅዱሳን የደብረ ታቦር ማእከል  ሰብሳቢ የሆኑት ዲ/ን ዶ/ር ለማ ጉልላት  እንደገለጹት ጠቢቡ ሰሎሞን በተግሣጹ ‘’በለሱን የጠበቀ ፍሬውን ይበላል’’ እንዳለ ከብዙ የልፋት ዓመታት በኋላ የድካማችሁን ፍሬ ላያችሁበት ለዚህች ዕለት ልዑል እግዚአብሔር እንኳን በሰላም እና በጤና አደረሳችሁ ብለዋል፡፡

ሰብሳቢው አክለውም ‘’ጢሞቴዎስ ሆይ የተሰጠህን አደራ ጠብቅ‘’ ብሎ አባቱ ቅዱስ ጳውሎስ የመከረውን ምክር ተቀብሎ ለአደራ እንደበቃው እንደ ጢሞቴዎስ እናንተም በዚህ የመከራ ወጀብ መካከል የወላጆቻችሁን ምክር፣ የአገራችሁንና የቤተ ክርስቲያናችሁን አደራ ጠብቃችሁ ለዚህ የምረቃ ክብር በመብቃታችሁ እግዚአብሔርንና እርሱ ያከበራቸውን ሁሉ ልናመሰግን ይገባናል በማለት ተናግረዋል።

አያይዘው ለተመራቂዎቹ ባስተላለፉት መልእክት በቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት መዋቅራት ማለትም በሰበካ ጉባኤ፣ በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በማኅበረ ቅዱሳን መዋቅር በመግባት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በገንዘባችሁ፣ በጉልበታችሁ እና በዕውቀታችሁ በማገልገል፣ በእውነተኛ ትምህርቷ ጸንታችሁ በመኖር በዘር እና በቋንቋ ለተፈተኑ የቤተ ክርስቲያን አካላት አርአያ እንድትሆኑ፣ በመንፈሳዊ ሕይወታችሁ ዕድገት ለማሳየት እንድትተጉ እና ችግሮቿን ለመፍታት ከጎኗ እንድትሆኑ ሲሉ አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም የአደራ መስቀል በመስጠት መርሐ ግብሩ ተጠናቋል፡፡
2025/06/30 04:37:13
Back to Top
HTML Embed Code: