Telegram Web Link
🕊

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ
አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡

❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖

ሰኔ ፲፯ [ 17 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

[ 🕊 ✞ አባ ገሪማ [ ይስሐቅ ] መደራ ✞ 🕊 ]

አቡነ ገሪማ የተወለዱት በ፭ [5] ኛው መቶ ክ/ዘመን ሮም ውስጥ ነው:: ወላጆቻቸው መስፍንያኖስና ሰፍንግያ እግዚአብሔርን የሚወዱ የሮም ከተማ ንጉሥና ንግሥት ነበሩ:: ልጅ በማጣታቸው እመቤታችንን ለመኑ፡፡

እመ ብርሃንም ደግ ፍሬ ሰጠቻቸው:: ስሙን ይስሐቅ ብለው አሳደጉት:: ገና በልጅነቱ አባቱ ድንገት በመሞቱ ይስሐቅ በዙፋኑ ተተክቶ ነገሠ:: ለ፯ [7] ዓመታት ሕዝቡን በፍትሕ እያስተዳደረ: መጻሕፍትንም እያጠና ኑሯል::

አንድ ቀን ግን ከግብፅ በርሃ የተላከ ደብዳቤ ደረሰው:: ላኪው አባ ዸንጠሌዎን ሲሆኑ መልዕክቱ "ምድራዊ ንግሥና ምን ያደርግልሃል? ይልቁኑስ በሰማይ ለዘለዓለም እንድትነግሥ ወደ በርሃ ና" የሚል ነበር::

ንጉሥ ይስሐቅ አላመነታም ሌሊት ተነስቶ ወደ ፈጣሪው ጸልዮ በለበሳት ልብስ ብቻ ዙፋኑን ጥሎ መነነ:: ድንገት ግን ቅዱስ ገብርኤል ደርሶ በቀኝ ክንፉ ነጥቆ ግብፅ አባ ዸንጠሌዎን በዓት ላይ አኖረው::

እርሳቸውም ተቀብለው ፍኖተ አበውን አስተምረው አመነኮሱትና ዘጠኝ ሁነው ወደ ኢትዮዽያ መጡ:: ተስዓቱ ቅዱሳን በሃገራችን ብዙ ሲሰሩ አንዱና ታላቁ አባ ይስሐቅ [ገሪማ] ናቸው:: ሰውነታቸውን በገድል ቀጥቅጠውት ቆዳና አጥንታቸው ተጣብቆ ነበር::

አንድ ቀን አባ ይስሐቅ በልቶ ቀደሰ ብለው ነግረዋቸው አባ ዸንጠሌዎን አዘኑ:: ልምከር ብለው "ልጄ ይስሐቅ የሰማውብህ ነገር አለና ሰዎችን አርቅልኝ" አሉ:: አባ ይስሐቅ ግን "ሰዎች ብቻ አይደሉም: ዛፉም እንጨቱም ገለል ይበል" ቢሉ የቤተ ክርስቲያኑ አጸድ አንድ ምዕራፍ ፰ መቶ ሜትር [800 ሜትር] ተጠራርጎ ሸሸ::

ይሕንን የተመለከቱት አባ ዸንጠሌዎን "ወልድየ ይስሐቅ ገረምከኒ  [ልጄ ይስሐቅ ገረምከኝ] አሏቸው:: ከዚያ ጊዜ ጀምሮም "አቡነ_ገሪማ" ተብለው ቀሩ፡፡

አቡነ ገሪማ ወደ መደራ ሲሔዱ እነዚያ የሸሹ ዛፍና ድንጋዮች "ገሪማ ለእኛም ግሩም ነህ" እያሉ በዝማሬ ተከትለዋቸዋል::

ጻድቁ ወንጌልን: ገዳማትን ከማስፋፋት ባለፈ ብዙ ተአምራትን ሰርተዋል :-

፩. ስንዴ ጠዋት ዘርተውት በ9 ሰዓት ያፈራ ነበር "በጽባሕ
ይዘርዕ: ወበሠርክ የአርር" እንዲል::
፪. ጧት የተከሉት ወይን በ9 ሰዓት ያፈራ ነበር::
፫. አንድ ቀን ምራቃቸው ቢወድቅ ጸበል ሆኖ ዛሬም አለ::
፬. ብዕራቸው ወድቃ አብባ አፍርታለች::
፭. አንድ ቀን ድርሳን እየደረሱ ሊመሽ በመሆኑ ፀሐይን
አቁመዋታል::

ከእነዚህ ሁሉ ዘመናት በኋላ ጌታችን ተገልጦ በማይዋሽ ንጹሕ አንደበቱ ቃል ኪዳን ሰጣቸው:: "ስምሕን የጠራ: መታሰቢያህን ያደረገ: እስከ ፲፪ [12] ትውልድ እምርልሃለሁ:: አንተ ግን ሞትን አትቀምስም" ብሏቸው ተሰወረ:: ያን ጊዜ መላእክቱ በሠረገላ ጭነው እየዘመሩ ብሔረ ሕያዋን አድርሰዋቸዋል፡፡

[ 🕊 ✞ አባ ለትጹን የዋህ ✞ 🕊 ]

ስመ ጥሩ ጻድቅ አባ ለትጹን በ፬ [4] ኛው መቶ ክ/ዘመን በግብጽ የተወለዱ:

- በፍጹም ተግሣጽ ያደጉ:
- ከልጅነታቸው ጀምሮ ራሳቸውን በሕገ ወንጌል የመሩ:
- አንድ ቀን በሰሟት የወንጌል ቃል የመነኑ:
- ገዳም ገብተው በትሕትና ለዘመናት ያገለገሉ:
- በመጨረሻም ወደ ትልቅ ተራራ ወጥተው ተጋድሏቸውን
የፈጸሙ ታላቅ አባት ናቸው::

ከየዋሕነታቸው የተነሳ ኃጢአተኛ ሰው ሲያገኙ ራሳቸው ንስሃ ይገቡ ነበር:: አንዴ ግን እናቱን ፲ [10] ጊዜ በዝሙት ያረከሰ: ስትጸንስም መርዝ አጠጥቶ ጽንሱን በማሕጸኗ የገደለና በሥጋ ወደሙ ላይ የተዘባበተ ሰው ሊሞት ሲል ደረሱ::

አጋንንት ሲዖል ታች ሲጥሉትም ተመለከቱ:: ኃጢአቱ ጭንቅ ቢሆንም የእርሱን ንስሃ ሊቀበሉ ጀመሩ: ከንስሃቸው ጽናት የተነሳ ሞቱ:: ጌታችን ከሞት አስነስቶ "አትለምነኝ: አልምረውም" አላቸው::

ጻድቁ ተስፋ አልቆረጡምና ቀጠሉ:: ለ፪ [2] ኛ ጊዜ ሞቱ:: አሁንም ቀጠሉ: ፫ [3] ኛ: ፬ [4] ኛ: ፭ [5] ኛ ጊዜም ሞቱ:: በ፮ [6] ኛው ግን መፍትሔ መጣ:: ጌታችን አእላፍ መላእክትን አስከትሎ: ያችንም ኃጥእ ነፍስ ይዞ መጣ:: "ፍርዴ አይታጠፍምና ወደ ገነት አላስገባትም:: ስለ አንተ ጽድቅና የዋሕነት ደግሞ ሲዖል አልጥላትም:: ስለዚሕም እንዳልተፈጠረች ትሁን" ብሎ እፍ አለባት:: ፈጥና ወደ ትቢያነት ተቀየረች::

ጻድቁም የፈጣሪያቸውን ቸርነት አድንቀው ሰገዱ:: ከብዙ ዘመናት ተጋድሎ በኋላም በዚህች ቀን ዐረፉ::

[ 🕊 ✞ አባ ዸላሞን ፈላሲ ✞ 🕊 ]

ቤተ ክርስቲያን ካፈራቻቸው ታላላቅ ገዳማውያን አንዱ አባ ዸላሞን የአባ ለትጹን ወዳጅ ነበር:: ይሕ ቅዱስ ከአጋንንት ጋር በገጠመው ጦርነት ምክንያት ለየት ይላል:: ከ፷ [60] ዓመታት በላይ እንኳን ሳቅና ደስታ ቀና ብሎም ሰው አላየም::

በነዚሁ ዘመናት ሁሉ ቅንድቡ እስኪላጥ አልቅሷል:: በዓለም ያሉ አጋንንት ሁሉ ተሰብስበው አሰቃይተውታል:: እርሱ ግን በእግዚአብሔር ቸርነት: በወዳጁ በአባ ለትጹን ጸሎትና በትጋት አሸንፏቸው ዛሬ ዐርፏል::

ቸሩ አምላካችን ከታላላቁ ቅዱሳን ጸጋ በረከት ይክፈለን:: በምልጃቸውም ይቅር ይበለን::

🕊

[ †  ሰኔ ፲፯ [ 17 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ብጹዕ አባ ገሪማ [ይስሐቅ] ዘመደራ
፪. አባ ለትጹን ዐቢይ ወየዋሕ
፫. አባ ዸላሞን ፈላሲ
፬. ቅድስት አርሴማ ጻድቅት
፭. ሰማዕታት እለ አኮራን
፮. ፯፼ ፹፻ ሰማዕታት ማኅበረ ቅዱስ ተክለሃ ይማኖት

[ †  ወርኃዊ በዓላት ]

፩ ፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ ቀዳሜ ሰማዕት
፪ ፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ዘቆጵሮስ
፫ ፡ ቅዱሳን መክሲሞስ ወደማቴዎስ
፬ ፡ ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ

" እግዚአብሔር ፍርድን ይወድዳልና::ቅዱሳኑንም አይጥላቸውምና:: ለዘለዓለምም ይጠብቃቸዋል. . . ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ:: በእርስዋም ለዘላለም ይኖራሉ::የጻድቅ አፍ ጥበብን ያስተምራል:: አንደበቱም ፍርድን ይናገራል::የአምላኩ ሕግ በልቡ ውስጥ ነው:: በእርምጃውም አይሰናከልም:: " [መዝ. ፴፮፥፳፰-፴፩] (36:28-31)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
5
4
                         †                         

የእሥር ዜናዎች !

▬▬▬▬▬▬   †    ▬▬▬▬▬▬

በናዳ ማርያም ገዳም ለበርካታ ዓመታት ጉባኤ ዘርግተው በማስተማር ላይ የሚገኙት ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ የኔታ ይባቤ መታሰራቸው ተገለጸ !

ሰኔ 14 ቀን 2017 ዓ.ም [ተሚማ/ አዲስ አበባ]

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰሜን ጎጃም ሀገረ ስብከት ሰሜን ሜጫ ወረዳ ቤተ ክህነት ድል በትግል ቀበሌ የምትገኘው የፈለገ ብርሃን ናዳ ቅድስት ማርያም እና ክብረ ደናግል ናዳ ቅዱስ ላሊበላ አንድነት ገዳም አበምኔት የሆኑት ታላቁ ሊቅ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ በትናንትናው ዕለት  መታሠራቸውን ለማወቅ ችለናል።

የመረጃ ምንጬቻችን ጨምረው እንደገለፁልን ለጊዜው ምክንያቱን በግልጽ ለማወቅ ባይቻልም ለጥያቄ ይፈለጋሉ ተብለው መወሰዳቸውን ገልጸውልናል።

ከ1979 ዓመተ ምሕረት ጀምሮ ወንበር ዘርግተው ጉባኤ ተክለው ለ38 ዓመታት ቅኔና የቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜን ያስተማሩት እኚህ አባት አሁንም በማስተማር  በርካታ ደቀመዛሙርትን ያስመረቁ የክብረ ደናግል ቅዱስ ላሊበላ አንድነት ገዳም መሥራችና አበምኔት /አስተዳዳሪ ናቸው።

ጉዳዩን ተከታትለን ተጨማሪ መረጃዎችን የምናደርስ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን።

[ ዘገባው የተ.ሚ.ማ ነው ]

እንዲሁም ሊቀ ትጉኃን ደረጀ ነጋሽ [ ዘወይንዬ ] ለጥያቄ ተፈልገዋል በሚል መወሰዳቸው ተገልጿል።

         †              †               †
▬▬▬▬ ▬▬▬▬▬ ▬▬▬▬
                       †                           

†    🕊  መንፈሳዊው መሰላል  🕊   †


              [   ክፍል  አርባ  ]

▬▬▬▬▬▬   ♱    ▬▬▬▬▬▬

❝ ከመናፍስት ጋር በሚደረግ ተጋድሎም ርዳታ ለማግኘት የማይጥር ሰው በእነርሱ ይገደላል፡፡

ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሐኪም ቤት የሚገቡ ሕመማቸውን [ ጉዳታቸውን ] ያሳዩ ፣ ወደ መታዘዝም የሚገቡ ትሕትናቸውን ያሳዩ፡፡

ሕሊናህ የመታዘዝህ መስታወት ይሁን ፣ ይህም የሚበቃ ነው፡፡ ለአባታቸው እየተገዙ በአጽንኦ በአት [ በጸጥታ ] ለሚኖሩ እነርሱን ተቃውመው የሚሠሩት አጋንንት ብቻ ናቸው፡፡ ዳሩ በማኅበር የሚኖሩ ግን ከአጋንንትና ከሰው ልጆች ጋር ይታገላሉ፡፡

የፊተኞቹ [ በአጽንኦ በኣት የሚኖሩት ] ሁሌም ከመምህሩ ዕይታ ሥር ናቸውና ትእዛዛቱን አጽንተው ይጠብቃሉ ፤ የኋለኞቹ [ በማኅበር የሚኖሩት ] ግን ከእሱ አለመኖር የተነሣ በመጠኑ ይጥሷቸዋል፡፡ ሆኖም ይህን ውድቀት አብልጠው ያካክሱ ዘንድ ግጭቶችንና መጸፋቶችን ታግሰው ቀናተኛና ትጉ የሚሆኑ እንዲሁ እጥፍ አክሊላትን ይቀዳጃሉ፡፡

በጥንቃቄ ሁሉ ራሳችንን እንጠብቅ፡፡ ወደቡ በመርከቦች ተሞልቶ ሳለ እርስ በርስ ለመጋጨት ቀላል ነውና ፣ በተለይ ሳይታወቅ በክፉ ጠባይ ትል የተበሳሱ ከሆነ፡፡

በበላዩ ፊት እጅግ ፍጹም የሆነ አርምሞንና አላዋቂነትን እንተግብር ፣ ዝምተኛ ሰው ሁሌም የበዛ እውቀትን የሚያገኝ የፍልስፍና [ የጥበብ ] ልጅ ነውና፡፡ ❞

[ ዮሐንስ ክሊማኮስ [ ቅዱስ ዮሐንስ ዘሰዋስው ]


🕊                      💖                     🕊
3
4
💛
▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬

🕊     ም ክ ረ     ቅ ዱ ሳ ን     🕊

▷  " አንተነትህ በእግዚአብሔር ፊት ! "

[   " ብፁዕ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ ... ! "   ]

[                        🕊                        ]
-----------------------------------------------

❝ እኔ መተላለፌን አውቃለሁና ፥ ኃጢአቴም ሁልጊዜ በፊቴ ነውና። አንተን ብቻ በደልሁ ፥ በፊትህም ክፋትን አደረግሁ ፥ ❞

[ መዝ . ፶፩ ፥ ፫ ]


🕊                        💖                     🕊
                             👇
5
4🥰1
🕊

† እንኳን ለጻድቅ ሊቀ ጳጳሳት አባ ድምያኖስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን። †

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ! †

🕊  †  አባ ድምያኖስ   †   🕊

†  አባ ድምያኖስ ተወልደው ያደጉት ግብጽ ውስጥ ነው:: ቤተሰቦቻቸው ክርስቲያኖች በመሆናቸው ገና በልጅነት ዕድሜአቸው ቅዱሳት መጻሕፍትንና በጐ ምግባራትን ተምረዋል:: ዕድሜአቸው ወደ ወጣትነቱ ሲጠጋ ሥርዓተ መነኮሳትን ለማጥናት ወደ ገዳመ አባ ዮሐንስ ሔዱ:: በዘመኑ ማንኛውም ሰው ተገቢውን ፈተና ሳያልፍ እንዲመነኩስ አይፈቀድለትም ነበር::

አንድ ሰው ሊመነኩስ ካሰበ በትክክል መናኝ መሆኑ ቢያንስ ለሦስት ቢበዛ ደግሞ ለአሥራ ሁለት ዓመታት እንዲፈተን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታዝዛለች:: ይኸውም "ሥርዓተ አመክሮ" ይባላል:: ከአሥራ ሁለት ዓመታት በላይ መቆየት ከፈለገ ግን ይፈቀድለታል::

በዚህም መሠረት አባ ድምያኖስ ለአሥራ ሰባት ዓመታት በአጭር ታጥቀው ገዳሙን አገልግለዋል:: ገዳሙም ይገባሃል በሚል ዲቁና እንዲሾሙ አድርጓል:: ከዚህ በኋላ ከአባቶች ተባርከው: ገዳሙንም ተሰናብተው ወጡ:: ነገር ግን የወጡት ወደ ዓለም ሳይሆን ራቅ ወዳለ ገዳም ነው::

የረድዕነት ዘመናቸውን ጨርሰዋልና አዲስ በሔዱበት ገዳም ወደ መደበኛው ገድል ተሸጋገሩ:: ያም ማለት በጾም: በጸሎት: በስግደት: በትሕርምት: በትሕትናና በፍቅር ሙሉ ጊዜአቸውን ማሳለፍ ጀመሩ:: በእንዲሕ ያለ ግብርም ዘመናት አለፉ::

የወቅቱ የግብጽ ፓትርያርክ አባ ጴጥሮስ በእረኝነት ሥራ የሚያግዛቸው ሰው እንዲፈለግላቸው በጠየቁት መሠረት ትምሕርትም: ጽሕፈትም: በጐ ምግባራትም የተሟላለት ሰው እንደ አባ ድምያኖስ አልተገኘምና ያለፈቃዳቸው ወደ እስክንድርያ ተወስደው የፓትርያርኩ ረዳት ሆነው ተሾሙ:: በረዳትነት በቆዩበት ጊዜ በወንጌል አገልግሎትና በመንኖ ጥሪት ሕዝቡንና ሊቀ ጳጳሳቱን አስደስተዋል::

ልክ አባ ጴጥሮስ ሲያርፉ ሕዝቡና ሊቃውንቱ በአንድ ድምጽ አባ ድምያኖስን ለፓትርያርክነት መርጧቸዋል::

ጻድቁ ሊቀ ጳጳሳት በዘመነ ፕትርክናቸው ከግል የቅድስና ሕይወታቸው ባለፈ እነዚህን ፈተናዎች በመወጣታቸው ይመሰገናሉ::

፩. ሕዝቡ ከሃይማኖታቸው እንዳይወጡና በምግባር እንዳይዝሉ ተግተው አስተምረዋል::

፪. በአካል ያልደረሱባቸውን በጦማር [በመልዕክት] አስተምረዋል::

፫. በዘመናቸው የተነሱትን መናፍቃን ተከራክረው : የተመለሰውን ተቀብለው : እንቢ ያሉትን አውግዘዋል::

፬. ከአንጾኪያ ፓትርያርክ የመጣውን የኑፋቄ ጦማር [መልዕክት] በይፋ ተቃውመው አውግዘዋል::

ለአርባ ሦስት ዓመታት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ሆነው ያገለገሉት አባ ድምያኖስ ከብዙ ትጋት በኋላ በመልካም ሽምግልና በዚህች ቀን ዐርፈዋል:: ከግብጽ አበው ሊቃነ ጳጳሳት ዝርዝር ውስጥም አርባ አምስተኛ ሆነው ተመዝግበዋል::

† ልመናቸው : ክብራቸው : ጸጋ ረድኤታቸው አይለየን::

🕊

[ †  ሰኔ ፲፰ [ 18 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. አባ ድምያኖስ ጻድቅ ሊቀ ጳጳሳት
፪. ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት

[ †  ወርኀዊ በዓላት ]

፩. ቅዱስ ፊልጶስ ሐዋርያ
፪. አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ሰባኬ ሃይማኖት [ረባን]
፫. አቡነ አኖሬዎስ ዘደብረ ጽጋጋ
፬. ማር ያዕቆብ ግብጻዊ

" ስለዚህ በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያንን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት : ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ:: ከሄድሁ በኋላ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ተኩላዎች እንዲገቡባችሁ እኔ አውቃለሁ:: ስለዚህ ሦስት ዓመት ሌሊትና ቀን በእንባ እያንዳንዳችሁን ከመገሰጽ እንዳላቋረጥሁ እያሰባችሁ ትጉ:: " † [ሐዋ. ፳፥፳፰]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
5
4
#ወዳጆቼ___?

#ኃጢአ መሥራት በራሱ አስቀያሚ ነው፤ ኃጢአት ከሠሩ በኋላ በዚያ ኃጢአት መታበይ ግን እጅግ #ጽኑ_ደዌ ነው፡፡ #ጽድቅን ሠርተው በዚያ በሠሩት ጽድቅ #ከተኩራሩበት ጽድቁን ያጡታል፡፡ ይህ በኃጢአት ሲኾን ደግሞ የባሰ ነው፤ ወደ ከፋ ጥፋት ይወስደናልና፡፡ ከሠራነው #ኃጢአት ይልቅ በሠራነው ኃጢአት መታበይ የሚያመጣው ፍዳ ኵነኔ እጅግ #ጽኑ ነውና፡፡

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

#መልካም_ቀን🙏

አጫጭር ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቶች
•➢ 👇 ለማግኘት // 👇

@Enatachn_mareyam
@Enatachn_mareyam
7🙏5
🕊

†  እንኩዋን ለሐዲስ ሰማዕት ቅዱስ ጊዮርጊስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ  †

🕊  †  ቅዱስ ጊዮርጊስ ሐዲስ  †  🕊

ሰማዕቱ የተወለደው በምድረ ግብጽ አሕዛብ [ተንባላት] በሰለጠኑበት የመጀመሪያው ዘመን ነበር:: በተለይ ተንባላቱ ግብፅና ሶርያን ከያዙ በሁዋላ ባልተጠበቀ ፍጥነት በኃይልም በሰውም ተደራጅተው ነበር:: ቅዱስ ጊዮርጊስ [ልብ በሉልኝ ሊቀ ሰማዕታት አይደለም] የተወለደው በዚህ አስቸጋሪ ጊዜ ነበር::

እናቱ የተመሠከረላት ክርስቲያን ብትሆንም እንዳለመታደል አባቱ ተንባላታዊ [አሕዛብ] ነበር:: ስሙንም መዛሕዝም ይሉታል:: ሕጻኑ እንደተወለደ ያወጡለት ስም አሕዛባዊ ከመሆኑ ባለፈ በሰዓቱ መጠመቅ አልቻለም:: የወቅቱ ሕግ ከወላጆቹ አንዱ አሕዛባዊ ከሆነና አጠምቃለሁ ቢባል የሚከተለው ሰይፍ ነበር:: በዚሕ ምክንያት ሳይጠመቅ ፯ [7] ዓመት ሞላው::

እናቱ ግን ሕጻን ቢሆንም ፍቅረ ክርስትናን ታስተምረው ነበር:: ባይጠመቅም ጸበሉን: እመቱን ትቀባው ነበር:: ደብቃ ቅዳሴ ታሰማውም ነበር:: አንድ ቀን ግን ሕጻናት ሲቆርቡ አይቶ ካልቆረብኩ ብሎ አለቀሰ:: ምን ታድርገው? ወደ ውጪ አውጥታ ከአውሎግያ [የሰንበት በረከት] አበላችው:: "ጌታየ! ልጄን እርዳው" አለች::

ልክ በአፉ ሲቀምሳት መዓዛ መንፈስ ቅዱስ አደረበትና ፍጹም ተደሰተ:: ትንሽ ከፍ ሲል ለምን እንደማይጠመቅና እንደማይቆርብ እናቱን ጠየቃት:: "ልጄ ሆይ! ይገድሉሃል" አለችው:: ከዚህች ቀን ጀምሮ የሚጠመቅበትን ዘዴ ይፈልግ ጀመር::

አስቀድሞ ትምሕርተ ክርስትናን ተማረ:: ለአካለ መጠን ሲደርስ አፈላልጐ ጠንካራ ክርስቲያን የሆነች ሴት አገባ:: ጥቂት ጊዜ ከቆየ በሁዋላ ሚስቱን ስለ መጠመቅ አማከራት:: "ሌላ ሃገር ሒደህ ተጠመቅ" አለችው:: ከግብፅ ተነስቶ ሶርያ ገባ:: አባቶችን አፈላልጎ ተጠመቀ:: ቀጥሎም መንገዱን ወደ ልዳ አደረገ::

ወደ ደብሩ ተጠግቶ አባቶችን "ስም አውጡልኝ" ቢላቸው መንፈስ ቅዱስ አናግሯቸው "ጊዮርጊስ" አሉት:: እሱም ደስ እያለው: ባጭር ታጥቆ የልዳውን ቅዱስ ጊዮርጊስ ያገለግለው ገባ:: ትንሽ ቆይቶ ሁከት መንፈሳዊ ተሰማው:: ማለትም ስለ ሃይማኖቱ ደሙን ማፍሰስ ፈለገና ወደ ግብፅ ተመለሰ::

በዚያ ያሉ አሕዛብ በክርስትና ስም: ልብስና ሞገስ ሲመለከቱት ተበሳጩ:: ዕለቱኑ አሠሩት:: ሌሊት እናቱና ሚስቱ መጥተው አሉት:- "አደራ! ፍቅረ ዓለም እንዳያታልልህ:: ሰማዕት ብትሆን ላንተም ክብር: ለእኛም ሞገስ ነው" ብለውም አጽናኑት:: [ እንዲሕ ያሉ እናትና ሚስት ማግኘትም ታላቅ እድል ነው!!! ]

ሐዲስ ጊዮርጊስም ጸና:: ከዚያች ቀን ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ደበደቡት: አካሉን ቆራረጡት: ደሙንም መሬት ላይ አንጠፈጠፉት:: በየመንገዱ እየጎተቱ ተሳለቁበት:: እርሱ ግን ክርስቶስን ወዷልና ሁሉን ታገሰ:: ሌሊት በሆነ ጊዜም ጌታችን ተገልጦ "ከሰማዕታት ተቆጠርህ" አለው::

በማግስቱ በአደባባይ አንገቱን በሰይፍ ቆረጡት:: ክፋታቸው የጸና ነውና ሥጋውን በእሳት አቃጠሉት:: ወደ ባሕርም ጣሉት:: እናቱ ከባሕር ስታወጣው ግን ምንም አላገኘውም ነበር:: በዚሕች ቀን እናቱና ሚስቱ በክብር ቀብረውታል::

ቸሩ አምላክ ከሰማዕቱ ጽናትን: ትእግስትን: ጸጋ በረከትን ይክፈለን::

🕊

† ሰኔ ፲፱ [ 19 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

፩. ቅዱስ ጊዮርጊስ ሐዲስ ሰማዕት
፪. አባ ብሶይ አኖብ ሰማዕት [ በአንበሳ ጀርባ ላይ የተቀመጠ አባት ]
፫. ቅዱሳን ፭ቱ "5ቱ" ጭፍሮች [ በብዙ ስቃይ ሰማዕት የሆኑ ባልንጀሮች ]
፬. አባቶቻችን የደብረ ቁዋዐት ጻድቃን

[ †  ወርሐዊ በዓላት ]

፩. ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት
፪. ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት
፫. አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ
፬. አቡነ ስነ ኢየሱስ
፭. አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም

" ስለዚሕ ወንድሞቼ ሆይ ! ጣዖትን ከማምለክ ሽሹ:: ልባሞች እንደመሆናችሁ እላለሁ:: በምለው ነገር እናንተ ፍረዱ:: የምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? የምንቆርሰውስ እንጀራ ከክርስቶስ ሥጋ ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን ? . . . እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ ሥጋ  ነን:: ሁላችን ያን አንዱን እንጀራ እንካፈላለንና:: " [፩ቆሮ.፲፥፲፬-፲፰] (10:14-18)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
4
2025/07/11 18:54:09
Back to Top
HTML Embed Code: