#ሰሙነ_ሕማማት

ከሰኞ እስከ ቅዳሜ ሰሙነ ሕማማት የጾመ ሁዳዴ የመጨረሻው ሳምንት፤ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሕማም የሚታሰብበት፤ ካህናትና ምእመናን በአጸደ ቤተክርስቲያን ተሰብስበው የሕማሙን ነገር የሚያወሳውን ዜማ የሚያዜሙበት፤ ግብረ ሕማም በመባል የሚታወቀውን መጽፍ የሚያነቡበትና የሚሰሙበት፤ በነግህ፣ በሠልስት፣ በስድስት፣ በተሰዓት /ዘጠኝ /ሰዓት፣ በሰርክ /በዐስራ አንድ/ ሰዓት እየመላለሱ የሚሰግዱበትና የሚጸለዩበት ልዩ ሳምንት ነው ከሆሳዕና ማግስት እስከ ትንሳኤ።

በዚህ ሳምንት በተለይ ካህናት ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ ምክንያቱም ጌታችን የደረሰበትን መከራና ስቃይ እንዲሁም የሰው ልጅ ፭ ሺ ፭ መቶ ዘመን በጨለማ ግዞት ይኖር እንደነበር ለማዘከርም ጭምር ነው። የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራና ሕማም በጽኑ እንድናስበው ያስተማሩን ሐዋርያት ናቸው። ለእነርሱም የነገራቸው ደግሞ ራሱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

ሰሙነ ሕማማት የጌታችንን ሕማማት ከማሰብ ጋር በየዕለቱ በርካታ ድርጊቶች መፈጸማቸውን የምናስታውስበት ሳምንት ነው፦

#ሰኞ
#መርገመ_በለስ_የተፈጸመበት_ሰኞ_ይባላል
በዚህ ዕለት ጌታችን ከቢታኒያ ሲወጣ ተራበ ቅጠል ያለባትን በለስ ተመልክቶ ወደ በለሲቱ ቢቀርብ ከቅጠል በቀር ምንም ነገር ባለማግኘቱ “ከአሁን ጀምሮ ለዘላለም ምንም ካንቺ ፍሬ አይበላ” ማር ፲፩፥፲፬ በማለት ስለረገማት መርገመ በለስ የተፈጸመበት ሰኞ ይባላል።

#አንጽሖተ_ቤተ_መቅደስ_ይባላል፡-
ጌታ ወደ ቤተመቅደስ ሄዶ በቤተመቅደሱ የሚሸጡትን እና የሚለውጡትን “ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች” ማቴ ፳፩፥፲፫ በማለት ከቤተመቅደስ ገርፎ አስወጥቷቸዋልና።

#ማክሰኞ
#የጥያቄ_ቀን_ይባላል
ሰኞ ዕለት በቤተመቅደስ ሲሸጡ እና ሲለውጡ የነበሩትን ሁሉ እየገረፈ በማባረሩ ምክንያት ለሰው ልጅ ሹመትንና ስልጣንን የሰጠ ጌታ “በምን ስልጣን ይህንን ታደርጋለህ?” ማቴ ፳፩፥ ፳፫ ተብሎ በፈሪሳውያን ተጠይቋልና የጥያቄ ቀን ይባላል።

#የትምህርት_ቀን_ይባላል፡-
በዚህ ዕለት በቤተመቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረም የትምህርት ቀን ይባላል። ሉቃ ፳፩ ፥፳፰ ፣ ማር ፲፪፥፪።

#ረቡዕ
#ምክረ_አይሁድ_ይባላል
ረቡዕ እለት የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንዳለባቸው የመከሩበትና ውሳኔ ያሳለፉበት ቀን በመሆኑ ምክረ አይሁድ ይባላል። ወቅቱ የፋሲካን በዓል የሚያከብሩበት ቀን በመሆኑ እና ብዙ ህዝብም ጌታን ይከተለው ስለነበር ሁከት እንዳይነሳ ስጋት ነበራቸው ። ነገር ግን ከአስራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ የአስቆሮቱ ይሁዳ አሳልፎ እንደሚሰጣቸው ስለነገራቸው ሉቃ ፳፪፥፩-፮ ጭንቀታቸው ተወግዶ በጌታ መያዝ ተስማምተዋል።

#የመልካም_መዓዛ_ቀንም_ይባላል፡-
ጌታችን በዚህ ዕለት በለምጻሙ በሰምዖን ቤት ተቀምጦ ሳለ መላ ሕይወቷን ለዝሙት አስገዝታ ትኖር የነበረችው ማርያም እንተ እፍረት/ባለሽቶዋ ማርያም/ ዋጋው እጅግ ውድ የሆነ የአልባጥሮስ ሽቱ አምጥታ በራሱ ላይ በማርከፍከፍ ስለቀባቸው ማቴ ፳፮፥፮-፯ የመዓዛ ቀን ይባላል።

#የእንባ_ቀን_ይባላል፡-
ባለሽቱዋ ሴት (ማርያም እንተ እፍረት) ኃጢአቷን ይቅር እንዲላት እየለመነች በእግሩ ስር ተደፍታ በእንባዋ እግሩን አርሳለችና ማር ፲፬፥፱ የእንባ ቀን ይባላል።

#ሐሙስ
#ጸሎተ_ሐሙስ_ይባላል
ጌታችን ለአይሁድ ተላልፎ ከመሰጠቱ በፊት በጌቴሴማኒ የአትክልት ስፍራ ሲጸልይ በማደሩ ማቴ ፳፮፥፴፮ ጸሎተ ሐሙስ ይባላል።ጌታችን የደቀመዛሙርቱን እግር በፍጹም ትህትና ዝቅ ብሎ ያጠበበት ዕለት በመሆኑም ዮሐ ፲፫፥፫-፲፩ ሕጽበተ ሐሙስ ይባላል።

#የምስጢር_ቀን_ይባላል፡-
ከሰባቱ ምስጢራት አንዱ የቅዱስ ቁርባን ምስጢር ማቴ፳፮፥፳፮-፳፱ በዚህ ዕለት ተፈጽሟልና የምስጢር ቀን ይባላል።

#የሐዲስ_ኪዳን_ሐሙስ_ይባላል፡-
መሥዋዕተ ኦሪት /በእንስሳት ደም የሚቀርብ መሥዋዕት/ቀርቶ ለአለም ድኅነት ራሱን ያቀረበበት ቀን በመሆኑ ሉቃ ፳፪፥፳ የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል።

#የነጻነት_ሐሙስ_ይባላል፡-
ለኃጢአትና ለዲያቢሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱን እንዲሁም የሰው ልጅ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለሆነም ዮሐ ፲፭፥ ፲፭ የነጻነት ሐሙስ ይባላል።

#ዓርብ
#የስቅለት_ዓርብ_ይባላል
ጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመልዕልተ መስቀል ላይ ተሰቅሎ የዋለበት ዕለት ነውና ማቴ ፳፯፥፴፭ የስቅለት ዓርብ ይባላል።

#መልካሙ_ዓርብ_ይባላል፡-
ከጌታ ስቅለት በፊት በተለይም በሮማውያን ህግ የወንጀለኛ መቅጫ ምልክት የነበረውን መስቀል ጌታችን በደሙ ቀድሶ የምህረት፣ የሕይወት አርማ፣ የዲያቢሎስ ድል መንሻ ስላደረገው፤ በሞቱ መልካሙን ሕይወት ስላገኘን መልካሙ ዓርብ ይባላል።

#ቅዳሜ
#ቀዳም_ስዑር_ትባላለች
ይህች እለት ከድሮ በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረች ቅዳሜ ይባላል።

#ለምለም_ቅዳሜ_ይባላል፡-
ካህናቱ ለምእመናን ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት በመሆኑም ለምለም ቅዳሜ ይባላል። ምዕመናንም ይህንን ለምለም ቀጤማ እስከ ትንሣኤ ለሊት በራሳቸው ላይ ያስሩታል።

#ቅዱስ_ቅዳሜ_ይባላል፡-
ቅዱስ የሆነው እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ያረፈበት ቀን ሲሆን በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ስራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ በነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዶ ሲኦልን በርብሮ ባዶዋን ሲያስቀራት በዚያ የነበሩትን ነፍሳት የዘላለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለሆነ ቅዱስ ቅዳሜ ይባላል።

(ስምዐ ጽድቅ መጋቢት ፳፻፪ ዓ.ም)
የሰሙነ ሕማማት ሰኞ፡-

#መርገመ_በለስ የተፈጸመበት ዕለት ነው፡

ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሆሣዕና ዕለት ቢታንያ አድሮ በማግሥቱም ከቢታኒያ ሲመጡ ተራበ፡፡ (ማር.11፤11-12) ቅጠል ያላት በለስ ከሩቅ አይቶ ወደ በለሲቱ ቀረበ፤ ነገር ግን ከቅጠል በቀር አንዳች ፍሬ አላገኘባትም፡፡ ከአሁን ጀምሮ ማንም ከአንቺ ፍሬ አይብላ ብሎ ረገማት። በለስ የተባለች ቤተ እስራኤል ናት፤ ፍሬ የተባለች ሃይማኖትና ምግባር ናት፤ ከእስራኤል ፍቅርን፤ ሃይማኖትን፤ ምግባርን ፈለገ አላገኘም፤ እስራኤል (ሕዝበ እግዚአብሔር) መባልን እንጂ፤ ደግ ሰው አይገኝብሽ ብሎ ረገማት፤ በመርገሙ ምክንያት እርሱ ከለያቸው በስተቀር ደግ ሰው ጠፋባት፡፡

በለስ ኦሪት ናት፤ ኦሪትን በዚህ ዓለም ሰፍና ቢያገኛት ኦሪትና ነቢያትን ልሽር አልመጣሁም ልፈጽም እንጂ በማለት ፈጸማት፤ ሕገ ኦሪትን ከመፈጸም በቀር በእርሷ ድኅነት አላደረገባትምና፤ ፍሬ በአንቺ አይሁን አላት፤ ደኅነት በአንቺ አይደረግብሽ ብሏታልና እንደመድረቅ ፈጥና አለፈች፡፡

በለስ ኃጢአት ናት፤ የበለስ ቅጠል ሰፊ እንደሆነች ሁሉ ኃጢአት በዚህ ዓለም ሰፍታ ሰፍና አገኛት፡፡ በለስ ሲበሉት ይጣፍጣል፤ ቆይቶ ግን ይመራል፤ ኃጢአትም ሲሰሩት ደስ ደስ ያሰኛል፤ ኋላ ግን ያሳዝናል፤ ወደ እርሷም ሄዶ ማለትም ከኃጥአን ጋር ዋለ፤ ኃጥእ ከመባል በቀር በአንደበቱ ሐሰት፤ በሰውነቱ ክፋት እንዳልተገኘበት ለማመልከት ፍሬ አላገኘባትም አለ፤ በአንቺ ፍሬ አይገኝ የሚለውም፤ በኃጢአት ፍዳ ተይዞ የሚቀር አይኑር ለማለት ነው፤ ስትረገም ፈጥና መድረቋም፣ በአዳም ምክንያት ያገኘችን ዕዳ በደል በእርሱ ካሣነት እንደጠፋችልን ለመግለጽ ነው፡፡

#አንጽሆተ_ቤተ_መቅደስ የተፈጸመበት ዕለት ነው፦

ጌታችን በለስን ከረገማት በኋላ ወደ ቤተ መቅደስ ሄደ፤ ቤተ መቅደስ፣ ቤተ ጸሎት፣ ቤተ መሥዋዕት መሆኑ ቀርቶ ቤተ ምስያጥ (የንግድ ቤት) ሆኖ ቢያገኘው ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች፤ እናንተ ግን የወንበዶች ዋሻ አደረጋችኋት ብሎ የሚሸጡበትን ሁሉ ገለበጠባቸው፤ ገርፎም አስወጣቸው፤ ይህም የሚያሳየው ማደሪያው ቤቱ የነበርን የአዳም ልጆች ኃጢአት ሰፍኖብን ስንኖር ቢያገኘን ኃጢአታችንን ሁሉ እንዳራቀልን የሚገልጽ ነው፡፡

በዚህ በሰሙነ ሕማማት ካህናትና ምእመናን በቤተክርስቲያን ተገኝተው ወዛቸው ጠብ እስኪል ድረስ በነግህ፤ በሠለስተ፣ በስድስቱ ሰዓት፤ በተሰዓቱ ሰዓትና በሠርክ መላልሰው ሲሰግዱና ሲጸልዩ ይሰነብታሉ፤ በተለይም ካህናት በማንኛውም አገልግሎት ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ፤ ምክንያቱም የደረሰብን መከራ ኀዘኑን እና 5ሺ ከ5መቶ ዘመን የሰው ልጅ በጨለማ ይኖር እንደነበረ ለማዘከር ነው፡፡
የሰሙነ ሕማማት ማክሰኞ

#የጥያቄ_ቀን_ይባላል፡-

ሰኞ ባደረገው አንጽሖተ ቤተመቅደስ ምክንያት፣ ሹመትን ወይም ሥልጣንን ለሰው ልጅ የሰጠ ጌታችን፣ ስለ ሥልጣኑ በጸሐፍት ፈሪሳውያን ተጠይቋልና፤ የጥያቄ ቀን ይባላል፡፡

ጥያቄውም ከምድራውያን ነገሥታት፣ ከሌዋውያን ካህናት ያይደለህ ትምህርት ማስተማር፣ ተዓምራት ማድረግ፣ ገበያ መፍታትን፣ በማን ሥልጣን ታደርጋለህ? ይህንንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ? የሚል ነበር፡፡ /ማቴ. 21፥23-27፣ ማር. 11፥ 7-35፣ ሉቃ.21፥23-27፣ ማር.11፥27-33፣ ሉቃ. 20፥1-8/፤ እርሱም ሲመልስ፤ «እኔም አንድ ነገር እጠይቃችኋለሁ፣ እናንተም ብትነግሩኝ በማን ሥልጣን እነዚህን እዳደርግ እነግራችኋለሁ፡፡ የዮሐንስ ጥምቀት ከወዴት ነበረ፣ ከሰማይ ነውን? ወይስ ከሰዉ? በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ ወይስ በሰው ፈቃድ?» አላቸው፡፡ እነርሱም ከሰማይ ብንል ለምን አልተቀበላችሁትም ይለናል፤ ከሰው ብንል ሕዝቡ ሁሉ ዮሐንስን እንደ አባት ያከብሩታል፣ እንደ መምህርነቱ ይፈሩታልና ሕዝቡን እንፈራለን፤ ተባብለው ከወዴት እንደሆነ አናውቅም ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ አልነግራችሁም አላቸው» ይህንንም መጠየቃቸው እርሱ የሚያደርጋቸውን ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተዉት አልነበረም፣ ልቡናቸው በክፋትና በጥርጥር ስለተሞላ እንጂ፡፡

#የትምህርት_ቀንም_ይባላል፡-

በማቴ. 21፥28፣ ማቴ. 25፥46፣ ማር.12፥2፣ ማር.13፥37፣ ሉቃ. 20፥9፣ ሉቃ. 21፥38 የሚገኙት ትምህርቶች ሁሉም የማክሰኞ ትምህርት ይባላሉ፡፡ በዚህ ዕለት በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረ፣ የትምህርት ቀን ይባላል፡፡ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ከሥጋዊ ነገር ርቆ በዚህ ሰሞን የሃይማኖት ትምህርት ሲማር ሲጠይቅ መሰንበቱም መጽሐፋዊ ሥርዓት ነው፡፡
#የሰሙነ_ሕማማት_ረቡዕ

#ምክረ_አይሁድ_ይባላል
ምክንያቱም የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንደሚገባቸው ምክር ያጠናቀቁበት ቀን ነውና፡፡ በዚህ ምክራቸው ላይ በጣም ትልቅ ጭንቀት ነበር፡፡ ምክንያቱም ወቅቱ የፋሲካ በዓላቸውን የሚያከብሩበት ቀን የተቃረበ በመሆኑ ብዙው ሕዝብም በጌታችን ትምህርት የተማረኩ ተአምራቱንም የሚያደንቁ ስለ ነበር ሁከት እንዳይፈጠር ነው፡፡ በዚህ ጭንቀት ሳሉ ከደቀ መዛሙርቱ አንዱ የአስቆሮቱ ይሁዳ በመካከላቸው በመገኘት የምክራቸው ተባባሪ ሆኖ ጭንቀታቸውን አስወግዶላቸዋል፡፡ (ማቴ. 26÷1-14፣ ማር. 14÷1-2፣ ሉቃ. 22÷1-6) የሐዲስ ኪዳን ካህናትና ምእመናን በዚሁ ዕለት በቤተ ክርስቲያን ተሰብስበው መላ ሰውነታቸውን ለእግዚአብሔር አስገዝተው የሞት ፍርዱን በማሰብና በማልቀስ ሐዋርያት ከጌታችን መያዝ በኋላ በኀዘን በፍርሐት እንደነበሩ እያሰቡ መጻሕፍትን በማንበብ በጾም በጸሎትና በስግደት ተወስነው ይቆዩና ከአሥራ ሁለት ሰዓት በኋላ ወደ ቤታቸው ይሄዳሉ፡፡

#የመልካም_መዓዛ_ቀንም_ይባላል
ምክንያቱም ጌታችን በዚህ ዕለት በቤተ ስምዖን ዘለምጽ ተቀምጦ ሳለ መላ ሕይወቷን ለዝሙት አስገዝታ ትኖር የነበረችው ማርያም እንተ እፍረት (ባለሽቱዋ ማርያም) "ከእንግዲህ ወዲህ በኃጢአት ተበላሽቶ ይኖር የነበረውን ሕይወቴን እንደዚህ መልካም ሽቱ የሚያጣፍጥ ኃጢአትን ይቅር የሚል አምላክ መጣ" ስትል ዋጋው እጅግ በጣም ውድ የሆነ ከሦስት መቶ ዲናር በላይ የሚያወጣ በአልባስጥሮስ ብልቃጥ የተሞላ ሽቱ ይዛ በመሔድ በጠጉሩ (በራሱ) ላይ በማርከፍከፍ ስለቀባችው ረቡዕ የመዓዛ ቀን ይባላል፡፡

#የእንባ_ቀንም_ይባላል
ማርያም እንተ እፍረት በጌታችን እግር ላይ ተደፍታ መላ ኃጢአቷን ይቅር እንዲላት በእንባዋ እግሩን አጥባዋለችና በጠጉሯም በእንባዋ ያጠበችውን እግሩን አብሳዋለችና። (ማቴ. 26÷6-13፣ ማር. 14÷9፣ ዮሐ. 12÷8) ኃጢአትን በማሰብ ማልቀስና ራስን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ለእግዚአብሔር ማቅረብን ከምታስተምረን ማርያም እንተ እፍረት እንባን ለንስሐ ሕይወት ልንጠቀምበት ይገባል፡፡
#የሰሙነ_ህማማት_ሐሙስ

#ጸሎተ_ሐሙስ
በቤተ ክርስቲያን የተለያዩ ስያሜዎች ያሏቸው በርካታ ድርጊቶች የተፈጸሙበት ዕለት ነውና ጸሎተ ሐሙስ ይባላል፡፡ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋን የተዋሐደ አምላክ፣ መሆኑን ለመግለጥና ለአርአያነት ጠላቶቹ መጥተው እስኪይዙት ድረስ ሲጸልይ ያደረበት ነውና ጸሎተ ሐሙስ ተባለ፡፡ (ማቴ. 26፥36-46 ዮሐ.17)

#ሕፅበተ_ሐሙስ_ይባላል፡-
ጌታችን በዚህ ዕለት የደቀመዛሙርቱን እግር በፍጹም ትሕትና ዝቅ ብሎ አጥቧል፡፡ ይህም የሚያሳየው የዓለምን ሁሉ ኃጢአት ለማጠብ የመጣ መሆኑን ነው፡፡ ይህን ለማስታወስ ዛሬም ካህናት በተለይም ሊቃነ ጳጳሳት፣ የደብር አስተዳዳሪዎች፤ «በመካከላችን ተገኝተህ የእኛንና የሕዝብህን ኃጢአት እጠብ እኛም የአንተን አርአያ አንዘነጋም የሌላውን እግር እናጥባለን፤» ሲሉ በቤተ ክርስቲያን የተገኙትን ምእመናንን እግር በወይንና በወይራ ቅጠል ያጥባሉ፡፡

#የምስጢር_ቀን_ይባላል፡-
ከሰባቱ ምስጢራት አንዱ በዚህ ዕለት ተመሥርቷልና፡፡ ይኸውም «ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው፡፡ እንካችሁ ብሉ» ጽዋውንም አንስቶ አመሰገነ «ይህ ስለ እናንተ ነገ በመስቀል የሚፈስ ደሜ ነው ከእርሱም ጠጡ» በማለት፤ እኛ ከእርሱ ጋር፣ እርሱ ከእኛ ጋር አንድ የምንሆንበትን ምስጢር ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ፣ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመሆኑ የተሰጠ ሥያሜ ነው፡፡ በዚህ ዕለት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በንስሐ ታጥቦ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል ይዘጋጃል፡፡

#የሐዲስ_ኪዳን_ሐሙስ_ይባላል፡-
ምክንያቱም መሥዋዕተ ኦሪት ማለትም በእንስሳት ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ፣ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ ነው፡፡ «ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን ሐዲስ ኪዳን ነው፡፡ ከእርሱ ጠጡ» በማለቱ ይታወቃል (ሉቃ. 22፥20) ኪዳን ማለት በሁለት ወገን መካከል የሚደረግ ውል፣ ስምምነት፣ መሐላ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ጌታችን ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ዘለዓለማዊውን ቃል ኪዳን በራሱ ደም የፈጸመበት ዕለት ስለሆነ የሐዲስ ኪዳስ ሐሙስ ተባለ፡፡

#የነጻነት_ሐሙስ_ይባላል፡-
ለኃጢአትና ለዲያብሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱ፣ የሰው ልጅ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡ ጌታችን ስለ ሰው ልጅ ነጻነት ሲናገር «ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም ባርያ ጌታዉ የሚያደርገውን አያውቅምና ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ» በማለት (ዮሐ. 15፥15)፤ ከባርነት የወጣንበት ልጆች የተባልንበትን ቀን የምናስብበት በመሆኑ ሊቃውንቱ የነጻነት ሐሙስ አሉት፡፡ እያንዳንዱ ክርስቲያንም ከኃጢአት ባርነት ርቆ፣ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያወዳጀውን መልካም ሥራ በመሥራት ሕይወቱን መምራት ይኖርባታል፡፡ ባሮች አልላችሁም ተብለናልና፡፡
#የሰሙነ_ሕማማት_ዓርብ

ዕለተ ዓርብ በቤተክርስቲያን ልዩ ቀን ነው፡፡ የማይታመመው ታሞ የዋለበት፣ የወደቁ ከተረሱበት ከትቢያ የሚያነሳ እሱ ሲወድቅ ሲነሳ የዋለበት፣ ሕመምተኞችን የሚፈውስ እሱ ሲያቃስት የዋለበት፣ ከሲኦል የዲያብሎስ ግብር ነፃ የሚያወጣ ሲገረፍ የዋለበት፣ ወልደ እግዚአብሔር ለወዳጆቹ ድኅነት በመስዋዕትነት ሙሽራ የሆነበት የደስታ ቀን፤ አሳዳጅ አሳሪያችን ዲያብሎስ ከነወጥመዱ ድል የተነሳበት ቀን ነው። ከዚህም የተነሳ በቤተክርስቲያን የተለያየ ምስጢራዊ ስያሜዎች ተሰጥቶታል፡፡

#የስቅለት_ዓርብ ይባላል
የዓለም ሁሉ መድኀኒት የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመልዕልተ መስቀል ላይ ተሰቅሎ ለዓለ ድኅነት መስዋዕት ሆኖ የዋለበት ዕለት በመሆኑ የስቅለት ዓርብ ተብሏል። (ማቴ 27፡35)

#መልካሙ_ዓርብ ይባላል
ይህም የሚያስገነዝበን ከስቅለተ ክርስቶስ በፊት ማንም ሰው ሲያጠፋ በመስቀል ተሰቅሎ እንዲሞት ይደረግ ነበር፡፡ በተለይ በሮማውያንና በፈሪሳውያን ሕግ መስቀል የወንጀለኞች መቅጫ ነበረ። በዚህ ዕለት ግን ታሪክን የሚቀይር ነገርን የሚገለብጠው አምላክ የወንጀለኞች መቅጫ ምልክት የነበረውን መስቀል በደሙ ቀድሶ የምህረት ምልክት፣ የሕይወት አርአያ፣ የዲያብሎስ ድል መንሻ ፣ የቤተክርስቲያን ጌጥ፣ የገዳማት ዘውድ ስላደረገውና በዕለተ ዓርብ በሞቱ ሕይወትን ስላገኘን መልካሙ ዓርብ ተብሏል፡፡

በዚህ ዕለትም ጌታ ሁሉ ተፈጸመ ብሎ ቅድስት ነፍሱን ከቅድስት ስጋው በራሱ ፈቃድ ከለየ በኋላ አምላክነቱን ለመግለፅ ተአምራት አሳይቷል፦
1. ፀሐይ ጨልማለች
2. ጨረቃ ደም ሆናለች
3. ከዋክብት ረግፈዋል
4. የቤተ መቅደስ መጋረጃ ከላይ እስከ ታች ተቀዷል
5. ምድር ተናወጣለች (ተንቀጥቅጣለች)
6. መቃብሮች ተከፍተዋል
7. ሙታን ተነስተዋል

በዓመት አንድ ጊዜ የምናገኘው ይህ ዕለት ቀራንዮን የምናስብበት ነገረ መስቀሉን የምናስተውልበት እንጂ ስለምድራዊ ኑሮአችን ስንባክን የምንውልበትና በዋዛ ፈዛዛ ልናሳልፈው አይገባም፡፡
"አባት ሆይ! ቢቻልስ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ"

[ይህ ጽሑፍ የተወሰደው ዓርብ ሌሊት ስድስት ሰዓት ከሚነበበው ከግብረ ሕማማት መጽሐፍ ነው፡፡ የተጻፈውም በጊዜው ለነበሩ መርቅያናውያንና ማኒያውያን ለተባሉ መናፍቃን ምላሽ ሲሆን በእኛ ዘመን ደግሞ በግልጥ
ለሙስሊም፣ ለይሖዋ ምስክሮችና አውቀውም ይሁን ሳያውቁ (ሎቱ ስብሐትና) ክርስቶስን ዝቅ ዝቅ ለሚያደርጉ ለሌሎች መናፍቃን መልስ የሚሆን ድርሳን (Homily) ነው፡፡]
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስቀድሞ “ይህን ረቂቅ ምክርና ጥልቅ ምሥጢር የማያስተውሉ ጌታ እንዲህ በማለቱ ፈርቶ ነው ይሉታል፡፡ ነገር ግን ወዳጆቼ ሆይ! እኛ ደግመን እንነግራችኋለንና አእምሯቸው ስለ ጠፋባቸው ስለ እነርሱ ዘለፋ ዛሬ
በፊታችሁ እንደ ትልልቆች ያይደሉ አእምሮ እንደሌላቸው ሕፃናት ናቸው ብለን
እንተረጕምላችኋለን” በማለት ይጀምራል፡፡ ቀጥሎም እርሱ ይጠይቅና ጌታ የመለሰለትን መልስ ይነግረናል፡፡
ብጹዕ አባታችን እንዲህ በማለት ጥያቄውን ይቀጥላል፡- “አቤቱ ጌታ ሆይ! ስለ
እኛ መከራ ትቀበል ዘንድ ለምን መጣህ? ለምንስ ለመስቀል ደረስክ? ለምን ወደህ በፈቃድህ ፈራህ? ለምን አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ከእኔ ይለፍ አልክ? የተገዢን ባሕርይ ገንዘብ ታደርግ ዘንድ ያስገደደህ ሳይኖር አንተ በፈቃድህ የተዋሐድክ አይደለምን? አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ የሞት ጽዋ ከእኔ ይለፍ ብለህ ለምን ትማልዳለህ? ይህንንም ጽዋ ትጠጣው ዘንድ አልተጋህምን? አንተ ራስህ የምጠመቀው ጥምቀት አለኝ፤ እፈጽመውም ዘንድ እተጋለሁ፤ እስከምጠጣውም ድረስ እታወካለሁ ያልክ አይደለምን? ትጠጣው ዘንድ የተሰጠህን ዛሬ ስለምን አልተጋህም? ለምንስ እምቢ አልክ? አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ከእኔ ይለፍ ለምን አልክ? ስለ እኛ ትሞት ዘንድ እንዳለህ
አላወቅህምን? አንተ የሰው ልጅ ክርስቶስን አብዝተው መከራ ያጸኑበታል፤ ይሰቅሉታል፤ ይገድሉታል፤ በሦስተኛውም ቀን ይነሣል ያልክ አይደለምን? ደቀ መዝሙርህ ጴጥሮስን ይህ በአንተ ላይ እንዲህ ይሆን ዘንድ አይገባም ባለህ
ጊዜ፡- ከኋላዬ ወግድ አንተ ባለጋራ እንቅፋት ሁነህብኛልና የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና ብለህ የገሰጽከው አይደለምን? እርሱን ጴጥሮስን የከለከልከውን እንግዲህ ለምን አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ከእኔ ይለፍ
አልክ? የሚታየውንና የማይታየውን የፈጠርክ አንተ አይደለህምን? ድውያንን በእጅህ ዳስሰህ እንዳዳንህ በሞት ሥጋው የፈረሰውን አልዓዛርን በቃልህ አጽንተህ እንዳስነሣህ፤ የደም ምንጭም የሚፈሣትን በልብስህ ዘርፍ እንዳደረቅክ፤ በአምስት እንጀራ አምስት ሺህ ሰውን እንዳጠገብክ፤ ባሕሩን ነፋሱን ገስጸህ ጸጥ እንደ አደረግህ፤ ሞትንም ደምስሰህ እንደ አጠፋኸው
እናውቃለን፡፡ ዛሬ ሞትን እንደምትፈራ ሁነህ አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይቺ የሞት ጸዋ ከእኔ ትለፍ ለምን ትላለህ? ሞትን የምትፈራ ከሆነ ትንሣኤም ሕይወትም እኔ ነኝ ለምን አልክ? ሕይወትም ትንሣኤም ሞትን አይፈራም፡፡ እንግዲህ የሚቻል
ከሆነ ይቺ የሞት ጽዋ ከእኔ ትለፍ ለምን አልክ?
ገና ሳትፈጥረው አስቀድመህ ሁሉን የምታውቅ ሆይ! አላወቅህምን? ይህ የሞት ጽዋ ከአንተ ማለፉ ይቻል እንደሆነ አይቻልም እንደ ሆነ አስቀድመህ አታውቅምን? ከወልድ በቀር አብን የሚያውቀው የለም እንዴት አልክ? ይህም
ጽዋ ማለፉንና አለማለፉን አታውቅምን? አንተስ ጳውሎስ ከእርሱ የተሠወረ ፍጥረት የለም፤ ሁሉም በፊቱ ፈጽሞ የተገለጠ ነው እንዴት አልክ? …አሁንም እኔ አላውቅም የሚቻል ከሆነ እንግዲህ ጽዋ ከእኔ ይለፈ እንዴት አልክ? በዚህ ቃል
ውስጥ ገና ያልተገለጸ ሥውር ምሥጢር ቢኖርበትም ይህ ነገር አቤቱ ላንተ አይገባህም፡፡ አንተ የአምላክ ልጅ አምላክ ነህ፤ የእግዚአብሔር አብ ቃል ነህ፤ ጥበብና ኃይል ነህ፤ ጸዳልና ብርሃን ነህ፤ የእውነት ፀሐይ ነህ፤ በኃጢአት ለሞትን
ለእኛ የትንሣኤያችንና የሕይወታችን ምንጭ ነህ፡፡”
ብጹዕ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህ “አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ከእኔ ይለፍ” የሚለው ቃል “እንደማይታይና እንደማይመረመር እንደ መለኰትና እንደ ትስብእት ተዋሕዶ ይመስላል፤ ስለዚህም ይህች ምሥጢር ለብዙዎች ጭንቅና
ጠባብ መንገድ ሆነች” በማለት “ኢየሱስ ፈርቶ ይህን ቃል ተናግሮታል” የሚሉትን መናፍቃን ይገስጻል፡፡ ከዚያም ጌታ እንዲህ ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ ለማስረዳት እርሱ በጌታ ተገብቶ (ለንግግር ያመች ዘንድ) ይመልስልናል፡፡ እንዲህም ይላል፡- “ጥበብ ለራስዋ ቤትን ሠራች ተብሎ እንደተጻፈ ራሴ የተዋሐድኩትን ሥጋ እንደፈጠርኩ፤ በሞት የደከመ ሥጋዬን ሕያው አድርጌ ማሥነሣት እንደምችል፡- አይሁድ እናንተ ግብዞች ሰነፎች ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት በሦስተኛው ቀን አነሣዋለሁ ብያቸው ነበርና፤ አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ሞት ከእኔ ይለፍ ያልኩት ሞትን በመፍራትና በመደንገጥ እዳልሆነ ለራስህ እወቅ፤ ተጠንቀቅ፤ ይህ ሥውር የሆነ የምሥጢር ቃል ነው እንጂ፡፡ ይህንንም ልመና እኔ በጥበብ ተናገርኩ፡፡ ይህች ቃል ሰይጣንን ጠብቃ የምታጠምድ ወጥመድ ናት፤ በእነዚህም ቃሎች ሰይጣን አጠምደው ዘንድ አለኝና፡፡
ተአምራትን እንዳደረግሁ፣ በሽተኞችን በእጄ ዳስሼ እንዳዳንኩ፣ አጋንንትም በቃሌ እንዳባረርኩ፣ የሸተተ በድን እንዳስነሣሁ፣ ባሕሩን ነፋሱን እንደገሠፅኩ፣ እነርሱም በመፍራትና በመንቀጥቀጥ እንደታዘዙልኝ ሰይጣን አይቶኝ ነበር፡፡ ያደረግሁትን ይህን ተአምራት አይቶ እኔ የአምላክ ልጅ እንደሆንኩ አውቆ እኔም ብሰቀል እርሱ እንደሚጠፋ ወደ ሲዖልም ብወርድ የብረቱን መቆለፍያ ቀጥቅጬ እንደማጠፋ የብረቱን የናሐሱን መዝጊያ ሰብሬ ሁሉን ወደ ሰማይ እንደማሳርግ ልብ ብሎ አስተውሎ ፈርቶ እንዳሸሽ፣ እንዳይጠፋ፣ በመስቀል የሚደረገው
ምሥጢረ ድኅነት እንዳይቀር እንዳይቋረጥ ምን ላድርግ? አልኩ፡፡ ስለዚህ ራሴን ብልህ እንዳጠመደው ወጥመድ አድርጌ ፈርቶ ከሞት እንደሚደነግጥም አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ከእኔ ይለፍ አልኩ፡፡ በእነዚህም የትሕትና ቃሎቼ ዕሩቅ ብእሲ (ሰው ብቻ) እመስለዋለሁ፤ ምሥጢረ ድኅነት የሚፈጸምበት መስቀል በምድር መካከል ይተከል ዘንድ ይቸኩላል፤ በእኔ ላይ የሚጠበብብኝ እየመሰለው እኔ ግን ለሰው ሁሉ ድኅነት ከእርሱ የሚደረግብኝ ሁሉ እታገሥ ዘንድ
አለኝ፡፡እርሱ የመጀመርያውን ሰው አዳምን ያጠፋው ዘንድ እጅግ ተተንኩሎ ተጠብቦበት ነበር፡፡ በተንኰል አነጋገር አዳምን እንደ ተጠበበበት እንግዲህ እኔ ሁሉን ለማዳን በይበልጥ ለምን አልጠበብበት? እንደዚሁ እኔም እርሱ ባመጣው ተንኰል ላጠምደው ትሕትናን በተመሉ ቃሎች ተጠበብኩበት፡፡ በመለኰታዊ
አነጋገርም ለሰይጣን አልተገለጽኩለትም፤ አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ሞት ከእኔ ይለፍ አልኩ እንጂ፡፡
ዓሣ አጥማጅ መቃጥኑን በመብል ሸፍኖ ወደ ባሕር ውስጥ በሚጥለው ጊዜ ሲስበው ለዓሣው እንደሚያስጐመጀው አንድ ጊዜም ሊጐርሰው ጕረሮውን እንደሚከፍት እንዲሁም እኔ መለኰቴን መብል አድርጌ ጣልኩለት፡፡ ለዘላለሙ
በማትመረመር ተዋሕዶ በሥጋዬ ውስጥ ያለ የመለኰት መቃጥንን ጣልኩለት፡፡
በሚያጠምድበት ላይ የተደረገው የሚጐረስ ትል (ወላፍ) ካልተንቀሳቀሰ ዓሣው መንጠቆውን ለመጕረስ አይጐመጅም፡፡ ስለዚህ ሥጋዬን እንደሚጐረስ (ወላፍ) ትል አድርጌ አሳየሁት፡፡ እኔ ሰው ያይደለሁ ትል ነኝ አልኩ፡፡ ይህን ሰምቶ በዚህ
በሥጋዬ ውስጥ ያለችን መቃጥን ሩጦ ሂዶ ይጐርስ ዘንድ፡፡እኔም በመቃጥኔ እስበዋለሁ፤ በኢዮብ መጽሐፍ ከይሲን በወጥመድ ትስበዋለህ ተብሎ የተጻፈውን ይፈጸም ዘንድ፡፡እኔም ፈርቶ እንደሚሸሽ ሰው ሆኜ ነፍሴ እስከ ሞት..
ደርሳ አዘነች፤ ተከዘች፤ አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ሞት ከእኔ ይለፍ አልኩ፡፡ ይህም
ሰይጣን እነዚህን የትሕትና ቃሎች ሰምቶ በአሳቡ ይህ እንደማንም ሰው ነው፤ እውጠዋለሁ (እቆራኘዋለሁ) አለ፡፡ አባቶች ነብያትን እነ አብርሃምን፣ ይሥሐቅን፣ ያዕቆብን እንደዋጥኳቸው (እንደተቆራኘኋቸው) ይህንንም እውጠዋለሁ
(እቆራኘዋለሁ) እንደሚፈራ ሰው አየዋለሁና አለ፡፡ እነሆ እንግዲህ እንደ ዕሩቅ ብእሲ መስየው ዋጠኝ (እቆራኘዋለሁ አለ)፤ ቃጣ፤ ግን በሆዱ አምላክ ሆኜ አገኘኝ፡፡ እርሱም እየተገዛ በሥጋ የተሸለመ (ሥጋን የተዋሐደ) መለኰቴን ዋጠ (ሊቆራኝ ቃጣ)፤ ግን የማይጠፋ የመለኰት ፍም ሆኖ አገኘው፤ ነገር ግን ውስጡን አቃጠለው፤ እንደ ተጻፈ ለዓለም እሳት አምጥቻለሁና፡፡
አባት ሆይ ይቺ ጽዋ ሞት ከእኔ ትለፍ ብዬ የተናገርኩት የተሳለ የመለኰትን ሰይፍ
እንደማላሳየው ሆኜ የበግ ጠቦት ያየ ጅብ (ዲያብሎስ) እንዳይሸሽ እንደ በግ ጠቦት ሆንኩለት፡፡ እንደ በግ ጠቦትም ይውጠኛል፤ ሦስት አፍ በሆነ ሰይፍ ከውስጡ ታረደ፤ ተቆረጠ፤ ሰላምን ልሰጥ አልመጣሁምና ሰይፍን እንጂ ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ አባት ሆይ የሚቻል ከሆነ ይህ ጽዋ ከእኔ ይለፍ ያልኩት አነጋገሬ በጠቦት በተመሰለው ሥጋዬ ሁሉን የሚጠብቅ መለኰቴን ሸሸግሁት፤ በምናገረው ጊዜ ጅብ (ዲያብሎስ) እንዳይሸሽ ጠባቂውን መለኰቴን እገልጸው ዘንድ አልወደድኩም፤ ጠባቂ እንደሌለው በግና ረዳት እንደሌለው ሰው ሆንኩ ተብሎ እንደተጻፈ ጠባቂ እንደሌለው በግ ሆንኩ፡፡ እንደ ጠቦት ይውጠኛል፤
ከእረኛውም የተነሣ በውስጡ በመስቀል ፍላጻዎች ይነደፋል፡፡ የሰናፍጭ ቅንጣት ያላምጣል፤ በውስጡም የምታጠርሰውና የምትመረው መለኰታዊ ግብር ሆና አገኛት፡፡ እንደ ዕሩቅ ብእሲ ያላምጠኛል፤ በውስጡም ጥርሶቹን የምትሰብር የጸናሁ ዓለት ሆኜ ያገኘኛል፤ ከዛሬ ጀምሮ ሰውን እንዳያላምጥ ያውቅ ዘንድ፤ አምላክ ጥርሶቹን በአፉ ውስጥ ይሰብራልና ያለውም ጽሑፍ ደረሰ ተፈጸመ፡፡…
በዋጠኝ ጊዜ ወድያውኑ ታውቆኛልና፡፡ ስለ እኔ ባየ ጊዜ ፀሐይ ፈጽሞ ጠፋ፤ ቀኑ ሌሊት ሆነ፡፡ ያን ጊዜም መረረው፤ በበታቹ ሲዖል በተገናኘችው ጊዜ መረረች (ደነገጠች) የሚል ጽሑፍ አለና፡፡…
ደግሞ ይህን ቃል ለሚሰሙ ሁሉ እንደ ደካማ እንደ ሆንኩ ይመስላቸዋል፤ የእግዚአብሔር ድካም ከሰው እንዲበረታ አላወቁምና፡፡ እኔ ጽዋውን በጠጣሁ ጊዜ እርሱ ሰይጣን ሰክሮ እንዲጠወልግ ወገኖች ነቅተው አስተዋዮች እንዲሆን አላስተዋሉም፡፡ የትሕትና ቃሎቼን በሚሰማ ጊዜ ደስ ይሏል፤ በሚውጠኝ ጊዜ ግን አፉ ሲሰነጠቅ፣ መቃብሮች ሲከፈቱ፣ ሙታኖች ሲነሡ ያያል፡፡ ያን ጊዜ በሰማይ ተድላ ደስታ ይሆናል፤ ያን ጊዜ ሰይጣን ያዝናል፤ ስለ እነዚህ የትሕትና ቃሎቼ
በእነርሱ በመጠመዱ ያጸጸታል፤ በአጠመዳት ወጥመድም እንደተጠመደ ያውቃል፡፡ ጕድጓድ ቆፈረ፤ በቆፈረውም ጕድጓድ ይወድቃል፡፡ ደክሞ የሠራው ክፉ ሥራው በራሱ ይመለሳል፤ የሠራትም ዐመፅ በራሱ ላይ ትወርዳለች ተብሎ
እንደተጻፈ፡፡
ለእኔ ያስተከለው መስቀል የሰርግ ቤት እንደ ሆነች፤ ለእርሱ መሰቀያ መጥፊያ እንደሆነው ለእኔ ደስ መሰኛ ለእርሱ መሞቻ እንደሆነው አላወቀም…
አባት ሆይ ሰምተኸኛልና አመሰግነሃለሁ፤ ሁል ጊዜም በየጊዜው እንደምትሰማኝ አውቃለሁ እያልኩ ስናገር ልምሾ የሆነ ሰይጣን በሰማኝ ጊዜ አወቀ፡፡
አሁንም የሞት ጽዋ ታልፍ ዘንድ ጸልያለሁና ይህች ጽዋ ታልፍ ዘንድ ስለ ሞት የተደረገ ጸሎት እንዳይመስልህ፤ ከዚያም ወደ መስቀል መውጣትን ቸል ያልኩእንዳይመስልህ፤ ሞትም እንድትመጣልኝ ስጸልይ አባቴ የእኔ ፈቃድ ያይደለ
የአንተ ፈቃድ ይሁን አልኩ፡፡ ነፍሴን ከሥጋዬ ለይቼ ላኖራት ደግሞም አዋሕጄ ላስነሣት ሥልጣን እያለኝ በሞት ሥልጣን ወደ መያዝ ደረስኩ፡፡ መለኮቴን በነገር ሽፋን ሰውሬ የእኔ ፈቃድ ያይደለ ያንተ ያባቴ ፈቃድ ይሁን ብዬ እንደ ሰው
ተናገርኩ፡፡ ዕውረ ልቡና ሰይጣን ግን የእኔ ፈቃድና የአባቴ ፈቃድ አንድ እንደሆነ አያውቅም፤ የአባቴ የሆነ ሁሉ የእኔ ነው ብዬ እንደተናገርኩ አያውቅም፡፡ ዳግመኛም እኔና አብ አንድ ነን እንዳልኩ፤ እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ
እንዳለ ታውቁ ዘንድ አልኩ ያልኩትን፤ አብ በማንም በማን አይፈርድም ፍርዱን ሁሉ ለልጁ ሰጠው እንጂ ብዬ እንደተናገርኩ፤ አብን እንደሚያከብሩት ወልድን ያከብሩት ዘንድ ይገባል ወልድን የማያከብረው ሁሉ የላከው አብን አያከብረውም እንዳልኩ፤ አባቴ ሁሉን ሰጠኝ እንዳልኩ ረስቶታል፡፡ እኔ ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኬ መጣሁ፤ ሙሴ በምድረበዳ የነሐሱን እባብ እንደ ሰቀለው የሰው ልጅ ክርስቶስ እንዲሁ ይሰቀል ዘንድ አለው ያመነበት ሁሉ እንዳይጠፋ ለዘላለም ሕያው ሆኖ ይኖራል እንጂ እንዳልኩ፤ …የስንዴ ቅንጣት ይሰቀላል፤ በሚውጣትም
ጊዜ ትንታ ሆና ያገኛታል ያልኩትን ቃል ረስቶታል፤ እርሱም በዚች ኃይል ታንቆ ይጠፋል ተሳልቄበታለሁና፡፡
”ብጹዕ የሆነው አባታችን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “ነገር እንዳናበዛባችሁ ዝንጋዔ ልብንም እንዳናመጣባችሁ እናጠቃልለው” ይልና፡- “ጌታችን በአጋንንቶቹና በሰይጣን ዲያብሎስ ላይ ተሣለቀባቸው፤ ይህም “በችሎታዬ እሠራለሁ፤
በጥበቤም የአሕዛብን ግንብ አፍርሼ ፍጥረቱን ሁሉ እንደ ጫጩቶች እጨብጠዋለሁ፤ እንደ ወደቀ እንቁላልም አንሥቼ እወስደዋለሁ፤ ተከራክሮ የሚነጥቀኝ የለም” በማለት በትዕቢት ቃሉን ከፍ አድርጎ በመናገር የሚታበይ ሰነፍ ሰይጣንን እንቡዝ ልብ ያደርጓል፡፡ ሰይጣንም ከአጋንንቶቹ ጋራ መሣለቅያ ይሆን ዘንድ አለው፤ እንደዚሁ የሚመኩ ሁሉ አአምሮ እንደሌላቸው ሕፃናት ይሆናሉና፡፡ ስለዚህም የሚሠሩትን አያውቁም ነበር፤ አውቀውስ ቢሆን የክብር ባለቤት ክርስቶስን ባልሰቀሉትም ነበር፡፡…
ስለዚህ አስቀድመን እንደነገርናችሁ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፈራ አይምሰላችሁ፤ ይቺ ጽዋ ሞት ከእርሱ ታልፍ ዘንድ ስለ ጽዋ ሞት አልጸለየም” በማለት ከማር የጣፈጠውን ትምህርቱ ይጨርሳል፡፡
ከአባቱ ጋር ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ለክርስቶስ ምስጋና እናቀርባለን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡
"+"የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት"+"

በጲላጦስ ዘመን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት፤ ትንቢቱም ይፈጸም ዘንድ መከራን ተቀበለ፤ ጲላጦስ በ፫ ሰዓት ይሰቅል ዘንድ ሲፈርድበትም፤ ‹‹መስቀሉንም ተሸክሞ በዕብራይስጥ ጎልጎታ ወደ ተባለው ቀራንዮ ወደሚባል ቦታ ወጣ›› (ዮሐ.፲፱፥፲፯) የራስ ቅል ስፍራ ቀራንዮ-ጎልጎታ አዳም ዐጽም የተቀበረበት ቦታ ነበር፡፡ በዚያም የአዳም መቃብር የሆነች ዋሻ አለች፤ የመስቀሉንም እንጨት በዚያ በምድር መካከል አይሁዶች ተከሉት፡፡
የአዳም አጽም ቀድሞ ከአዳም ትውልዶች ሲተላለፍ ከኖኅ ደርሷል፤ ኖኅም ወደ መርከብ እንደታቦት አስገብቶት በኋላ መልከጼዴቅ ቀብሮታል፡፡ ጌታችንም ከአዳም የራስ ቅል በላይ ሊያድነው መስቀል ተሸከሞ ተንገላታ፤ አይሁዶችም የቀራንዮን ዳገት እየገረፉ ከወደ ጫፍ አደረሱት፤ሁለቱንም እንጨት አመሳቅለው ዐይኖቹ እያዩ እጆቹንና እግሮቹን ቸነከሩት፤ በዕለተ ዐርብ ቀትር ፮ ሰዓት ላይም ተሰቀለ፡፡
ጌታችን የተሰቀለበት ሰዓት ፀሐይ በሰማይ መካከል በሆነ ጊዜ የጥላ መታየት በሚጠፋበት፤ ወደ ሰው ተረከዝም በሚገባበት ነበር፡፤ ከ፮ ሰዓት ጀምሮ እስከ ፱ ምድር ጨለመች፤ ፀሐይ፤ ጨረቃ፤ ከዋክብት ብርሃናቸውን ከለከሉ፤ ምክንያቱም የፈጣሪያቸውን ዕርቃኑን ይሸፍኑ ዘንድ ነበር፤ ‹‹ቀትርም በሆነ ጊዜ ፀሐይ ጨለመ፤ምድርም ሁሉ እስከ ፱ ሰዓት ድረስ ጨለማ ሆነ›› ማር.፲፭፥፴፫፡፡
በ፱ ሰዓት በቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ ስለ ጌታችን በሰማይ ፫ት በምድር ፬ት ተአምራትን ሲያደርጉ አይቶ በእውነት አምላክ እንደሆነ አመነ፤ ‹‹አቤቱ በመንግሥት በመጣህ ጊዜ አስበኝ›› ባለ ጊዜ በግራ የተሰቀለው ዳክርስ ግን ‹‹እስቲ አምላክ ከሆነ እራሱን ያድን›› ብሎ ተዘባበተ፡፡ ፍያታዊ ዘየማን ግን ‹‹እኛስ በበደላችን ነው የተሰቀልን፤ እርሱ ግን ምንም ሳይበድል ነው፤ እንዴት በአምላክ ላይ ክፉ ነገርን ትናገራለህ›› ብሎ ገሰጸው ፤ፍያታዊ ዘየማንም ጌታችን በጌትነት መንበረ ጸባዖት(መንግሥት) ሆኖ ታየው፤እርሱንም አይቶ ‹‹ተዘከረኒ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ›› ቢለው ጌታችን ‹‹ዮም ትሄሉ ምስሌየ ውስተ ገነት›› ብሎ ደመ ማኅተሙን ሰጥቶታል፤ በኋላ ገነት ሲገባም መልአኩ አንተ ማነህ፤ አዳም ነህ፤ አብርሃም ወይንስ ይስሐቅ? እያለ ጠይቆታል፡፡
መልአኩ ሳያውቅ የጠየቀ ሆኖ አይደለም፤እንኳን በመጨረሻ የጸደቀ ፍያታዊ ቀርቶ በዘመናቸው የኖሩ ጻድቃንን ያውቃል፤ አዳምን ፤አብርሃምን፤ ይስሐቅን ሳያውቅ ቀርቶም አይደለም፡፡ ነገር ግን ሊቃውንት ሲተረጉሙት ‹‹አዳም ነህ›› ማለቱ የአዳምን ያህል ሥራ አለህን? አብርሃም ነህ ሲለው ደግሞ የአብርሃምን ያህል ሥራ አለህን? ለማለት ነው፡፡ ‹‹በጌታችን ኢየሱስ መስቀል አጠገብም እናቱ፤ የእናቱም እኅት፤ የቀለዮጳም ሚስት ማርያም፤መግደላዊትም ማርያም ቆመው ነበር›› (ዮሐ.፲፱፥፳፭) ‹‹እነርሱም ማርያም መግደላዊት፤ የታናሹ ያዕቆብ እና የዮሳ እናት ማርያም፤ የዘብዴዎስም የልጆቹ እናት ሰሎሜም ነበሩ›› (ማር.፲፭፥፵)፡፡
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከተናገራቸው የአደራ ቃላት አንዱ እመቤታችን ለቅዱስ ዮሐንስ መሰጠቷ ነው፤ ለወዳጁ ዮሐንስ ከስጦታ ሁሉ ስጦታ የሆነች እናቱን እናት ትሁንህ ብሎ ሰጠው፤‹‹እነኋት እናትህ፤ እነሆ ልጅሽ›› (ዮሐ.፲፱፥፳፮)፡፡ በኋላ ወደ ቤቱ ወስዷት ፲፭ ዓመት ኖራለች፤ በዚህም የዮሐንስ ቤት በአቢዳራ ቤት ተመስላለች፤እመቤታችንም የሚያጽናናትን ወዳጁ ዮሐንስን ሰጥቷታል፡፡
የእመቤታችን ለዮሐንስ መሰጠት ቀድሞ በሙሴ አንጻር ጽላቷ ለሕዝቡ ሁሉ እንደተሰጠች፤በዮሐንስ አንጻርም እመቤታችን ለሁላችን ለምእመናን ተሰጥታናለች፡፡
፱ ሰዓት በሆነ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ፤አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ›› ብሎ በታላቅ ቃል ተናገረ፤ (ማር.፲፭፥፴፬)፡፡ በዚያም ቆመው የነበሩት ‹‹ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ፤ ›› የሚለውን ድምጽ የሰሙ ኤልያስን ይጣራል እያሉ አሙት፤ ክህደትንም ተናገሩ፤ ያንጊዜ አንዱ ወታደር ሮጦ ሆምጣጤ የመላበት ዕቃ ተቀምጦ ነበርና በሰፍነግ መልቶ በሂሶጽም አድርጎ በአፉ ውስጥ ጨመረለት፡፡
በመስቀል ላይ ሳለ ጌታችን ኢየሱስም በታላቅ ድምፅ ሁሉ ተፈጸመ አለ፤ (ማር. ፲፭፥፴፯)፤ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በፈቃዱ ለየ፡፡
አይሁድም እኒህ ሰዎች እንደተሰቀሉ አይደሩ፤ ምክንያቱም ቀጣዩ ቀን ሰንበት ነውና ጭናቸውን ሰብረው ያወርዷቸው ዘንድ ጲላጦስን ጠየቁት፤ እርሱም ፈቀደላቸው፡፡ የሁለቱ ወንበዴዎች፤ ፈያታይ ዘየማንንና ፈያታይ ዘጸጋምን አብረው አወረዷቸው፤ ከጌታችን ዘንድ ቢቀርቡ ፈጽሞ ሞቶ አገኙት፤ በዚህም ጭኑን ሳይሰብሩት ቀሩ፡፡ ሌላው ግን የተመሰለው ምሳሌ ፍጻሜ ሲያገኝ ነው፤ የፋሲካውን በግ ‹‹አጥንቱን ከእርሱ አትስበሩ›› የተባለው አሁን ተፈጸመ፤ (በዘፀ.፲፪፥፲)፡፡ ከጭፍሮቹም አንዱ ቀኝ ጎኑን በጦር ወጋው እንዲል ከወታደሮቹ አንዱ የሆነው ለንጊኖስ የጌታችንን ጎን ቢወጋው ትኩስ ደምና ቀዝቃዛ ውኃ ፈሷል፡፡ ለንጊኖስ ጥንተ ታሪኩ አንድ ዐይኑ የጠፋ ሲሆን ጌታችን በተሰቀለበት ጊዜ ወደ ጫካ ሸሽቶ ርቆ ነበር፤ ምክንያቱም ከዚህ ሰው ሞት አልተባበርም በማለት ነው፡፡ አመሻሹ ላይ የአይሁድ አለቆች ሲመለሱ ከመንገድ አገኘቱ፤ ስለምን ከመሢሑ ሞት አልተባበርክም አሉት? እርሱም ምንም ስላላገኘሁበት አላቸው፡፡ ከዚያም በኋላ እንደሕጋቸው እንደሚቀጡት ቢነግሩት እየሮጠ ሔዶ የጌታችንን ጎን ሲወጋው ደሙ በዐይኑ ላይ ፈሰሰ፤ ያን ጊዜ ዐይኑ በራለት፤ ከጌታችን ጎን የፈሰሰው ደም እንደ ለ ቅርጽ ሆኖ በሁለት ወገን ደምና ውኃ ሆነ፡፡ ከጌታችንም የፈሰሰውን ትኩስ ደም መላእክት በጽዋ ቀድተው በዓለም ላይ ረጩት፤ ይህ መሠረት ሆኖ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታነጸው የጌታችን ደም የነጠበበት ነው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹አሁንም በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ›› ያለው (ሐዋ.፳፥፳፰)፡፡ ከጌታ ጎን የፈሰሰው ውኃ ደግሞ ምእመናን የልጅነት ጥምቀትን ስንጠመቅ ውኃውን ካህኑ ሲባርከው ማየ ገቦ ይሆናል፡፡
ቅዳሜ ከቀድሞው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረችው ቅዳሜ ትባላለች፤ ይህ ቅዳሜ ጌታችን ሥጋው በመቃብር የዋለበት በመሆኑ እኛም እንደ ሐዋርያት የትንሣኤውን ብርሃን ሳናይ እህል አንቀምስም በማለት በጾም ስለምናሳልፈው ነው፡፡
ቄጠማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤው ሌሊት በራሳቸው ላይ ያሰሩታል፤ የቄጠማው አመጣጥና ምሥጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፤ ምድር በጥፋት ውኃ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሠረችው ቄጠማ ይዛ በመግባት ነው፡፡ ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ኃጢአት ጠፋ፤
በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነፃነት ተሰበከና ታወጀ በማለት ካህናቱ ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበስሩበታል፡፡
በዚህች ቅድስት ቅዳሜ፤ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ፤ በዚህች ዕለት ከሥራው ሁሉ ያረፈባት ዕለት ናት፡፡ ጌታችን የተቀበረበትም ስፍራ ለተሰቀለበት ቦታ አቅራቢያ ነበር፤ ዮሴፍ ከኒቆዲሞስ ጋር ሆኖ ጌታችንን እንደፍጡር
በሐዘንና በልቅሶ ሲገንዙት የጌታችን ዐይኖች ተገለጡ ‹‹እንደፍጡር ትገንዙኛላችሁን? በሉ እንዲህ እያላችሁ ገንዙኝ፤ ቅዱስ እግዚአብሔር፤
ቅዱስ ኃያል፤ ቅዱስ ሕያው›› አላቸው፡፡
"+" ቀዳም ሥዑር (የተሻረች ቅዳሜ) "+"

ቀዳም ስዑር ለምለም ቅዳሜ፣ ቅዱስ ቅዳሜ
ትባላለች፡፡ ቀዳም ሥዑር መባሉ ከወትሮው
ዕለታት በተለየ ይህችኛዋ ዕለት በጾም ስለምትታሰብ የተሻረች ቅዳሜ እንላታለን፡፡
ለምለም ቅዳሜ መባሏም ካህናቱ የምሥራች
አብሳሪ የሆነውን ቄጤማ ይዘው ወደ
ምእመናን ቤት ስለሚሔዱ ለምለም ቅዳሜ
ትባላለች፡፡ ቅዱስ ቅዳሜ መባሉም ቅዱስ
እግዚአብሔር አምላካችን በጥንተ ተፈጥሮ
ሃያ ሁለቱን ስነ ፍጥረታት የሚታዩትንና
የማይታዩትን፣ በእግር የሚሄዱትን እና በክንፍ
የሚበሩትን፣ በባሕር የሚዋኙትንና
በመጨረሻም ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ
የፈጠረው በዕለተ ዐርብ ሲሆን ቅዳሜ ዕለት
ደግሞ ከሥራው ያረፈበት ዕለት ናት፡፡ በዘመነ
ሐዲስም የማዳን ሥራውን አከናውኖ በከርሰ
መቃብር አድሮ በአካለ ነፍስም ሲዖልን
በርብሮ ተግዘው የነበሩትን ነፍሳት ያወጣበት
ዕለት በመሆኑ ቅዱስ /ልዩ/ ቅዳሜ ተብላ
ተሰይማለች፡፡
ዕለቱ ዝርዘር አድርገን ስንመለከተውም ይህች
የመጀመሪያው ቅዳሜ ለእግዚአብሔር
የዕረፍት ዕለት ናት፤ እግዚአብሔር ሥነ
ፍጥረትን ፈጥሮ ስላረፈባት ሰንበት ዐባይ
(ታላቋ ሰንበት) ትባላለች (ዘፍ. 1፡3) ይህችን
ታላቋን ሰንበትም እንዲያከብሯት ሕዝበ
እግዚአብሔር የተባሉ እስራኤላውያን ታዘው
ነበር፡፡
ዕለተ ቀዳሚት (ሰንበት ዐባይ) በዘመነ
ሐዲስም የተለየ የድኅነት ሥራ
ተከናውኖባታል፡፡ ጥንት ሥነ ፍጥረትን
በመፍጠር ዕረፍት እንደተደረገባት ሁሉ
በሐዲስ ኪዳንም አዳምን ለማዳን ሕማምና
ሞት የተቀበለው ቸሩ አምላክ በሐዲስ
መቃብር አርፎባታል (ማቴ. 27፡61)፡፡
በዚህች ዕለት ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ
ክርስቶስ በከርሰ መቃብር ዐርፎ የዋለባት
ዕለት በመሆኗ በምሥጢር ከሰንበት ዐባይ ጋር
ትገናኛለች፡፡ ቀዳም ስዑር (የተሻረች ቅዳሜ)
የተሰኘችውም በዓመት አንድ ቀን
ስለምትጾም ነው፡፡ እናቱ ቅድስት ድንግል
ማርያም፣ ወዳጆቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታ
ተላልፎ ከተሰጠበት ዕለት አንስተው ብርሃነ
ትንሣኤውን እስከሚያዩ ድረስ እህል ውኃ
በአፋቸው አልዞረም፡፡ ይመኩበትና ተስፋ
ያደርጉት የነበረ መምህራቸው በመቃብር
ስላረፈ ዕለቷን ነገረ ሞቱን በማሰብና
ትንሣኤውን በመናፈቅ በጾም አክብረዋታል፡፡
ከቅዱሳን ሐዋርያት ሲወርድ ሲወራረድ
በመጣው ትውፊት መሠረት ቅዱሳን
ሐዋርያት በሐዘን፣ በጾምና በጸሎት ዕለቷን
እንዳከበሯት ክርስቲኖችም የተቻላቸው
ከዓርብ ጀምረው በማክፈል፣ አሊያም ዓርብ
ማታ በልተው ቅዳሜን በመጾም የጌታን
ትንሣኤን ያከብራሉ፡፡
ቅዳሜ ጧት ምእመናኑና ካህናቱ ወደ ቤተ
ክርስቲን ይሰበሰባሉ፡፡ የጧቱ ጸሎት ሲፈጸም
”ገብረ ሰላመ በመስቀሉ” በመስቀሉ ሰላምን
መሠረተ፣ ሰላምን ፈጠረ፤ የምሥራች እየተባለ
በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰበው ሁሉ ቄጠማ
ይሰጣል፡፡ የምሥራች ምልክት ነው፡፡
ምእመናኑም እየሰነጠቁ በራሳቸው
ያስሩታል፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ላልመጡት
ምእመናንም ካህናት በየሰበካቸው ልብሰ
ተክህኖ ለብሰው መስቀልና ቃጭል ይዘው
ቄጠማውን የምሥራች እያሉ ያድላሉ፡፡
የዚህ የቄጠማው ታሪክ መነሻው የኖኅ ዘመን
ታሪክ ነው፡፡ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን
በጻድቁ ኖኅ ዘመን የነበሩ ሰዎች በማየ አይህ
ከጠፉ በኋላ የውኃውን መጉደል
እንድትመለከት የተላከች ርግብ የምሥራች
ምልክት የሆነ ለምለም ቄጠማ በአፏ ይዛ
ተመልሳለች፡፡ በዚህም የውኃው መጉደል፣
የቅጣቱ ዘመን ማለፍ ተረጋግጧል (ዘፍ. 9፡
1-29)፡፡
ቄጠማ ለጥፋት ውኃ መድረቅ የምሥራች
መንገሪያ እንደሆነው ሁሉ አሁንም በክርስቶስ
ሞት መተ ነፍስ ከሰው ልጆች ተወገደ ስትል
ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ ቄጠማ ታድላለች፡፡
ምእመናንም የምሥራች ተምሳሌት የሆነውን
ቄጠማ በግንባራቸው ያስሩታል፣ በጣታቸው
ቀለበት ያደርጉታል፡፡
የክርስቶስ ተከታዮች ሁሉ ከጨለማ
ወደሚደነቅ ብርሃን፣ ከሚያቃጥለው ዋዕየ
ሲዖል (የሲዖል ቃጠሎ) ወደ ልምላሜ ገነት፣
ጥንተ ማኅደራቸው መመለሳቸውን በዚህ
አኳኋን እየገለጡ በዓለ ትንሣኤን በቅድስት
ቤተ ክርስቲያን ያከብራሉ፡፡
ወንድሞቼና እህቶቼ እነሆ ስለ ቀዳም ስዑር
(የተሻረች ቅዳሜ) በማስመልከት ከስምዐ
ተዋሕዶ የስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ዘሰሙነ
ሕማማት፣ ማኅበረ ቅዱሳን፣ ሚያዝያ 2004፣
አዲስ አበባ ያገኘሁትን ስብከት
እንደሚከተለው ላካፍላችሁ፡፡
ቅዳሜ ቀዳም ሥዑር ይባላል፡፡ በዚች ዕለች
ከድሮው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ
በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረችው
ቅዳሜ ትባላለች፡፡
የማትጾመዋ ቅዳሜ ስለምትጾም ስዑር /
የተሻረች/ ተብላለች በዓል መሻርን
አይመለከትም በቀዳም ሥዑር ሌሊት ሥርዓቱ
የሚጀመረው በመኀልየ ሰሎሞን ምንባብ
ነው፡፡ ማኀሌቱም እዝሉ እየተቃኘ
እየተመጠነ፣ እየተዘመመ እየተመረገደ
እየተጸፋ ያድራል፡፡ ጥዋት አቡን መዋሥዕት
ውዳሴ ማርያም ዜማ ተደርሶ ወለመልአከ
ሕይወትሰ ሰቀልዎ በሚለው ሰላም
ይጠናቀቃል፡፡በዚህ ዕለት ልብሰ ተክህኖ የለበሱ
ካህናትና ዲያቆናት ቄጤማ ተሸክመው ቃጭል
ሲያቃጨሉ መታየታቸው ዕለተ ትንሣኤውን
ለሚናፍቅ ምእመን ትልቅ ብስራት ነው፡፡
ለምለም ቅዳሜ፡- ካህናቱ ለምእመናን
ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት ስለሆነ
በዚህ ተሰይሟል፡፡ ቀጤማውንም ምእመናን
እስከ ትንሣኤ ሌሊት በራሳቸው ላይ
ያስሩታል፡፡
በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ
ቃጭል /ቃለዓዋዲ/ እየመቱ ገብረ ሰላመ
በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ የሚለውን
ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ
ሰላምን እንደሰጠን እና ትንሣኤውንም
እንደገለጠልን በማብሰር፤ ቄጤማውን
ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡
ምእመናኑም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት
የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡
ቄጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም
አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ
የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ ያሠሩበትን
ድርጊት የሚያስታውስ ነው፡፡
የቀጤማው አመጣጥና ምስጢርም
ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡
ምድር በማየ አይኅ /በጥፋት ውኃ/ በጠፋችበት
ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ
የውኃውን መጉደል ያበሰረችው ቀጤማ ይዛ
በመግባት ነው፡፡
ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች የኃጢአት
ውኃ ጐደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋ በክርስቶስ
ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ ታወጀ በማለት
ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን
ያበሥሩበታል፡፡
ቅዱስ ቅዳሜ ይባላል፡፡ ቅዱስ ቅዳሜ መባሉ
ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ
ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ በዚህ ቀን
ከሥራው ሁሉ ያረፈበት ነው፡፡ በዘመነ ሐዲስ
ደግሞ የማዳን ሥራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው
በመቃብር ሲያርፍ፣ በነፍሱ ሲዖልን በርብሮ
ባዶዋን አስቀርቷታል፡፡ በዚያ ለነበሩት
ነፍሳትም የዘለዓለም ዕረፍትን ያወረሰበት
ዕለት ስለሆነ ከሌሎቹ ዕለታት የተለየ ዕለት
ለማለት ቅዱስ ቅዳሜ ተብሏል፡፡
ምእመናን ሆይ፣ በአጠቃላይ ሥርዓተ
ሕማሙን፤ ሰሙነ ሕማማት ብለው የተለየ
ሥርዓት አውጥተው አባቶቻችን ተግተው
ያቆዩልንን ሥርዓተ መላእክት ልንጠብቀውም
ልንጠቀምበት ይገባል፡፡ የዕለታቱን ክብርና
ስያሜ ከማወቅና ከመረዳት ጋር በዕለታቱ
የታዘዙትን ሃየማኖታዊ ግዴታዎችን መወጣት
ከሁላችንም ይጠበቃል፡፡
ያብጽሐነ ያብጽሕክሙ እግዚአብሔር በሰላም
ከበዓሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን፣ አሜን፡፡
††† በትንሣኤ በዓል እርድ መከናወን ያለበት መቼ ነው? †††
ብዙ ሰዎች የቀዳም ስዑር ምሽት ዶሮ፣ በግ፣....ወዘተ ያርዳሉ። በዚህ ዕለት ማረድ በልማድ ተያይዞ የመጣ እንጂ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንም ሆነ ትውፊቱ አያዝም። በቀዳም ስዑር ለምን እንደሚያርዱም ሲጠየቁ "ለበዓሉ ቅድመ ዝግጅት ለማድረግ፣ ሌሊት ከቤተ ክርስቲያን አስቀድሰው ሲመለሱ ለመግደፍና ነዳያንን ለማፈሰክ ነው" በማለት ይመልሳሉ። ሊቃውንቱ ሲያትቱ ግን ዝግጅት የሚያስፈልጋቸው የሚባሉት በባህርያቸው የሞቱ ለምንላቸው ምግቦች ነው። ማለትም እንጀራ፣ ዳቦ...ወዘተ። ምክንያቱም እነዚህን ለማዘጋጀት ብዙ ጊዜ የሚፈልግ ነውና። እንስሳት ግን ደመ ነፍስ ናችው። እንስሳን ለማረድ ዝግጅት አይጠይቅም፤ ወዲያው የሚታረዱ ናቸው። ነዳያንን ማስፈሰክ ለተባለውም ተንሥኣ እሙታን ከሚባልበት ከመንፈቀ ሌሊት በኋላ ተሠርቶ የሚደርስ ነው።
በዓሉን በማስመልከት ባለን ዐቅም እርድ የምናርደው የደስታ፣ የምሥራች መግለጫ ነው። ደስታችንን የምንገልጸው ደግሞ ጌታችን ከተነሣ በኋላ ነው። የትንሣኤያችን የምሥራች የተሰበከልን በጌታችን ትንሳኤ ምክንያት ነውና። ስለዚህ <<ወተንሥአ እሙታን፤ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤>> ተብሎ ዐዋጅ ሳይታወጅ መታረድ የለበትም። በቀዳም ስዑር ማረድ ዐዋጅ ሳይታወጅ ከማረዳችንም በላይ የትንሣኤን በዓል አላከበርንም እንደ ማለት ነው። የጌታችን ትንሣኤ የምሥራች እስከ ሚነገርበት ሰዓት ድረስ ስመ ሥላሴ አይጠራም። ታድያ በቅዳሜ ምሽት በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ሳይባል፣ በመስቀል ሳይባረክ ማረድ በዘመነ ኦሪት እንደታረደ ፣/እንደተሠዋ/ ነው የሚቆጠረው። ምክንያቱም "ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን" አልተባለምና።
እንደ ሊቃውንቱ አገላለጽ ሌሊት ከቅዳሴ መልስ በየቤታችን ልንመገበው የሚገባ ከጥሉላት ምግቦች ርቀን ከመቆየታችን አንጻር ጤንነታችንን የማይጎዳ ማር፣ ተልባ፣ ወተት በእርጎ ተደርጎ ነው የሚበላው። እርድ መፈጸም ያለበት ጠዋት ወይም ደግሞ ከሌሊቱ 6፡00 በኋላ ነው። ያኔ መስቀል ይዞራልና። አንዳንድ ሰዎች ሲናገሩ ቀዳም ስዑር ጾም መሆኑን አምናለሁ። ነገር ግን ከምሽቱ 11፡00 /ከዋዜማው/ ጀምሮ ወደ ሚቀጥለው ቀን /እሑድ/ ስለሚቆጠር ማረድ ይቻላል ይላሉ። ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ለዚህ ሲመልሱ፦ ፍትሐ ነገሥቱ በአቀጸ ጾም ላይ "ክብርት በምትሆን በ፵ ጾም በመጀመሪያው ሱባኤ እስከ 12 ሰዓት፣ ከቅድስት ጀምሮ እስከ ኒቆዲሞስ ዓርብ እስከ 11 ሰዓት፣ በሰሙነ ሕማማት እስከ 13 ሰዓት /ከሌሊቱ አንድ ሰዓት ጨምሮ ወይም እስከ ፀአተ ኮከብ -ኮከብ በሰማይ መልቶ እስኪታይ/ ጹሙ" ይላል። ቅዱሳት መጻሕፍትም ለጾም ማድላት እንዳለብን ይመክሩናል። ከምሽቱ 11፡00 ጀምሮ ወደ ሚቀጥለው ቀን /ወደ ማግሥቱ/ ነው የሚቆጠረው የሚባለው ለምስጋና ሲሆን ነው። ለምሳሌ፦ በዋዜማ ምሥጋና ለነገ የበዓሉ መዳረሻ /መግለጫ/ እንዲሆን ማለት ነው። ጾም ግን ወዲያውኑ በተግባር /በድርጊት/ የሚፈጸም ነው። ወደ ማግሥቱ ይቆጠራል አንልም፤ ምክንያቱም ጾም ተግባር ነውና።
በተጨማሪም ቅዱሳት መጻሕፍትም የሚያዙት "የሚቻላችሁ ከሆነ ከዚህ አብልጣችሁ ጹሙ" ነው የሚሉን። ይልቁንም የጾማችንን ጊዜ ከዕለት ወደ ዕለት ከፍ እያደረግን ልንሄድ ይገባናል እንጂ በየምክንያቱ ከነበርንበት ልንቀንስ አይገባም። የሰው ልጅ በረከት፣ ስርየተ ኃጢአት፣ ድኅነት፣ የዘላለምን ሕይወት ለማግኘት ራሱን ለሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መገዛት ማስገዛት ካልቻለ ከፈጣሪው ጋር አንድነት አይኖረውም። ፈቃደ ነፍስን ለመፈጸም የምታበረታታ ደገኛ ሕግ ደግሞ ጾም ናት።" በአጠቃላይ በቀዳም ስዑር ማረድ የጾም ክፍል በኾነው ሰዓት ከማረዳችን በተጨማሪ የትንሣኤን ምሥራች አይሰብክም። ምክንያቱም ጌታችን እስኪነሣ ድረስ በኅዘን ነው ያለነው፤ እንደ ሥርዓቱ ከሆነ ሲታረድ ካህኑ ቢላዋውን ይባርክለታል ፥ አራጁ ያርዳል፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሙስና መቃብር አጥፍቶ ተነሥቷልና፤ "ክርስቶስ ተንሥኣ እሙታን" ተብሎ ዐዋጅ ተነግሯልና። ስለሆነም በቀዳም ስዑር ምሽት ማረድ በልማድ የመጣ እንጂ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት አይደለም።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
➬ † እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላምና በፍቅር አደረሳችሁ በመላው አለም ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን የእምነቱ ተከታዮች በሙሉ †
† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †
† # ብርሃነ_ትንሣኤ †
➬†#የዓለማት_ሁሉ_ፈጣሪ_የዘለዓለም_አምላክ_ወልድ_ዋሕድ_ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በዚህች ዕለት መግነዝ ፍቱልኝ : መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል በባሕርይ ኃይሉና ሥልጣኑ ተነስቷልና እንኳን ደስ አለን::
††† ከዚህ በኋላ ለ50 ቀናት እንዲህ እያልን ሰላምታ እንለዋወጣለን:-
††† ክርስቶስ ተንስአ እሙታን!
¤በዐቢይ ኃይል ወስልጣን!
††† አሠሮ ለሰይጣን!
¤አግዐዞ ለአዳም!
††† ሰላም!
¤እምይእዜሰ!
††† ኮነ!
¤ፍሥሐ ወሰላም!
በእርግጥም አምላካችን በሞቱ ሞትን ገድሎ : በትንሣኤው ሕይወትን አድሎናልና ደስታ ይገባናል:: መድኃኔ ዓለም በኅቱም ድንግልና እንደ ተወለደ በኅቱም መቃብር ተነስቷል:: ለደቀ መዛሙርቱም "ሰላም ለእናንተ ይሁን" ሲል
በዝግ ደጅ ገብቷል::
በዕለተ ትንሣኤው የመጀመሪያውን ደስታ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም
ተካፍላለች:: የእርሷን ያህል በሃዘን የተጐዳ የለምና:: ቀጥለው ቅዱሳት አንስት
እነ ማርያም መግደላዊት ትንሣኤውን አይተዋል:: ሰብከዋልም::
††† በዚሕች ቀን ማዘን አይገባም:: በትንሣኤው የደነገጡና የታወኩ የአጋንንትና የአይሁድ ወገኖች ብቻ ናቸውና::
††† አምላካችን ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ከትንሣኤው በረከት አይለየን:: በዓሉንም የሰላም : የፍቅርና የበረከት ያድርግልን::
††† የጌታችን በጐ ምሕረቱ በሁላችን ትደርብን::
††† "ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ? ተነስቷል እንጂ በዚህ
የለም:: 'የሰው ልጅ በኃጢአተኞች እጅ አልፎ ሊሰጥና ሊሰቀል: በሦስተኛውም ቀን ሊነሣ ግድ ነው' እያለ ገና በገሊላ ሳለ ለእናንተ እንደተናገረ አስቡ::" †††
(ሉቃ. ፳፬፥፭-፰)
††† "አሁን ግን ክርስቶስ ላንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተነስቷል:: ሞት በሰው በኩል ስለ መጣ ትንሣኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኗልና:: ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ እንዲሁ ሁሉ በክርስቶስ ደግሞ ሕያዋን ይሆናሉና::" †††
(፩ቆሮ. ፲፭፥፳)
††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
ሰኔ 12 - እንኳን ለመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
ሰኔ 12-የቅዱስ ላሊበላ በዓለ ዕረፍት ሲሆን የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤል ደግሞ ዕጥፍ ድርብ በዓሉ ነው፡፡
==SHARE
(በገብረሥላሴ)
ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚበር ንሥረ አርያም የሚባል ውዳሴው እንደ ማር የጣፈጠ ንዑድ ክቡር የሆነ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል አፎምያን ያዳነበት ዕለት ነው፡፡ ዳገመኛም ይህች ዕለት የባሕራንን የሞት ደብዳቤ ቀዶ ለታላቅ ክብር ያበቃባት ዕለት ናት፡፡ ዳግመኛም ይህች ዕለት ቅዱስ እለ እስክንድሮስ አንድን ቤተ ጣዖት አፍርሶ ከቦታው ላይ ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ታቦተ ሚካኤልን አግብቶ በዓሉን በደስታ በሐሴት አሳለፈባት ዕለት ናት፡፡
ዳግመኛም ዛሬ የጻድቁ የቅዱስ ላሊበላ በዓለ ዕረፍት ነው፡፡ ቅዱስ ላሊበላ ጌታችን የጠጣውን መራራ ሐሞት በማሰብ ሁልጊዜ ዓርብ ዓርብ ኮሶ ይጠጣ ነበር፡፡ ቅዱስ ገብርኤል ላሊበላን ኢየሩሳሌም ወስዶት በዚያ ያሉ ቅዱሳን መካናትን ሁሉ አሳይቶ አሳልሞታል፡፡ ወደ ሰማይም ነጥቆ ወስዶ ሰባቱ ሰማያትን ያሳየው ሲሆን በጌታችን ፊትም አቅርቦት አስባርኮታል፡፡ ጌታችንም ‹‹ሕዝቦቼ የመከራና የሥቃዬን ቦታ ለማየት ኢየሩሳሌም በመሔድ በመንገድ እየቀሩ ስለሆነ አሁን ግን አንተ በሀገረ ሮሀ ኢየሩሳሌምን ትሠራለህ›› በማለት የቤተ መቅደሶቹን አሠራር በዝርዝር ነግሮታል፡፡ ከነገሠም በኋላ ሱባኤ ገብቶ ቤተመቅደስ የሚሠራበትን ቦታ በጸሎት ሲጠይቅ ዛሬ ቤተ ማርያም ካለችበት ቦታ ላይ የብርሃን አምደ ወርቅ ተተክሎ መላእክት ሲወጡና ሲወርዱ ስላየ ቦታው እግዚአብሔር የፈቀደው መሆኑን አውቆ ሥራውን ጀመረ፡፡ ጌታችን ቀድሞ ‹‹እኔ ራሴ ነኝ እንጂ ቤተ መቅደሶቹን የምትሠራቸው አንተ አይደለህም፣ ነገር ግን በአንተ ስም እንዲጠራ ስለፈቀድኩ ሄደህ ሥራ›› ብሎ እንዳዘዘው ቅዱስ ገድሉ ይናገራል፡፡ ላሊበላ ዓሥሩን ቤተመቅደሶች ሲሠራ እርሱ አንድ ስንዝር ሠርቶ እንደሆነ ሌሊቱን ዓሥር ስንዝር ሆኖ ያገኘው ነበር፡፡ ቀንም ሲሠራ ቅዱሳን መላእክት በማይታወቁ ሰዎች አምሳል ሆነው ይራዱት ነበር፡፡ በመጨረሻም ጌታችን በገሃድ ተገልጦለት በቦታው ላይ እጅግ አስገራሚ ቃልኪዳኖችን ሰጥቶታል፡፡
በመሆኑም ይህንን ጣፋጭ የቅዱስ ላሊበላን ሙሉ ገድል በኀላ ላይ እመለስበታለሁ አሁን ግን ውዳሴው እንደ ማር የጣፈጠ ንዑድ ክቡር የሆነ የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን ተአምራት ወደመናገር እንመለስ፡፡
ሚካኤል ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ሚ-መኑ' ካ-ከመ' ኤል- አምላክ ማለት ሲሆን በአንድነት ሲነበብ መኑ ከመ አምላክ (እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው) ማለት ነው፡፡ አንድም ለእግዚአብሔር አሸናፊ ድል አድራጊ የቸርነትና የርህራሄ መገኛ መዝገብ ማለት ነው፡፡
ይህ ታላቅ መልአክ ዮሐንስ ወንጌላዊ በራዕዩ ‹‹በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙትን ሰባቱን መላእክት አየሁ›› ብሎ ከተናገረላቸው መላእክት ውስጥ የሚመደብ ሲሆን የሰባቱም ሊቃነ መላእክት አለቃ እንዲሆን እግዚአብሔር መርጦ ሹሞታል፡፡ ይህ ታላቅ መልአክ ያደረጋቸው የሠራቸው እጅግ ብዙ የሆኑ ተአምራት አሉት፡፡
ስለዚህ ስለ ታላቁ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ክብር፤ ጠባቂነትና አማላጅነት ከአባቶቻቸው የተማሩትን በኑሮአቸው ያዩትን አባቶቻችን ጽፈዋል፡፡ ስለ ቅዱስ ሚካኤል ከጻፉት አባቶች መካከል የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያክል፡-
+ ዮሐንስ አፈወርቅ
+ ኤዎስጣቴዎስ ዘአንፆኪያ
+ ቅዱስ መቃርዮስ
+ ቅዱስ ያሬድ
+ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
+ የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አባዲማቴዎስ ናቸው፡፡ እኛም የአባቶቻችንን አንደበት አንደበታችን አድርገን በኅዳር 12 ክቡር ገናና የሆነ ቅዱስ ሚካኤል ካደረጋቸውና ከሠራቸው ብዙ ተአምራት ውስጥ የተወሰኑትን በመልአኩ ተረዳኢነት እንዲህ ብለን እንናገራለን አንጽፋለን፡፡
ጥንተ ነገሩ እንዲህ ነው፡- ንግስት ክሌዎፓትራ ‹‹ሳተርን›› ለሚባለው ጣዖት የሠራችው ቤተ ጣዖት በእስክንድርያ ነበር፡፡ ይህ ቤተ ጣዖት እስከ እስክንድርያው ፓትርያርክ እለ እስክንድሮስ /312 - 326/ ዘመን ድረስ ነበር፡፡ እለ እስክንድሮስ ሊያጠፋው ሲነሣ ሕዝቡ ከልቡ ገና የአምልኮ ጣዖት ስላልጣፋ "18 ፓትርያርኮች ያልነኩትን አንተ ለምን ታፈርስብናለህ?" ብለው ተቃወሙት፡፡ እለ እስክንድሮስም ሕዝቡን መክሮና አስተምሮ የሳተርን በዓል ይውልበት በነበረው ዕለት የቅዱስ ሚካኤልን በዓል እንዲያከብሩ አውጆ ቤተ ጣዖቱንም በቅዱስ ሚካኤል ስም ሰይሞ ቤተክርስቲያን አደረገው፡፡
ሕዝቡ በየዓመቱ መሥዋዕት እየሠው ተረፈ መሥዋዕቱን እየተመገቡ እየዘፈኑ እያጨበጨቡ ያከብሩ ነበር፡፡ ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ቁስጠንጢኖስ "አብያተ ጣዖታት ይዘጉ አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ" ብሎ ካወጀ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት እለ እስክንድሮስ ቤተ ጣዖቱን አፍርሶ ከቦታው ላይ ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ታቦተ ሚካኤልን አግብቶ በዓሉን በደስታ በሐሴት አሳለፉት፡፡ እለ እስክንድሮስም ሕዝቡን የጣዖቱን በዓል ተው "ይህን የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል አክብሩ" ብሎ በየዓመቱ በዚህ ቀን በዓል እንዲሆን ሥርዓት ሠራላቸው፡፡ ይህንንም የቅዱስ ሚካኤልን በዓል ከሚያከብሩ ምእመናንን አንዱ የባሕራን አባት ነበር፡፡
እርሱም እግዚአብሔርን እጅግ አድርጐ የሚፈራ ወር በገባ በየዐሥራ ሁለቱ ቀን የቅዱስ ሚካኤልን ዝክሩን የሚዘክርና ይልቁንም በኅዳር ዓሥራ ሁለትና በሰኔ ዓሥራ ሁለት ቀን በታላቅ ክብር የሚያከብር አንድ ሰው ነበር። ለዚህ እግዚአብሔርን ለሚፈራ ሰውም ርኅራኄ የሌለው በእርሱም ላይ ጥላቻ ያደረበት አንድ በለጸጋ ጐረቤት ነበረው፡፡ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል በሚያከብርበት ጊዜ ሁሉ ይዘብትበት ይሳለቅበት ነበር። ይህ እግዚአብሔርን ለሚፈራ ሰውዬ በዚህ ዓይነት በጐ ሥራ ብዙ ጊዜ ከኖረ በኋላ ከዚህ ዓለም ድካም ያርፍ ዘንድ የሞቱ ጊዜ ቀረበ። ሚስቱንም ጠርቶ "በጐ ስራ ከመሥራት ለድኃ ከመመጽወት ቸል አትበይ የቅዱስ ሚካኤልንም በዓል በየወሩ ከማክበር አትቦዝኝ ይልቁንም በኅዳር ዓሥራ ሁለትና በሰኔ ዓሥራ ሁለት ቀን ከፍ ባለ ሥነ ሥርዓት እንድታከብሪ አደራ እልሻለው" አላት፡፡ በሚሞትበትም ጊዜ ሚስቱ ፀንሳ ነበር። ይህም ደገኛ ሰው በሰላም ዐረፈና ፍጹም መንግሥተ ሰማያትን ወረሰ።
ከዚህም በኋላ ሚስቱ የመውለጃዋ ጊዜ ተቃርቦ ነበርና ምጥ ይዟት በታላቅ ጭንቅ ላይ እንዳለች "አንተ የእግዚአብሔር መልአክ ሆይ በእኔ ላይ ይቅርታን አውርድ ከዝህ ከደረሰብኝም ጭንቅ ይገላግለኝ ዘንድ ስለኔ እግዚአብሔርን ለምንልኝ አንተ ከእግዚአብሔር ዘንድ ታላቅ ባለሟልነት ተሰጥቶሃልና" እያለች ለመነች። ይህንንም በምትልበት ጊዜ ያለችበት ቤት በብርሃን ተመላ ከጭንቋም ዳነችና መልኩ በጣም ያማረ ልጅ ወለደች። የእግዚአብሔር መልእክተኛ ቅዱስ ሚካኤልም ከሰማይ ወርዶ ያን ሕፃን ባረከውና "ቸርነት ርኅራኄ የሌለውን የዚህን ባለጸጋ ገንዘብና ሀብት እርሻውንም ሁሉ ይህ ሕፃን እንዲወርስ እግዚአብሔር አዟል" አለ። ያን ጊዜ ያ ባለጸጋ በሴትዮዋ ቤት መስኮት አጠገብ ሆኖ ሁኔታውን ሁሉ ይመለከት ነበርና ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ልቡ በታላቅ ኅዘን ተነካ፤ ሕፃኑንም የሚገድልበትን ምክንያት ይፈልግ ጀመር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር በቅዱስ ሚካኤል ጸሎት ብላቴናውን ከክፉ ነገር ሁሉ ይጠብቀው ነበር።
ብላቴናውም ዓሥር ዓመት በሆነው ጊዜ እናቱ በጣም ችግር ፀናባት፡፡ በዚህን ጊዜ እምነት የጐደለው ያ ባለጸጋ "አንቺ ችግረኛ ስለሆንሽ ይላከኝ ያገለግለኝ ዘንድ ልጅሽን ስጭኝና ምግቡንና ልብሱን ምንም ሳላጐድል ተንከባክቤ አኖረዋለው ለአንቺም ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሻለው" አላት። ይህንንም ባላት ጊዜ ስለ ችግሯ በጣም በመደሰት ልጅዋን ሰጠችውና ሃያውን ወቄት ወርቅ ተቀበለች፡፡ ብላቴናውንም በወሰደ ጊዜ እንግዲህ ሃሳቤ ሁሉ ዛሬ ተፈጸመልኝ እያለ በጣም ደስታ ተሰማው፡፡ ከዚህ በኋላ በልጅ ቁመት ልክ ሳጥን አሠርቶ ሕፃኑን በሣጥኑ ውስጥ አግብቶ በላዩ ላይ ቆለፈበትና ሣጥኑን ወስዶ ከባሕር ጨመረው፤ እንዲሁም የሣጥኑን ቁልፍ መክፈቻ አብሮ ወረወረው። ነገር ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ ያ ሣጥን ሳይሰጥም በባሕሩ ላይ እየተንሳፈፈ ከዚያች አገር ርቃ ወደምትገኝ የባሕር ወደብ ደረሰ።
በባሕሩ አካባቢ በጎቹን አሰማርቶ የሚጠብቅ አንድ ሰው ነበርና ያንን ሣጥን ባየው ጊዜ ከባሕሩ አወጣውና ወደ ቤቱ ወሰደው። እቤቱም በደረሰ ጊዜ "ይህን ሣጥን በምን እከፍተዋለሁ?" እያለ ሲያወጣ ሲያወርድ ተመልሶ ወደ ባሕሩ ይሄድ ዘንድ እግዚአብሔር አሳሰበው፤ በሄደም ጊዜ አንድ ዓሣ የሚያጠምድ ሰው አገኘና ዓሣ አጥማጁን "በኔ ስም መረብህን ወደ በሕር ጣልና የተሠገረው ዓሣ ለኔ ይሆናል ዋጋውን ግን እከፍልሃለው" አለው፡፡ ዓሣ አሥጋሪውም እንደ ተነጋገሩት መረብን ከባሕር ቢጥል ታላቅ ዓሣ ተያዘና ለሰውየው ሰጥቶት ዋጋውን ተቀበለ። እሱም ያንን ዓሣ ከቤተሰቦቹ ጋር ጠብሶ ይበላ ዘንድ በችኮላ ወደ ቤቱ ሄደና ያሣውን ሆድ ቢሰነጥቀው የዚያን የሣጥን ቁልፍ መክፈቻ አገኘ፡፡ በዚያን ጊዜ ይህ መክፈቻ የዚህ ሣጥን ቁልፍ መክፈቻ መሆን አለበት ሲል አሰበና ቁልፉን ለመክፈት ቢሞክር ወለል ብሎ ተከፈተ። በዚህም እየተደነቀ ሳለ ሣጥኑን ቢከፍተው ያ ባለ ፀጋ ሊገድለው ያሰበውን ሕፃን በሣጥኑ ውስጥ አገኘው። ባየውም ጊዜ እጅግ ተደስቶ በባሕር ውስጥ ስላገኘው ስሙን "ባሕራን" ብሎ ሰየመውና እንደ ልጁ አድርጐ ይንከባከበው ዘንድ ወሰነ፡፡
ከባሕራን ሀገር የበግ ጠባቂው አገር የዓሥር ቀን ጐዳና የሚያስኬድ ርቀት ነበረው። ከብዙ ዓመታት በኋላ ያ ባለ ጸጋ ሰው ለንግድ ከሀገሩ ወጣ፡፡ በጉዞውም ላይ ሳለ ፀሐይ ስትገባ ከዚያ የበግ ጠባቂው ዘንድ ደረሰ። በግ ጠባቂውንም "ወንድሜ ሆይ ባንተ ዘንድ የማድርበት ቢኖር ታሳድረኝ ዘንድ እለምንሃለው፣ ኪራዩንም እከፍልሃለው" ብሎ ጠየቀውና ያ በግ ጠባቂ ወደ ቤቱ አስገባው። ባለጸጋውም ገብቶ ጥቂት ካረፈ በኋላ በግ ጠባቂው ያን ብላቴና ባሕራን ብሎ ሲጠራው በሰማ ጊዜ "ልጅህ ነውን?" ብሎ ጠየቀው። በግ ጠባቂውም "አዎን ይህ አሁን ጐልማሳ ሆኖ የምታየው ወጣት ገና ሕፃን ሆኖ ሳለ በሣጥን ተከቶ ከባሕር ውስጥ ተጥሎ አግኝቼው ወስጄ አሳድጌዋለሁና ልጄ ነው" አለው። ባለጸጋውም በባሕር ውስጥ የጣለው ሕፃን መሆኑንም ስላወቀ ይህንን ነገር በሰማ ጊዜ ፈጽሞ ደነገጠ፤ ይገድለውም ዘንድ ፈለገ፡፡
በበነጋውም መንገዱን ለመሄድ ሲዘጋጅ ልዩ ልዩ ምክንያት (ሰይጣናዊ ሃሳብ) በመፍጠር በግ ጠባቂውን "ወንድሜ ሆይ አንድ የማስቸግርህ ጉዳይ አለኝ ይኸውም በቤቴ የረሳሁት ነገር ስላለ ዕገሊት ወደ ምትባል ሀገር ሄዶ መልእክት ያደርስልኝ ዘንድ ይህን ብላቴና እንድትሰጠኝ ነው የድካሙንም ዋጋ ሃያ ወቄት ወርቅ እከፍላለሁ" አለው።
ያም በግ ጠባቂ ስለ ወርቁ ስጦታ ደስ በመሰኘት ያን ጐልማሳ ጠርቶ "ልጄ ባሕራን ሆይ ይህ ክቡር ሰው ለሥራ ጉዳይ ወደ ቤቱ ሊልክህ ይፈልጋልና መልእክቱን አድርስለት እግዚአብሔር በሰላም ያግባህ" ሲል ጠየቀው፡፡ ልጁም "እሺ መልካም ነው አባቴ ሆይ ያዘዝከኝን ሁሉ ለመፈጸም ዝግጁ ነኝ" አለው። ከዚህም በኋላ ያ ባለጸጋ "ይህችን የመልእክት ደብዳቤ ይዞ ወደ አንተ የመጣውን ስሙ ባሕራን የተባለውን መልእክቷ በደረሰችህ ጊዜ ፈጥነህ ግደለው ገድለህም ሬሣውን ከጉድጓድ ጣለው እኔ በሰላም ተመልሼ እስክመጣ ድረስ ማንም ማን ይህን ምሥጢር አይወቅ" የሚል ጽሑፍ ለሹሙ ጽፎ አዘጋጀ፡፡ እንዲሁም በሹሙና በእርሱ መካከል የሚተዋወቁበትን ማኅተም በደብዳቤው ላይ አትሞ ለባሕራን ሰጠው፡፡ ለመንገዱም የሚሆነው ስንቅ ሰጥቶ ላከው።
ባሕራንም መልእክቱን ለማድረስ ዘጠኝ ቀን ተጉዞ የአንድ ቀን ጎዳና ሲቀረው እነሆ ክቡር የሚሆን የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በንጉስ ጭፍራ አምሳል በፈረስ ተቀምጦ ወደሱ ደረሰና ወዴት እንደሚሄድ ጠየቀው፡፡
ባሕራንም "ከአንድ ባለጸጋ ሰው የተጻፈ ደብዳቤ ይዤ እርሱን ለማድረስ ዕገሊት ወደምትባል አገር እሄዳለሁ" አለው። ንዑድ ክቡር የሚሆን ቅዱስ ሚካኤልም "እስኪ የመልእክቱን ደብዳቤ አሳየኝ?" አለው፡፡ ባሕራንም "ጌታዬ ለማንም አታሳይ ብሎኛል" አለው፡፡ መልአኩም "እሺ ያም ባይሆን እንደተጠቀለለ አሳየኝ" አለው፡፡ ባሕራንም አሳየው፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም በሞቱ ደብዳቤ ላይ እፍ ቢልበት የሞቱን ትእዛዝ አጥፍቶ የሕይወት ትዕዛዝ ጽፎበታል፡፡ በደብዳቤው ላይ የተጻፈውን የሞት መልእክት ደምስሶ "ከእኔ ከባለጸጋ ዕገሌ የተጻፈ" ይልና "ይህን መልእክት ይዞ ለመጣሰው ዕገሊት የምት ባለዋን ልጄን አጋቡት (ዳሩለት) በዱር የተሰማራውን ከብቴን በቤት ያለውን ሀብቴን በጠቅላላው የሚንቀሳቀስና የማይንቀሳቀስ ንብረቴን በሙሉ አውርሼዋለሁና እኔ እስክመጣ ድረስ አትጠብቁ በሄድኩበት ሀገር የምቆይበት ጉዳይ አለኝና፤ በቤቴና በንብረቴ ላይ ሙሉ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና የወደደውን ያደርግ ዘንድ አትከልክሉት ስለዚህም በእኔና በአንተ መካከል የምንተዋወቅበትን ምልክት አድርጌበታለሁ" የሚል ጽሑፍ ጽፎ ሰጠውና "እንግዲህ ወደ ባለጸጋው ቤት ሂድና ይህን መልእክት አድርስ ነገሩ እንዳይገለጽብህ ከእኔ ጋር መገናኘታችንንና የመልእክቱን ጽሑፍ እንደለወጥኩልህ ለማንም አትንገር" ሲል አስጠነቀቀው፡፡ ባሕራንም "እሺ ጌታዬ እንዳዘዝከኝ አደርጋለሁ" ብሎ ጉዞውን ቀጠለና የዚያን የባለፀጋ ቤት እየጠየቀ ከደረሰበት በኋላ ደብዳቤውን ለሹሙ ሰጠው።
ያም ሹም ደብዳቤውን ተቀብሎ ሲያነብ የታተመበት ማኅተም ዕውነተኛ መሆኑን ከአረጋገጠ በኋላ እግዚአብሔር እንዳዘዘው በቤተ ክርስቲያን ደንብ የባለጸጋውን ልጅ በተክሊል አጋባው፣ የሠርጉንም በዓል እስከ ዐርባ ቀን ድረስ በታላቅ ደስታ አከበሩ። ከሠርጉም በዓል ፍጻሜ በኋላ ያ ባለጸጋ ሰው ከሄደበት አገር ወደ ሀገሩ ተመልሶ ገባና በቤቱ አካባቢ ሲደርስ የደስታና የዘፈን ድምፅ ስለሰማ "ይህ የምሰማው ድምፅ ምንድነው?" ሲል ጠየቀ፡፡ ሰዎቹም "ባሕራን የተባለ ጐበዝ ካንተ ዘንድ ልጄን ዳሩለት የሚል ትእዛዝ አምጥቶ ልጅህን አግብቶ በሠርጉ ምክንያት ይዘፍናሉ ይደሰታሉ እነሆ እየበሉና እየጠጡ በቀንና በሌሊት እየዘፈኑ ሲደሰቱ ዐርባ ቀን ሆኗቸዋል በመልእክትህም እንዳዘዝከው ገንዘብህን የወንድና የሴት ባሮችህን በጠቅላላው የሚንቀሳቀስና የማይንቀሳቀስ ንብረትህን ሁሉ በሙሉ አስረክበውታል" አሉት።
ያም ባለጸጋ ያህን ቃል በሰማ ጊዜ ከድንጋጤው የተነሳ በታላቅ ቃል በመጮኽ ከመሬት ላይ ተከስክሶ ሞተና ነፍሱን አጋንንት ተረክበው ወደ ሲኦል አወረዷት። ከዚህም በኋላ ባሕራን የተባለ ያ ጐልማሳ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል በየወሩ እያከበረ ዝክሩን እየዘከረ ይኖር ጀመር። በዚያን ጊዜ በጉዞ ላይ ሳለ ተገልጾለት የሞቱን መልእክት ወደ ሕይወት የለወጠለት ቅዱስ ሚካኤል እንደሆነም አወቀ ተረዳ። ንዑድ ክቡር የሚሆን የመላእክት ሁሉ አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ያደረገው ተአምር ሊቆጥሩት የማይቻል ብዙ ስለሆነ በኛም ላይ ኃይለ ረድኤቱ አድሮብን ይኑር እስከ
ዘላለሙ ድረስ አሜን።
ቅድስት አፎምያ፡- ቅድስት አፎምያ ሀገሯ ኪልቅያ ነው፡፡ ባለቤቷ አስተራኒቆስ መስፍነ ኪልቅያ ነበረ፡፡ እርሷም በትዳር በነበረችባቸው ዘመናት እግዚአብሔርን ከሚወድ ባለቤቷ ጋር እግዚአብሔርን ስታገለግለው የኖረች ሴት ደገኛ ሴት ናት፡፡ በየወሩ በ29 ቀን የጌታችንን የልደቱን፣ ወር በገባ በ21 የእመቤታችንንና ወር በገባ በ12 የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ እያደረጉ ነዳያንን ይጎበኙ ነበር፡፡
ባለቤቷ አስተራኒቆስ ከዚህ ዓለም የሚያርፍበት ጊዜ እንደደረሰ ባወቀ ጊዜ ይሰጡት የነበረውን ምጽዋት እና የሦስቱን በዓላት መታሰቢያ ማድረግ እንዳታስታጉል ከአደራ ጋር አዘዛት፡፡ እርሷም የመልአኩን የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባለቤቷን ጠይቃ አሠርቶ ሰጣት፡፡ በከበረ ቦታም አኖረችው፡፡ ባሏ ካረፈ በኋላ ያዘዛትን መንፈሳዊ ሥራ ከወትሮው አስበልጣ መሥራት ቀጠለች፡፡ ባሏም ታሞ ሞቶ ከሀብቷ ከንብረቷ እየሰጠች እየመጸወተች በጾም በጸሎት ተወስና ትኖር ነበር፡፡ ሰይጣን ለምቀኝነት አያርፍምና ደግ መነኩሴ መስሎ አጋንንትን መነኮሳይያት አስመስሎ መጥቶ ከደጅ ሆኖ አስጠራት፡፡ እርሷም "ከቤት ገብታችሁ በቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ፊት ጸልዩልኝ" አለቻቸው፡፡ ሰይጣናቱም "እኛማ በነግህ ጸልየናል?" አሏት፡፡ ቀጥሎም ሰይጣን "...እንደው አንቺ ግን ይህ ሁሉ ጾም ጸሎት ምን ያደርገልሻል? ሀብትሽን ሰጥተሸ መጨረስሽስ ስለምንድን ነው? በዚያ ላይ አንቺ ስትደክሚ የሚደግፍሽ ስታረጂ የሚጦርሽ ልጅ የለሽም ሁለተኛ ማግባት ኃጢአት መስሎሻልን? እነ አብርሃም እነ ዳዊ ከብዙ ሴቶች ብዙ ልጆች ወልደው የለምን? አሁንም ቤት ሰሪ ጎመን ዘሪ ልጅ ያስፈልግሻልና ባል አግቢ፣ እሺ በይኝ" አላት፡፡
ቅድስት አፎምያም "አባ ቆብህ መልካም ነበር ንግግርህ ግን ክፉ ነው፣ አትጹሚ አትጸልዩ ያልከኝ ጌታ ምጽዋት አበድር እመስዋዕት ብሎ የለምን? ሁለተኛ ባል አግቢ ማለትንስ ከምን አገኘኸው? እርግቦች እንኳ ባሎቻቸው ከሞቱባቸው ከሌላ ወንድ አይቀርቡም ታዲያ ጥንቱን በንጽሕና ሊኖር የተፈጠረ ሰው ሁለተኛ አላገባም ቢል ዕዳ ፍዳ ሊሆንበት ነውን?" ብላ ሞገተችው፡፡
የሰው ልጆች ጠላት የሆነው ሰይጣንም በመልካም አገልግሎት ስትበረታ አይቷታልና ዝም ብሎ ሊተዋት አልወደደም፡፡ ከላይ እንዳየነው በመጀመሪያ ባል ሳታገባ ማገልገሏን ትታ ሌላ ባል አግብታ ልጅ ወልዳ እንድትኖር በብዙ ማባበል ጠየቃት፡፡ ባሏ መንግሥተ ሰማያትን ስለወረሰ ምንም ምጽዋት እንደማይሻ አስመስሎ ነገራት፡፡ ቅድስት አፎምያ ግን ዳግመኛ ትዳር ላለመመሥረት ቃል ኪዳን እንደገባች ርግብንና ዖፈ መንጢጥን አብነት አድርጋ እነርሱ እንኳ በሕይወት ዘመናቸው ከአንድ ባል ውጪ ሌላ ባል እንደማያውቁ በመጥቀስ አሳቡን እንደማትቀበለው ገለጸችለት፡፡ ሰይጣንም አስመሳይ መሆኑ አላዋጣ ሲለው ማንነቱን ቀይሮ ሊያንቃት ቢሞክር የእግዚአብሔርንና የቅዱስ ሚካኤልን ስም ጠርታ አባረረችው፡፡ እርሱም ተመልሶ መጥቶ እንደሚያጠፋት ዝቶባት እንደአቧራ በኖ እንደ ጢስም ተኖ ጠፋ፡፡
በሰኔ 12 ቀን የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ እያዘጋጀች ሳለች ሰይጣን ብርሃናዊ መልአክ መስሎ መጣ፡፡ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል እንደሆነ ገልጾ የመጀመሪያውን የመሰለ ከንቱ ምክሩን አሰማምሮ አቀረበላት፡፡ አሳቡንም የእግዚአብሔር ፈቃድና አሳብ እንደሆነ አድርጎ ለማሳመን ሞከረ፡፡ ሰይጣን አስቀድሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በገዳመ ቆሮንቶስ መጻሕፍትን እየጠቀሰ እንደተፈታተነው ሁሉ ቅድስት አፎምያንም ለማሳመንም አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣ ያዕቆብን፣ ዳዊትን የመሳሰሉ ደጋግ አባቶችን ታሪክ እየጠቀሰ ወደ ትዳር እንድትገባ ደጋግሞ ወተወታት፡፡ ቅድስት አፎምያም በእግዚአብሔር ኃይል ጸንታ በቅዱስ ሚካኤልም ተራዳኢነት ታምና "የእግዚአብሔር መልአክ ከሆንክ መንፈሳዊ ማረጋገጫህ የሆነው የመስቀል ምልክት የታለ?" በማለት በምድራዊ ንጉሥና በጭፍራው መካከል የሚኖርን የጋራ መግባቢያ መንገድ ዋቢ አድርጋ ጠየቀችው፡፡ ለጊዜው "በእኛ በመላእክት ዘንድ እንዲህ አይደለም" ብሎ ሊሸነግላትና አቋሟን ሊያስቀይራት ሞከረ፡፡ ከቤቷ ያለ የቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ላይ ያለውን ምልክት አብራርታ የእርሱ ግን ከዛ ጋር አንድነት እንደሌለው አረጋገጠችበት፡፡ በመቀጠልም ከቤቷ ላለው ለቅዱስ ሚካኤል ሥዕል እጅ እንዲነሣ ጠየቀችው፡፡ በዚህ ጊዜ መልኩ ወደ ትክክለኛ ሰይጣናዊ ማንነቱ ተለወጠና ጨለማ ለብሶ እየዛተ አነቃት፡፡ ቅድስት አፎምያም የከበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤልን "ድረስልኝ" እያለች በጠራችው ጊዜ መልአኩም ፈጥኖ በመድረስ ከሰይጣን እጅ አዳናት፡፡
የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም ለሰይጣኑ ተገቢውን ቅጣት ሰጥቶ ቅድስት አፎምያን ባረካት፡፡ የዕረፍት ቀኗ በዚህ ቀን መሆኑን ነግሮ ቤቷን እንድታዘጋጅ አዘዛት፡፡ የበዓሉን ዝግጅት አከናውና ሥጋ ወደሙን ተቀብላ ኤጲስ ቆጶሱንና ካህናቱን እንደየመዓርጋቸው ጠርታ በቤቷ አክብራ ተቀበለቻቸው፡፡ ለነዳያንና ለጾም አዳሪዎች በኤጲስ ቆጶሱና በካህናቱ እጅ ገንዘቧን መጽውታ መንገዷን አሳመረች፡፡ ስለ ኃጢአቷ እንዲጸልዩላት ተማፅና በፊታቸው ተንበርክካ ጸለየች፡፡ ባሏ ያሠራላትን የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል አቅፋ ስማ ከተማጸነች በኋላ ሰኔ 12 ቀን በሰላም ዐረፈች፡፡ .
ከ10ኛው እስከ 13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (920-1253 ዓ.ም ድረስ) በላስታ ቡግና ምድር የነገሡ የላስታ ቡግና ተወላጅ የሆኑ የኢትዮጵያ ቅዱሳን ነገሥታት የንግሥናቸው መጠሪያ ‹‹የዛጉዌ ሥርወ መንግሥት›› ወይም ‹‹የላስታ መንግሥት›› በመባል ይታወቃል፡፡
የላስታ ነገሥታት የዘር ሀረጋቸው ከንጉሥ ሰሎሞን ዘር ሲያያዝ የመጣ ነው፡፡ ከላስታ (ከዛጉዌ) ነገሥታት መካከል ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ፣ ቅዱስ ገብረ ማርያም፣ ቅዱስ ላሊበላና ቅዱስ ነአኵቶለአብ እነዚህ አራቱ ነገሥታት እንደ መልከጼዴቅ (ዘፍ 14፡18) ክህነትን ከንግሥና፣ ቅድስናን ከንጽሕና ጋር አንድ አድርገው በመያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅድስና አገልግለው አልፈዋል፡፡ በንግሥናቸው ሀገራችንን በመልካም ሥራና በቅድስና ከማስተዳደራቸው በተጨማሪ ቅዱሳን ጻድቃን ሆነው እግዚአብሔርን በብዙ ድካም በመልካም ተጋድሎአቸው ያገለገሉና አገልግሎታቸውም ሆነ ቅድስናቸው በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተመሰከረላቸው ጌታችን የሰጣቸውን ቃልኪዳን መሠረት በማድረግ ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ፣ በስማቸው ቤተክርስቲያን አንጻ፣ ጽላት ቀርፃ በዓላቸውን እያከበረች መታሰቢያቸው ተጠብቆ ለዘለዓለም እንዲኖር አድርጋለች፡፡
ገድለ ቅዱስ ላሊበላ፡- እኛ ኢትዮጵያውያን የቅዱስ ላሊበላን እጅግ ድንቅ የሆኑ ሥራዎቹን ዓለም ከሚመለከትበት የተለየ መንፈሳዊ ዐይን ሊኖረን ይገባል፡፡ ስለዚህም የቅዱስ ላሊበላን የቅድስና ሕይወትና ከእግዚአብሔር ጋር ስለነበረው ግንኙነት ገድለ ቅዱስ ላሊበላን መነሻ በማድረግ ብዙ ነገሮችን ቀጥሎ እናያለን፡-
1.1 ቅዱስ ላሊበላ ከአባቱ ዣን ስዩምና ከእናቱ ኪርወርና ጌታችን በተወለደበት ዕለት ታኅሣሥ 29 ቀን 1101 ዓ.ም በላስታ ቡግና ወረዳ ልዩ ስሟ ሮሀ በተባለችው ሥፍራ ተወለደ፡፡ የልደቱን ነገር አስቀድሞ ቅዱስ ሚካኤል ለእናቱ ነግሯት ነበርና በተወለደ ጊዜ ብዙ ነጫጭ ንቦች መጥተው በሰውነቱ ላይ አርፈው እንደ ማር እየላሱት ስለታዩ እናቱ ‹‹ልጄን ንብ ዘበኛ ሆኖ ይጠብቅልኛል›› ስትል ስሙን ‹‹ላል ይበላል›› ብላዋለች፡፡ ላል በአገውኛ ንብ ማለት ነው፡፡ በጊዜ ብዛት በተለምዶ ነው ‹‹ላሊበላ›› ተብሎ መጠራት የተጀመረው፡፡ ንቦቹ ግን ሥጋዊ ንቦች ሳይሆኑ
በንብ የተመሰሉ መላእክት ናቸው፡፡ ንጉሥ መሆኑን እያመለከቱ የሃይማኖትና የምግባር ማር ከእርሱ ይቀዳል ሲሉ በንብ ሠራዊት ተመስለው ሰውነቱን ላሱት፡፡ እንደ ዮሐንስና እንደ ኤርምያስም በእናቱ ማኅፀን ሳለ ነው መንፈስ ቅዱስ የሞላበት፡፡
ከዚህ ቀጥሎ በገድሉ ውስጥ የተጠቀሱ አንዳንድ አስደናቂ ነገሮችን እናያለን፡፡
1.2. ቅዱስ ላሊበላ ያነጻቸውን አብያተ ክርስቲያናት መመልከት ያለብን በቅርስነታቸውና በቱሪስት መስህብነታቸው ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ የተገኙ ብቸኛ መንፈሳዊ ሀብቶቻችን መሆናቸውን ነው፡- ስለ ቅዱስ ላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት ከማንሳታችን በፊት በመጀመሪያ እውነተኛ የሕይወት ቃል የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስን መመልከት የግድ ያስፈልጋል፡፡ ቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያ ቀድሞ በሕገ ልቡና ከዚያም በሕገ ኦሪት እግዚአብሔርን ስታመልክ ኖራለች፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ሐዋርያቱ እንኳን ለስብከት ከኢየሩሳሌም ሳይወጡ ነው በ34 ዓ.ም በራሷ ሐዋርያ በጃንደረባው ባኮስ አማካኝነት በክርስቶስ ማመንንና ጥምቀትን ወደ ሀገሯ ያመጣችው፡፡ የዚህ ደግሞ ምስክሩ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ 1ኛ ነገ 10፡1-13፣ ሐዋ 8፡26-40፡፡ በዚህ መረጃ መሠረት ኢትዮጵያውያን ከጥንት ጀምሮ እስከ ሰባተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ ወደ ኢየሩሳሌም እየሔዱ ሃይማኖታዊ ጉዞ ያድርጉ ነበር፡፡
ከ7ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በኋላ ግን ከኢትዮጵያ ተነስቶ በሱዳን በግብፅ አድርጎ ወደ ኢየሩሳሌም በእግርና በእንስሳት ጉዞ ለማድረግ የመንገዱ አድካሚነትና በረሃማነት የሚባክነው ጊዜ እንዲሁም በኢየሩሳሌም ዙሪያ ተሻግሮም እስከ ግብፅና ሱዳን ድረስ የእስልምና ሃይማኖት ስለተጠናከረ ለኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ወደ ኢየሩሳሌም ለመጓዝ አስቸጋሪ ስለሆነባቸው ለሃይማኖታዊ አምልኮና ስግደት ወደ ኢየሩሳሌም የሚያደርጉት ጉዞ ተቋረጠ፡፡ ይህ ሁኔታም ሲያያዝ እስከ ቅዱስ ላሊበላ ዘመን ደርሷል፡፡
ቅዱስ ላሊበላም የኢትዮጵያ ክርስቲያኖች ወደ ኢየሩሳሌም ያደርጉት የነበረው ጉዞ በመቋረጡ በእጅጉ እያዘነ ተግቶ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ የኢየሩሳሌምንም አምሳያ የሆኑ አብያተ ክርስቲያናትን በሀገሩ ለመሥራት ይመኝ ነበር፡፡ ጥቂት ነገር ሲለምኑት አብዝቶ መስጠት ለእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ነውና ላሊበላ ምድራዊ ኢየሩሳሌምን በሀገሩ ለመሥራት ሲያስብ ልዑል እግዚአብሔር በጥበቡ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ (2ኛ ቆሮ 12፡1-7) ወደ ሰማይ አሳርጎት ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን አሳይቶታል፡፡ ጌታችንም ‹‹ሕዝቦቼ የመከራና የስቃዬን ቦታ ለማየት ኢየሩሳሌም በመሄድ በመንገድ እየቀሩ ስለሆነ አሁን ግን አንተ በሀገረ ሮሐ ኢየሩሳሌምን ትሠራለህ›› በማለት የቤተ መቅደሶቹን አሠራር ሁሉ በዝርዝር ነግሮታል፡፡ በሰማያዊት ኢየሩሳሌምም ምሳሌ በሀገሩ ላይ ወጥ ከሆኑ የዓለት ድንጋዮች መላእክት እየተራዱት ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን እንዲያንጽ ነግሮታል፡፡
1.3. ጠላት ለክፉ ያሰበውን እግዚአብሔር ለበጎ ያደርገዋል፡- ወደኋላ ተመልሰን የቅዱስ ላሊበላን የልጅነት ሕይወቱን እናንሳ፡- ቅዱስ ላሊበላ እናትና አባቱ ከሞቱበት በኋላ ወደ ጎጃም በመሄድ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን፣ ብሉይና ሐዲስን በደንብ ተምሮ ከጨረሰ በኋላ ወደ ደብረ ሮሐ ተመልሶ መጥቶ ነግሦ ከነበረው ከወንድሙ ከገብረ ማርያም ዘንድ ተቀመጠ፡፡ ‹‹ከገብረ ማርያም ቀጥሎ የሚነግሠው ላሊበላ ነው›› ተብሎ ትንቢት ስለተነገረ ሊያጠፋው ምክንያት ይፈልግበት ነበር፡፡ ለዐፄ ገብረ ማርያም በእናትም በአባትም እኅት የምትሆነው ለላሊበላ ግን በአባት ብቻ እኅት የሆነችው ዮዲት ላሊበላን ለመግደል በማሰብ ቀን ከሌሊት አጋጣሚን ትጠብቅ ነበር፡፡ ቅዱስ ላሊበላም ጌታችን መራራ ሐሞት መጠጣቱንም እያሰበ ሁልጊዜ ዓርብ ዓርብ ከጾምና ጸሎት በኋላ መራራ ኮሶ ይጠጣ ነበርና ይህን አጋጣሚ በመጠቀም አንድ ቀን እንደጠማው አውቃ በጠላ ውስጥ መርዝ ጨምራ ሰጠችው፤ ቅዱስ ላሊበላም መርዝ የተቀላቀለበትን ጠላ ጠጣው፡፡ እርሱ ከመጠጣቱ በፊት ያገለግለው የነበረው ዲያቆን ቀምሶት ወዲያው ሲሞት አየ፡፡ ዲያቆኑ ያስመለሰውን የጠጣው ውሻም ወዲያው ሞተ፡፡ ቅዱስ ላሊበላም ይህን ሲመለከት በሐዘንና በፍጹም ፍቅር ሆኖ ‹‹አገልጋዬ ለእኔ የተዘጋጀውን መርዝ ጠጥቶ እንደሞተ ሁሉ እኔም መሞት ይገባኛል›› በማለት ያን መርዝ ስለወዳጁ ፍቅር ሲል ጠጥቶ ለመሞት ቆረጠና ጠጣው፡፡ ጌታችን በወንጌሉ ስለራሱ ‹‹ስለ በጐቹ ቤዛ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ የሚሠጥ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም›› (ዮሐ 15፡13) ብሎ የተናገረውን ቃል ቅዱስ ላሊበላም ስለ ወዳጁ ሞት ሲል ራሱን ለሞት አሳልፎ ሰጠ፡፡ ነገር ግን መርዙ እንኳን ሊጎዳው ይቅርና በሆዱ ውስጥ ከልጅነቱ ጀምሮ የነበረበትን የሆድ ሕመም ነቅሎ አወጣለት፡፡ በዚህም ጌታችን በወንጌሉ ‹‹የሚገድል መርዝም ብትጠጡ ምንም አትሆኑም›› (ማር 16፡18) ያለው ቃል ተፈጽሞለታል፡፡ መርዙ ለበጐ ሆኖለት ከሆዱም ውስጥ የነበረው ጥፍሮች ያሉት አውሬ መሰል ፍጡር ወጣለትና የሆድ ሕማሙ ፈጽሞ ተወው፡፡ ያን ጊዜም ቅዱስ ላሊበላ በወቅቱ ለሦስት ቀንም ያህል እንደሞተ ሆኖ የቆየ ቢመስልም ቅዱስ ገብርኤል ግን በመንፈስ ወደ ሰማይ ነጥቆ ወስዶ ሰባቱ ሰማያትን ያሳየው ሲሆን በጌታችን ፊትም አቅርቦት አስባርኮታል፡፡ ጌታችንም ቅብዓ መንግሥት ቀብቶት ትልቅ ቃልኪዳን ሰጥቶታል፡፡
ጻዲቁ ንጉሥ ቅዱስ ላሊበላ ቅድስናን ከንግሥና፣ ክህነትን ከንጽሕና፣ ጥበብ መንፈሳዊን ከጥበብ ሥጋዊ ጋር አንድ አድርጐ አስተባብሮ የያዘ በመንፈስ ቅዱስ የሚመራ፣ ቅዱሳን መላእክትም ይራዱት እንደነበርና ጌታችንም ትልቅ ቃልኪዳን እንደሰጠው ከቅዱስ ገድሉ ላይ እናገኛለን፡፡ ከጌታችን ዘንድ የተሰጠውንም ቃልኪዳን በሦስት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ በዚህም መሠረት፡-
1ኛ. መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ቅዱስ ላሊበላን እየመራው ከላስታ ወደ አክሱም ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌም አድርሶ በዚያ የሚገኙትን ቅዱሳት መካናት ሁሉንም ካሳየው በኋላ ‹‹ወደ ሀገርህ ሮሐ ተመልሰህ በእነዚህ ምሳሌ ታንጻለህ›› ብሎታል፡፡ ወደ ሀገሩም ተመልሶ በአሽተን ማርያም ተራራ ላይ ሱባኤ ይዞ በጾም ጸሎት ተወስኖ ሳለ እግዚአብሔር የሚሠራቸውን መቅደሶች በግልጽ በራእይ አሳይቶታል፡፡
2ኛ. ከላይ እንዳየነው ለሞት ተብሎ የተሰጠው መርዝ ለሕይወት ሆኖለት በመሬት ላይ ወድቆ ሳለ በነፍስ መልአክ ነጥቆት እስከ ሰባተኛው ሰማይ ጽርሐ አርያም ድረስ ደርሶ በጌታ ፊት ቀርቦ ከጌታ ዘንድ ‹‹እኔ አከበርኩህ ቃሌ አይታበይም፣ ከአንድ ቋጥኝ እነዚያን በራእይ ያሳየሁህን አብያተ ክርስቲያናት ታንጻለህ›› የሚል ቃልኪዳን ተቀብሏል፡፡
3ኛ. ከኢየሩሳሌምም ተመልሶ የንግሥናውን ዙፋን ከቅዱስ ገብረ ማርያም ከተረከበ በኋላ በተሰጠው መንፈሳዊ ሀብትና ባየው ራእይ መሠረት አብያተ ክርስቲያናቱን አንጾ ከጨረሰ በኋላ በቀኝና በግራው ዓሥር ዓሥር ኪሎ የሚመዝን የዓለት ድንጋይ ተሸክሞ ለ7 ዓመት ሲጾም ሲጸልይ ጌታችን ተገልጦለት ‹‹…ያነጽካቸውን ቤተ መቅደሶች የተሳለመውን ኢየሩሳሌምን እንደተሳለመ አድርግለታለሁ›› የሚለውን የመጨረሻውን ቃልኪዳን ሰጥቶታል፡፡ (ይህን ቃልኪዳኑን መጨረሻ ላይ በዝርዝር እናየዋለን) እነዚህን ሦስት ዋና ዋና ቃልኪዳኖቹን በቅድሚያ ማንሳት የፈለኩበት ምክንያት ቀደም ብዬ እንደጠቀስኩት ስለ ቅዱስ ላሊበላ ድንቅ ሥራዎች ከማሰባችንም ሆነ ከመናገችን በፊት በቅድሚያ ስለ ራሱ ስለ ቅዱስ ላሊበላ የቅድስና ሕይወቱና ከእግዚአብሔር ጋር የነበረውን ግንኙነት ማወቁ የግድ አስፈላጊ መሆኑን ለመጠቆም ነው፡፡ አሁን አሁን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሆን ተብሎ
በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ውቅር አብያተ ክርስቲያናቶቹ በቱሪስት መስህብነታቸው ብቻ እየታዩ የቅድስና ታሪካችንም እየተጨፈለቀና መንፈሳዊ እሴቶቻችንንም ለማጥፋትም ጥረት እየተደረገ ስለሆነ እውነተኛውን ነገር በደንብ ማወቅና በእጅጉ መጠንቀቅ ስላለብን ነው ይህን የማነሳው፡፡ ስለዚህ የቅዱስ ላለበላን የቅድስና ሕይወትና ከእግዚአብሔር ጋር የነበረውን ግንኙነት ስንረዳ እነዚያ እጅግ ድንቅ የሆኑ ሥራዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ኃይልና በሰማያውያን መላእክት እርዳታ የተሠሩ መሆናቸውን እንረዳለን፤ እግዚአብሔርም ለእኛ የሰጠንን ድንቅ የምሕረትና የቃልኪዳን ስጦታዎቻችን መሆናቸውን እንረዳለን፡፡ ያንጊዜም ውቅር አብያተ ክርስቲያናቶቹን ዓለም ከሚመለከትበት የተለየ መንፈሳዊ ዐይን ይኖረናል፡፡ የቃልኪዳኑም ተጠቃሚዎች ለመሆን መንፈሳችን ይነሳሳል፡፡ በዚህ ደግሞ አሁን ያለውም ሆነ ወደፊት የሚመጣው ትውልድ ታሪኩን ከማጉደፍና ከጥፋት ይጠበቃል፣ አኩሪ ታሪኩንም ጠንቅቆ ለማወቅ መንፈሳዊ ቅናትም ስለሚያድርበት ራሱንም ከውጪው የባሕል ወረራና ጥቃት ይጠብቃል፡፡ በሀገራችን ያሉትን እጅግ ጥልቅ የሆኑ ሃይማኖታዊና ባሕላዊ ምሥጢሮችን ጠንቅቀው የተረዱት እነ ፕሮፌሰር ፓንክረስት ‹‹ክርስቶስ ከነጮች ይልቅ ለኢትዮጵያውያን ቅርበት አለው›› በማለት ምስክርነታቸውን እየሰጡ ባለበት ወቅት የዘመኑ የሀገራችን ወጣት ማንነቱን ጠንቅቆ ቢያውቀው ኖሮ የእነርሱን (የነጮቹን) ባሕል ለመከተል ባልዳዳው ከዘመናዊ ባርነትም ራሱን በጠበቀ ነበር፡፡
1.4.መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለቅዱስ ላሊበላ ስለ ቤተመቅደሶቹ አሠራር በዝርዝር እንዳስረዳው፡- በተራ ቁጥር ሁለት ላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው በቅዱስ ገድሉ ላይ ከገጽ 117-127 ድረስ በጣም በስፋትና በዝርዝር እንደተጠቀሰው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ላሊበላን እስከ ሰባተኛው ሰማይ ድረስ በመላእክት ተነጥቆ በፊቱ እንዲቆም ካደረገው በኋላ ቤተ መቅደሶቹን እንዴት እንደሚያንጽ ቃል በቃል ነግሮታል፡፡ እግዚአብሔር ለኖህ መርከቡን እንዴት እንደሚሠራ ከነልኬቱ ጭምር በዝርዝር እንደነገረው ሁሉ ለቅዱስ ላሊበላም ዝርዝር ሁኔታዎችን ጭምር እንዲህ በማለት ትእዛዝ ሰጥቶታል፡- ‹‹መልአኩም ክብሩ ከሰማያት ሁሉ ክብር ወደሚበልጥ ወደ ሰባተኛው ሰማይ አደረሰው፣ ቅዱስ ላሊበላም ይህንን አይቶ በግንባሩ ተደፋ፣ ከኪሩቤል ዘንድ ይነሳ የሚል ቃል ተሰማና አንዱ ሱራፌል መጥቶ አነሣው፡፡ ልቡንም አጽንቶ አቆመው…እግዚአብሔርም ተናገረው፡- ‹በምድር ላይ ቤተመቅደስ ትሠራልኝ ዘንድ የማሳይህን አስተውል፤ እዝነ ልቡናህንም ግለጥ፡፡ ከሰው ጋር ስለምኖር በሰማያት የምትኖር አባታችን እያሉ ከሚጠሩኝ በሃይማኖት ከተጐናፀፈኝ ስሜን ከሚያመሰግኑ ከመረጥኳቸው ከሕዝብ አንደበት በምመሰገንበት ገንዘብ እኔ ፈጥሬያቸዋለሁና፡፡
ከመጀመሪያይቱ ድንኳን ውስጥ በተሣለው ላይ ምስላቸው የተሠራ ከሚንቀሳቀሱ ከኪሩቤል አምሳል ለሙሴ እንደተናገርኩት አይደለም፡፡ ወዳጄ ሙሴ የመጀመሪያይቱን ድንኳን አርአያ በደብረ ሲና እንዳሳየሁት ድንኳንን እንደሠራ ሁሉ እንደሁ አንተም እንዳሳየሁህ ትሠራ ዘንድ ዕወቅ፣ አስተውል፣ ተጠንቀቅም፡፡ የማሳይህ ግን ለሙሴ እንዳሳየሁት አይደለም፤ መቅደሴን የምትሠራልኝም ሙሴ እንደሠራው አይደለም፤ ሙሴስ ከተፈተለ ልብስና ከእንጨት ድንኳን ሠራ፤ አንተ ግን ለምሰሶውም ሆነ ለመቀኑ ለመድረኩ እንጨትን የምትፈልግ አይደለህም፤ ለጠፈራቸው መማገሪያ ገመድ የምትሻ አይደለህም፣ እንጨትንም ለማገር፣ ለምሰሶዋቸውም ገበታ፣ ለዙሪያቸውም ለማያያዣ ጭቃን የምትፈልግ አይደለህም፡፡ የቤተመቅደሶችን ፈቃድ ሁሉ ከአንድ ቋጥኝ ድንጋይ ትፈጽማለህና፡፡ የማሳይህ እኚህ የቤተ መቅደሶች አኗኗር ከምድር ልብ ውስጥ እስከዛሬ አለ፡፡ ከአሁን ጀምሮ በእጅህ እስኪገለጡም ድረስ በምድር ልብ ይኖራሉ፡፡ በሰው ልጅ ጥበብ ያይደለ በእኔ ሥልጣን ከምድር ልብ ውስጥ ታወጣቸው ዘንድ መረጥሁህ፡፡ ሕዝቦቼ ተወልጄ አድጌ ሞቼ ተቀብሬ ከሞትም የተነሳሁባትን ሀገር ለማየት ኢየሩሳሌም በመሄድ ግማሹም በበረሃ ይቀር ነበር አሁን ግን አንተ ኢየሩሳሌምን በሀገርህ ትሠራለህ፡፡ በማንም እጅ ዳግመኛ ሊሠሩ የማይችሉ ቤተ መቅደሶቼን እንዳሳየሁህ ትሠራለህ፡፡ አንተም እንዳሳየሁህ በልብህ ውስጥ አኑራቸው፡፡ ስትሠራቸውም እየልካቸው ይሁን፤ ከእርዝመታቸውም በላይ ቢሆን፣ ከወርዳቸውም በላይ ቢሆን፣ በመወጣጫቸውም ላይ ቢሆን አንዳች እንዳትጨምር፡፡ ያሳየሁህ እሊህ ዐሥሩ መቅደሶች ከአንዲት ቋጥኝ ድንጋይ ሲወጡ አይተሃልና….› እያለ ጌታችን ሲነግረው ጻዲቁ ንጉሥ “ይህ እንዴት ይሆናል?” በማለት ይጠይቃል፡፡ ጌታም እውነት እልሃለሁ እነዚህ ያሳየሁህ መቅደሶች በሰው ኃይል የሚሠሩ ሆነው አይደለም፤ ጀማሪያቸው ሠሪያቸውና ፈጻሚያቸው እኔ ነኝ ነገር ግን ኃይሌ በአንተ እጅ እንዲገለጽ ለምክንያት ተልከሃል፤ አንተ አነጽካቸው እየተባለ እስከ ዕለተ ምፅዓት ድረስ ስምህ ይጠራባቸዋል…›› እያለ ይቀጥላል የቅዱስ ላሊበላ ገድል፡፡ ቤተ መቅደሶቹንም ለመሥራት ቦታውን ያውቅ ዘንድ ሱባኤ ገብቶ ሳለ ዛሬ ቤተ ማርያም ካለችበት ቦታ ላይ ቅዱሳን መላእክት ሲወጡና ሲወርዱ ታይተውት በቦታው ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ መቅደሱን መሥራት ጀመረ፡፡ ዓሥሩን ቤተ መቅደሶች ሲሠራ እርሱ አንድ ክንድ ሠርቶ እንደሆነ ሌሊቱን አድሮ በቀጣዩ ቀን አሥር ክንድ ሆኖ ያገኘው ነበር፣ ቀንም በማይታወቁ ሰዎች አምሳል እየተገለጡ
መላእክት ይራዱት ነበር፡፡
1.5. አንዳንድ ነገሮች ስለ ቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፡- ቅዱስ ላሊበላ ዓሥሩም ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በጣም በሚያስገርም ሁኔታ በውስጥና በውጭ ያሉት ብዙ ቅርጾች ነገረ ድኅነትን በምሳሌ እንዲወክሉ አድርጎ ነው ያነጻቸው፡፡ የክርስቶስን መከራና በእርሱም የተገኘውን ፍጹም ዘላለማዊ ድኅነት በእያንዳንዱ ቤተ መቅደስ ውስጥ እንዴት አድርጎ በምሳሌ እንዳስቀመጠው እጅግ አስገራሚ ነው፡፡
በላስታ ቅዱስ ላሊበላና አካባቢው የሚገኙ ሌሎች አስደናቂ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፡- ከአሥሩ የቅዱስ ላሊበላ አስደናቂ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በተጨማሪ የቅዱስ ነአኵቶለአብና የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ አብያተ ክርስቲያናት እንዲሁም አሸተን ማርያም በዋናነት ሕዝበ ክርስቲያኑ የሚጐበኛቸው ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡ በላሊበላና አካባቢው ግን እጅግ ጥንታዊና አስደናቂ የሆኑ በጣም በርካታ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል ሣርዝና ሚካኤል፣ ብልባላ ቂርቆስ፣ ብልባላ ጊዮርጊስ፣ አርባዕቱ እንስሳ፣ ትርኩዛ ኪዳነምሕረት፣ ገነተ ማርያም፣ ቀንቀኒት ሚካኤል እነዚህ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ሲሆኑ እንዲሁም ዋልድቢት ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳም፣ አቡነ ዮሴፍ ገዳም፣ ገብረ ክርስቶስ ዋሻ ቤተክርስቲያን፣ ቅድስት አርሴማ ቤተክርስቲያን፣ ቀደሊት ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ እመኪና መድኃኔዓለምና እመኪና ልደታ፣ ማውሬ እስጢፋኖስ፣ የቅዱስ ገብረ ማርያም ቤተክርስቲያን፣ ማይ ማርያም ቤተክርስቲያን፣ ተከዜ ኪዳነምሕረትና መድኃኔዓለም አንድነት ገዳም ከብዙ በጥቂቱ ይጠቀሳሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዳንዶቹ ከ485-536 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ በዐፄ ካሌብ ዘመነ መንግሥት የታነጹ ናቸው፡፡ ሌሎቹንና በሰሜን ላስታ ያሉትን ደግሞ እነ ላሊበላና ይምርሃነ ክርስቶስ አንጸዋቸዋል፡፡
ቅዱስ ላሊበላ እኛ ከምናውቃቸው ከድንቅ ሥነ ሕንፃዎቹ ሥራ በተጨማሪ ከሺህ ዓመታት በፊት በሥዕል፣ በሥነ ጽሑፍ፣ በሃይማኖት፣ በኢኮኖሚ፣ በውጭ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙትና በመሳሰሉት ሁሉ እጅግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ቅዱስ ላሊበላ ከሺህ ዓመታት በፊት አዳራሾችን፣ ፎቆችን፣ የውስጥ ለውስጥ መተላለፊያዎችን፣ የእንግዳ መቀበያዎችን፣ የሕፃናት ማሳደጊያዎችን፣ የሕሙማን መፈወሻዎችን፣ የሕንፃ መሳሪያዎችን፣ የትምህርት ማዕከሎችን፣ የመደጎሻ ቦታዎችን ያቋቋመ መሆኑን የብራና ገድሉ እንደሚናገር የደብሩ አባቶች ይገልጣሉ፡፡ ወደፊት ተርጎመው እንሚያቀርቡልን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ ቅዱስ ላሊበላ ከዚህ በተጨማሪ የግእዝ ቋንቋን በጽሑፍ አበልፅጎ ያቆየ ባለውለታ ነው፡፡ ከላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ውጭ ሌሎችንም በርካታ ቤተ መቅደሶች ሠርቷል፤ ከሀገራቸንም አልፎ በሱማሌ ሞቃዲሾ ላይ መቅደሰ ማርያም የተባለች ቤተክርስቲያን ሠርቷል፡፡ ክርስትናን ከግብፅ ምድር ጨርሰው ለማጥፋት ተንባላት በተነሡ ጊዜ ዓባይን ሊያግድባቸው ሲነሣ በብዙ ምልጃና ልመና ስለማራቸው በሀገሪቱ ውስጥ ክርስትና እስካሁን እንዲቆይ የራሱን ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ በአጠቃላይ ቅዱስ ላሊበላ ነቢይም ሆኖ፣ ሐዋርያም፣ ጻዲቅም፣ ሰማዕትም ሆኖ ጥበብ መንፈሳዊንና ጥበብ ሥጋዊን ከእግዚአብሔር ተሰጥቶት ንግሥናንና ክህነትን፣ ቅድስናንና ንጽሕናን በሚገባ አስተባብሮ በማያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅንነት ሲያገለግል ኖሮ ሰኔ 12 ቀን 1197 ዓ.ም ከፈጣሪው ታላቅ ቃልኪዳን ተቀብሎ በዝማሬ መላእክት፣ በመዝሙረ ዳዊት ቅድስት ነፍሱ ከሥጋው ተለይታ ሰማያዊ ክብርን ወርሷል፡፡ ክቡር ሥጋውም ራሱ ባነጸው ቤተ ሚካኤል መቅደስ ሥር በክብር ዐርፏል፡፡
1.6.መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለቅዱስ ላሊበላ የገባለት ልዩ ቃልኪዳን፡-
1.6.1. ወደ ሰማይ ነጥቆ ወስዶት በዙፋኑ ፊት የሰጠው ቃልኪዳን፡- ‹‹ዛሬ በዚህች ቀን ከአንተ ጋር እነሆ ኪዳኔን አጸናሁ፡፡ በጸሎትህ ኃይል ታምኖ በውስጣቸው የሚያመሰግን ትሠራቸው ዘንድ ያላቸው አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ የደረሰ ሁሉ አንተን አስቦ ‹አቤቱ ፈጽመህ ይቅር በለኝ› የሚለኝ፣ ‹ይህን የሚያስደንቅ ሥራ በእጁ ስለገለጥክለት ስለ ባሪያህ ስለ ቅዱስ ላሊበላ ብለህ ይቅር በለኝ› እያለ የሚጸልየውን በዚያ ጊዜ እኔ ጸሎቱን እሰማዋለሁ፡፡ ከሕፃንነቱ ጀምሮ የሠራውን ኃጢአት ሁሉ አስተሠርይለታለሁ፤ ከማኅፀነ ዮርዳኖስ እንደ እንደተወለደባት ቀን የነፃ አደርገዋለሁ፡፡ የዕዳ ደብዳቤውንም በእጅህ ትቀደው ዘንድ ለአንተ እሠጥሃለሁ፤ ዕድሜውንም በምድር ላይ አረዝምለታለሁ፤ ቤቱንና ንብረቱን ሁሉ እባርክለታለሁ፤ በተንኮል የሚከራከረው ቢኖር ድል እንዳይነሣው አሠለጥነዋለሁ፤ እግሮቹ እየተመላለሰ ወደ ቤተክርስቲያን የገሠገሠ ሁሉ በኢየሩሳሌም ሰማያዊት በኤዶም ገነት ውስጥ እንዲመላለስ አደርገዋለሁ፤ መባዕ የሚያገባ ሁሉ ጥቂትም ቢሆን ብዙም ቢሆን በእጅህ ከምሠራው ከቤተ መቅደሴ የሚያመጣውን መባዕ ሁሉ ቀኝ እጄን ዘርግቼ ከእጁ ፈጽሜ እቀበለዋለሁ፡፡ ከዕጣንም ወገን በየአይነቱ ያገባ ቢኖር እንደሰው ልማድ ሥጋዬን እንደቀባበት እንደ ኒቆዲሞስ ሽቱ እቀበለዋለሁ፣ በቢታንያ እንደቀባችኝ እንደ ማርያም እንተ ዕፍረት ሽቱ መዓዛውን አሸትለታለሁ፤ ስለ ማርያም እንተ ዕፍረት እስከ ዓለም ዳርቻ ሁሉ የመንግሥቴ ወንጌል በተሰበከበት ስሟን ይጠሩ ዘንድ እንዳዘዝኩ ሁሉ ትጉሃን በሚሆኑ በሰማያውያን መላእክት ከተሞች ስሙን ይጠሩት ዘንድ አዛለሁ፡፡ ለመብራት የሚሆን ዘይት ቢያገባ በይቅርታዬ ዘይትነት ራሱን አወዛዋለሁ፣ ሰውነቱ ለዘለዓለሙ አይሻክርም፣ ከፊቱም የብርሃን መብራት አይጠፋም፡፡ ወደ ሠርግ ቤት ከሚገቡ መብራታቸው ካልጠፋባቸው ከልባሞች ደናግል ጋር በመጣሁ ጊዜ በደስታ ይቀበለኛል፡፡››
1.6.2. በኢየሩሳሌም ሳለ ጌታችን የስቅለቱን መከራ በራእይ ካሳየው በኋላ የሰጠው ቃልኪዳን፡- ‹‹ለሌሎቹ ጻድቃን ከዚህ ዓለም በሞት በሚለዩበት ወቅት በፍጹም ልቡናቸው እንደሚገባ ያገለገሉኝን ዋጋቸውን ሰጠኋቸው፣ ለአንተ ግን በሞት የምትለይበት ጊዜ ሳይደርስ በሕይወትህ ሳለህ ኪዳንን ሰጠሁህ፡፡ ማደሪያህ ከጳውሎስና ከጴጥሮስ ጋር ይሆናል፡፡ አቀማመጥህ በቀኜ ነው፣ ደቀ መዛሙርቴን በ12 ወንበር ተቀምጣችሁ በ12ቱ ነገደ እስራኤል ትፈርዳላችሁ እንዳልኳቸው አንተም ወንበርህ ከወንበራቸው አያንስም፤ ብርሃንህ ከብርሃናቸው፣ ክብርህ ከክብራቸው አያንስም፤ ኪዳንህም ከሰጠኋቸው ኪዳን አያንስም፤ ርስትህ ዕድል ፈንታህ ከእነርሱ ጋር ነው፡፡ የሰጠሁህን ቃልኪዳንና ገድልህን የሚያቃልል ሁሉ ዕድል ፈንታው ከአንተ ጋር አይሁን፣ ርስት ጉልቱም ከአንተ ርስት ጉልት አይገኝም፤ የጸናሁልህን ቃልኪዳን የማያምን ያ ሰው እኔን ክርስቶስን እግዚአብሔር አይደለም እሩቅ ብእሲ ነው እንጂ እንደሚለኝ ሰው ይሁን፡፡ መጽሐፍህን ሰምቶ የተቀበለ ሁሉ የመንግሥቴን ወንጌል እንደተቀበለ ይሁን፤ አንተን ያከበረ እኔን እንዳከበረ ይሁን፡፡ ደቀ መዛሙርቴን እናንተን የሰማ እኔን የሰማ ነው፣ እናንተን የካደ እኔን የካደ ነው እንዳልኳቸው አሁንም አንተን የሰማ ቃልኪዳንህንም ያመነ እኔን ጌታህን የሰማ ነው እልሃለሁ፡፡ መከራህንና ቃልኪዳንህን የካደ ሰው ቢኖር እኔ በምድር የተቀበልኩትን መከራ እንደ ካደ ሰው ነው፡፡ ወንዶችም ሆኑ ሴቶች በጸሎትህ ኃይል የታመኑ ሁሉ ማደሪያቸው ከአንተ ጋር ይሁን፤ ለቤተክርስቲያኖችህ አምኃ የሰጠ ቢኖር እንደ ደሜ ፍሳሽ እንደ ሥጋዬ ቁራሽ አድርጌ እቀበለዋለሁ፡፡››
19.3.ቤተ መቅደሶቹን ሠርቶ ከጨረሰ በኋላ ጌታችን የሰጠው ቃልኪዳን፡- ቅዱስ ላሊበላ ጌታችን ባሳየውና ባዘዘው መሠረት አብያተ ክርስቲያናቱን አንጾ ከጨረሰ በኋላ በቀኝና በግራው ዓሥር ዓሥር ኪሎ የሚመዝን የዓለት ድንጋይ ተሸክሞ ለ7 ዓመት ሲጾም ሲጸልይ ከኖረ በኋላ ጌታችን ተገልጦለት በፊት የገባለትን ቃልኪዳን በዚህም ጊዜ በድጋሚ አረጋግጦለታል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ‹‹…ወደ ደጅህ የመጡት ሁሉ አስራት ይሁኑልህ፣ አንተ ከገባህበትም ይግቡ፣ አንተንም ከ12ቱ ሐዋርያት ጋር በፍርድ ቀን 13ኛ አደርግሃለሁ፡፡ ያነጽካቸውን ቤተ መቅደሶች የተሳለመውን ኢየሩሳሌምን እንደተሳለመ አደርግለታለሁ፤ መታሰቢያህን ያደረገውን፣ ገድልህን የጻፈውን ያጻፈውን፣ በዚህ ቦታ ላይ መጥቶ አማልደኝ ያለውን፣ በአማላጅነትህ የተማጸነውን ሁሉ እስከ 15 ትውልድ ምሬልሃለሁ›› ብሎ የመጨረሻውን ቃልኪዳን ሰጥቶታል፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን! እኛንም በአማላጅነታቸው የምንታመን ሁላችንንየመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን እና የቅዱስ ላሊበላን በረከታቸውን ያድለን በጸሎታቸው ይማረን አሜን!!!
(ምንጭ፡- ገድለ ቅዱስ ላሊበላ፡- የቅዱስ ላሊበላ ደብር በ2003 ዓ.ም ያሳተመው፣ ስንክሳር ዘወርሃ ሰኔ፣ ድርሳነ ሚካኤል ዘወርሃ ሰኔ)
ዳግም ምጽአት

ዳግም ምጽአት በቤተክርስቲያን አስተምሮ በዓመት አራት ጊዜ ቀን ተቆጥሮለት ጊዜ ተሰፍሮለት ይታሰባል ከነዚህ ዕለታት መካከል
በዓብይ ጾም እኩሌታ በደብረዘይት

በወርሃ ጷጉሜ ጓላ ባለ መልኩ ይታሰባል። ጌታችንም በደብረ ዘይት ተራራ ስለ ዳግም ምጽአት " እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ፥ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው። ንገረን፥ ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው? አሉት።" (የማቴ 24:3፤) ብለው ሐዋርያት በጠየቁ ጊዜ በስፋት አስተምራል ።

የመጀመሪያው ምጽአቱ (በግብር መምጣት)ሥጋ በመልበስ ለሰው መሥዋዕት ሁኖ ሊያድን ለካሳ በፍጹም ትህትና የእኛን ውርደት ተቀብሎ ወደዚች ዓለም ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ መለኮቱን ከእኛ ሥጋዊ ጋር አዋሕዶ በበረት በመወለድ መጣ።

ዳግማዊ ምጽአቱ (በኩነት)በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት በፍጹም ጌትነት በኃጥአን (የመጀመሪያ ምጽአቱን) ባልተቀበሉት ላይ ሊፈርድ ዐይን ሁሉ እየተመለከተው በገሃድ ይመጣል፡፡ ‹‹እግዚአብሔርስ ገሀደ ይመጽእ ወአምላክነሂ ኢያረምም እሳት ይነድድ ቅድሜሁ፣ እግዚአብሔር ግልጥ ሁኖ ይመጣል ዝምም አይልም እሳት በፊቱ ይነዳል (መዝ 49፡3) ለፍርድ የሚመጣው ከሦስቱ አካል አንዱ ወልድ ነው፡፡ በፍቃድ አንድ ስለሆኑ።የሚመጣውም ለፍርድ ስለሆነ እጅግ በጣም በሚስፈራ ግርማ ነው።

ጌታችንም በዚህች ምድር በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ሲመላለስ ሐዋርያት ሁሉን ትተው ተከትለውት ነበርና " ልባችሁ አይታወክ በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ።"በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፤ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፤" (ዮሐንስ 14:2፤) ብሉ ተስፋውን ከሐዋርያት ጀምሯል።

ቀዳማዊ ምጽአቱ ከልጅ ከልጅ ተወልጅ አድንሃለሁ ያለውን ቤተ አይሁድ በተስፋ ጠብቀውታል ። ክርስቶስ በመወለዱም የደነገጡ ደስ ያላላቸው እነሔሮድስ የአይሁድ ካህናትም ነበሩ በዳግም ምጽአቱም ደስ የማይላቸው " በዚያን ጊዜ መንግሥተ ሰማያት መብራታቸውን ይዘው ሙሽራውን ሊቀበሉ የወጡ አሥር ቆነጃጅትን ትመስላለች።"የሚደነገጡ ከአስሩ ደናግል መካከል በእኩለ ሌሊት ከእነርሱም አምስቱ ሰነፎች አምስቱም ልባሞች ነበሩ።"(ማቴ 25:2)

እነዚህን ሁሉ ምልክቶች ፣ማስጠንቀቂያዎች ፣ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ ፣ጽኑ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ በአእምሮ ጽላት ቀርፆ በማስተዋል በሃይማኖት እና በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ጸንቶ የኖረ የሕይወትን ቃል ሰምቶ የክብር፣የድልና የጽድቅ አክሊልን ተሸልሞ በዘላለማዊ ደስታ ይኖራል። ተስፋዎች የምናደርጋትን መንግስቱንና የምንጓጓላትን ርስቱን ለመውረስ መደንገጥ መንቀጥቀጥ ሳይሆን ንስሐ ገብተን ክቡር ሥጋውን ቅዱስ ደሙን ተቀብለን ተዘጋጅተን ልንጠብቅ ይገባል።
2024/05/03 02:26:55
Back to Top
HTML Embed Code: