Telegram Web Link
ማንአልሞሽ ዲቦ አልበም ውስጥ 7ተኛው ዘፈን የሚያሳዝን፣ የማያስጨፍር፣ ዘመናዊ የፍቅር ዘፈን ነው።
ቤት አሰርቼለት በልቤ ከተማ
ሳይሞሸርበት መሄዱ ተሰማ
ተቀጣሁ ተቀጣሁ በፍቅር ተቀጣሁ
ላልጨርስ ጀምሬው የልቤን እያጣሁ
ተው በሉት ተው በሉት ተው በሉት ያን ሰው
ማን አላት ብሎ ነው እንባዬን የሚያፈሰው

የሚል።

እና 8ተኛው ዘፈን ላይ ወደጭፈራዋ ትገባለች። አሳ በለው... ደሞ የጎንደር ሰው እያለች።

ግን ያቺ ሰባተኛ ዘፈን ትንግርት ናት። አትገጥምም፣ አትሄድም። እና እውነት የምትባል ነገር እንደዛ ትመስለኛለች
@coffeeandscribblings
ጠረንሽን ከአፍንጫዬ የቱ ንፋስ አመጣው? የጸጉርሽ ቀለም በአይኖቼ የሳለው የቱ ሰዐሊ ነው? በተቀመጥኹበት ናፍቆትሽ እንደዝናብ ወረደብኝ። በመላ ሰውነቴ... በመላ አቅሜ... በመላ የስሜት ህዋሳቶቼ ናፈቅሽኝ።

አይኖቼ
የማር ወለላ የመሰለ የቆዳሽን ቀለም ይናፍቃሉ። ጸጉርሽን የተቀባሽው ቡኒ፣ ከሰውነትሽ ቡኒ ይለያል። የአይንሽ ቡኒ ከጸጉርሽ ቡኒ ይለያል። ያ ቡኒ ሹራብሽ ከሌሎቹ ቡኒዎች ሁሉ ይለያል። የመዐት ቡኒዎች ስብጥር ነሽ። ሀገሬን ሳስባት በቡኒ ነው። የጠይሞች መዐት ከላይ ከሳተላይት ስትታይ ቡናማ ያደረጋት ይመስለኛል። አባይ አፈር እየጠረገ ሲቻኮል የሚፈስ ቡኒ ነገር። ሰዎቿ ሁሉ የሚያንቃርሩት ቡና። እና የአንቺ ቡኒ ግን ከሁሉ የሚለይ። የመዐት ቡኒ ስብጥር።

ጥርሶችሽ የአይኖቼ ጥማት ናቸው። ተሰድረው እንደፈንዲሻ ናቸው። ፈንዲሻ ይሰደራል? ጨዋ ፈንዲሾች። ወታደራዊ ፈንዲሾች።
ሳቅሽ ሲፈነዳ እጃቸውን ጥምር ጥምር አድርገው ብቅ የሚሉ ፈንዲሾች። ጥርስሽ ላይ አልሳምኩሽም።

ጆሮዎቼ
እርምጃሽን ይናፍቃሉ። ቸኮል ቸኮል። ነጠቅ ነጠቅ። ጣጣ። በእርምጃሽ መምጣትሽን አውቃለሁ። ''ሄሎ'' የሚል የሚጎተት ድምጽሽን ይናፍቃሉ። ቀጭን። ቃላቶችሽን በስንፍና የምታወጪ... 'ቀ'ዎችሽ የላሉ። 'ጨ'ዎችሽ የላሉ። 'ደ'ዎችሽ የላሉ። በሸክመ ቀሊል እገዛ ዘንድ ፊደሎችሽ ባደረገኝ። 'ውሸታም።' 'ቲስ' 'ኤ' የምትይው ሁሉ ይናፍቃሉ። ደግሞ በጣም ስትስቂ መኃል ላይ ዋይ ብለሽ የምትጮኺው ነገር።

አፍንጫዬ
የሽቶ ጠረንሽን ይናፍቃል። የእጣንሽን። ከሰል ስታያይዢ የሚመጣውን የአዲስ ከሰል መቀጣጠል ሽታ። የቲማቲም ስልስሽ። (ያለቲማቲም ስልስ አታውቂም?) የቡናሽ። የአልጋሽ ሽታ። እስክትመጪ አልጋሽ ላይ ተደግፌ ስጠብቅሽ የሚያጽናናኝ። ትራሶችሽ።

ምላሴ
ቲማቲም ስልስሽን ይናፍቃል። ቡናሽን። ቅቅልሽን። ቡላሽን። ስሰናበትሽ በአፌ የገባውን የእንባዬን ጣዕም ይናፍቃሉ።

ልቤን ደስ ያሰኘኝ ወቅት ከአንቺ የነበርኹበት ነው። ደስታዬ መልክና ቁመት ቢኖረው አንቺ ነሽ። የምናፍቀው አንቺን ብቻ ሳይሆን እኔንም ነው። ሌላ ነበርሁ።

የማይገኝ ነገር ነው። ዘመኑም። ሰዉም። እህሉም ውኃውም የሌላ አለም ነው የሚመስለኝ። አለመታደል ነው።

@coffeeandscribblings
Forwarded from Reddit History
In 1956 Marilyn Monroe said that she'd like to try act in something "like Dostoevsky's Karamazov". The press mocked her. One guy even challenged her to spell Dostoevsky. This reporter tried to catch her sounding stupid but instead Marilyn responded with a zinger.
https://redd.it/16paejo
Something worth watching. A masterpiece actually.
Beautiful songs. Amazing actress with ፍንጭት. Such an artist in every scene.
Every take done so masterfully.
Beautiful. Just beautiful.
@coffeeandscribblings
Mawlid al nabi mubarak!
የስንብት ቀለማትን አንብቤ ጨረስኹ። በአራት ወር። መሽቶ ነግቶብኝ ድጋሚ መሽቶ ነግቶብኝ መጻሕፍት አፍቃሪዎች አቦል እና ቶና ጠጥተው በረካ ላይ መድረሴ አልጠፋኝም። ግን ወፍራም ቡና ነው።
ከሰባት አመት በፊት መጽሐፉን የሰጠኝ ልጅ:-
ከስጦታዎች ሁሉ መጻሕፍት ይልቃሉ። ከዘመናችን ደራሲያን ሁሉ አዳም ረታ ይልቃል።
ብሎ ጽፎበታል።
አፌ ቁርጥ ይበልለት።
አዳም ከባድ ደራሲ ነው። ባነነብኸው ቁጥር የበላቸው መጻህፍት ብዛት ይታይኃል። አፉ ዙሪያ ወረቀቶች ተለጣጥፈው ቀለም ሲያጋሳ ምናምን። ፖለቲካ፣ ፍልስፍና፣ አፈ ታሪክ፣ ማህበራዊ ሀሳቦች፣ ፍቅር፣ ሀይማኖት፣ ስነ ጽሁፍ ምናምን በቃ። ሁሉም አለበት።
ደግሞ ማንም ያልደፈረው ያ ውዥንብሩ ያልጠራበት በታሪክ መኃል ባዶ ቦታ የመሰለ የሰማንያዎቹ አጋማሽ ነው መቼቱ። ወላ ብዙ ያላሰብኸው ነገር ነበር።
ከሁሉ የወደድኹት ዮሐንስ ወላይሶ የተባሉት ገጸ ባህርህ በቀይ በቀይ ከታች የሚጽፏቸውን ነገሮች ነው።

ደግሞ ሌላ የገረመኝ ተኮላ የሚባለው የአንጀት ተውሳክ አጋጥሞት ደግሞ ደግሞ ሲፈሳ ፈሶቹ ሁሉ በሙዚቃ ኖታ መጻፋቸው ነው።
አንዲት ኮልታፋ ልጅ ረዥም ሰዐት ስታወራ ሲጽፍ ወላ 20 እና 30 ገጽ አንድ ሳያዛንፍ ኩልትፍናዋን ጠብቆ ነው። ተዐምር ነው። ጽናት። የማለ ይመስል። ቀኝ እጁን ወደላይ አንስቶ... በግድየለሽነት አንዲት ቃል ላልጽፍ... ምናምን።

የውሾች ዜና መዋዕል አለው።

ድንቅ ነው። ለአንባቢህ እንዲህ መወዝወዝ። አይገባውም ተብሎ የሚታለፍ ነገር የለም። ጊዜ አለ። አዳም አለ። ወረቀት አለ። ብዕር አለ። መጻፍ ነው።

በዚህ ጊዜ የሚጽፍ ሰው መሆን እዳም ነው እድልም ነው። በአዳም ጽሁፎች ተገፍተን ግማሽ መንገድ ወጥተናል። እዳ የሆነው እሱ እንዲህ እየጻፈ እኛ ብንጽፍ ለሯጭ ማንቧቸር ለተናጋሪ መኮላተፍ ነው።
ብቻ ይሁን። አመሰግናለሁ። ላበረታታችኹኝ። ለሰጠኸኝ ይሄን መጽሐፍ አመሰግናለሁ። ቅርስ ነው።

በአዕምሮዬ በፊቴ ለተደቀኑ መዐት ድምጽ ማጉያዎች ነው የማወራው።
@coffeeandscribblings
ለምን ሮሚዮ ሆንህ ትላለች የሼክስፒሯ ዡልየት። አባትህን ካድ፣ ስምህን ግደፍ ትላለች። የዋህ ናት። አይፈረድባትም። አንድም አፍቅራለች ደግሞም 15 አመቷ ነው። ዘግናኝ ሁኔታ ነው በእውነቱ።
ትቀጥላለች። እንደምትወደኝ ከማልኽልኝ እኔ ደግሞ ስሜን እክዳለሁ ትላለች። የዋህነት። ኧረ ተይ።
በስም ምን አለ? ጽጌረዳን ምንም ብለን ብንጠራው ሽታው ይቀየራል ወይ? እናማስ ሮሚዮ ሮሚዮ ባይባል ፍጹምናውን አይቀጥልም ወይ? ኧረ ሮሚዮ ስምህን ግደፍ። በስምህ ፈንታ ሁለመናዬን ተረከብ ትላለች።

ጽጌሬዳ ቅንቡርስ ቢባል ምንም አይሆንም። የሰው ልጅ ግን ስሙ ብዙ ነገሩ አይደለም?
@coffeeandscribblings
መልካም የመስቀል በዓል!

Follow capturing authenticity for authentic pictures like this. (It is my sister btw)
https://instagram.com/capturing_authenticity_?igshid=MzRlODBiNWFlZA==
ስሟን ስጠይቃት አሰብ አድርጋ ነው የነገረችኝ። 'ኢማን'

ኢማን በጣም ቆንጆ ቡና ታፈላለች። የሚሸጥ አይመስልም። 10 ብር ያንሰዋል። (ያኔ ቡና 10 ብር ነበር።) ከዝርዝር ጥርሶቿ እና ድብን ተደርጎ ከተነቀሰ ጥርሷ ፈገግታ አይጠፋም። የማስባት በእጆቿ ላይ ጀበናዋን እንዳንጠለጠለች ነው።
የምግብ ቤቱ በር ላይ ትልቅ ረከቦቷን ዱብ አድርጋ፣ ከጀርባው ሁሌ እንደተንጎዳጎደች ነው። እየተንጎዳጎደች ካልሆነ በእጇ ትሪና ጀበናዋን ይዛ ቡና ያዘዘውን ሰው እየፈለገች ነው። እየፈለገች ሳለች ደግሞ ሰው ደግሞ ትዕዛዝ ይወረውርባታል። "እዚህ ጋር ሁለት ቡና"፣ "ኤይ አንድ ሻይ" ምናምን።

ግን ፈገግ ትልልኛለች። በግርግር መኃል ምናምን ቡና ስትቀዳልን ፈገግታዋ አይቀርም። ደግሞ ሮዚ ነው የምትለኝ። አላርማትም። ሮዚ ብሆን ምን ጨነቀኝ አይከፋም።

ኢማን ቆንጆ ቡናዋን ከእጣንና ጤናአዳም ጋር ነው የምታቀርበው። እሷ ከሄደች ወዲህ እንዲህ ያለ አለም የለም። ደግሞ እስከአፍ ጢሙ። የፍቅሯን። በቃ ፈሰሰ እኮ እስክላት።


እኔና ሔለን ቅዳሜ ጠዋት መጥተን ቁጭጭጭጭ ብለን ቁርሳችንን በልተን ደግሞ አጥንተን ደግሞ አውርተን ስንቆይ... መአት መአት ስኒ ቡና ነው የምንጠጣው። በቃ ሳቋ አይቆምም። እንደቡናው ነው የሚፈሰው።

''ስኳር ላቆም ነው በቃ ከዚህ ወዲህ ባዶ ነው የምትቀጂልኝ።'' አልኳት አንድ ቀን።
''ሮዚ ባዶ።'' እያለች ስኳር እንዲጎመዝዘኝ የረዳችኝ እሷ ናት።

ጠዋት 1:45 ሄጄ ኢማን ቡና ኡኡ ስልባት እየሳቀች 1:50 ቡናዬን ታስኮመኩመኛለች። 2:00 ላይ 'A bright day, ain't it?' እላለሁ ስራ ቦታ።

ዛሬ አለምአቀፍ የቡና ቀን ነው። ለምን እንደሆነ የሚያከብሩት አላውቅም። ቀጠናዊ የቡና ንግድ ትስስር ለማዳበር ምናምን ይሆናል። አላውቅም።

ለኔ ቡና ግን እናቴ በልጅነቴ ካሳየችኝ በተጨማሪ ( እናቴ፣ ቡና አብሮኝ ነው ያደገው። ታናሽ ወንድሜ ይመስለኛል ትላለች።) እነዚህ ጠያይም ሴቶች ጎልያድን የሚያህል ኑሮን ተገዳድሮ ለመጣል የሚወረውሩት ድንጋይ ነው። ሲቆሉት፣ ሲያፈሉት፣ ሲያቀርቡት ቆንጆ ጠያይም ፊታቸውን የሚገርፍ እሳት አለ። ቻል ያደርጓታል። የሚከፏት ቀናት አሉ ኢማን። መቼም የማላውቃቸው። አንድ ቀን ስሄድ በኢማን ቦታ ሌላ ሴት ስትንጎዳጎድ አገኘሁ። ኑሮ ነውና አይ ኢማንዬ የት ገባች እያልሁ የአዲሲቱን ቡና ሸረር አድርጌያለሁ።
ሀጢያት ነው? ነው።
ይድረስ ለእህቴ ለማላውቅሽ ያስብለኛል አንዳንዴ።

(ይድረስ ለእህቴ ለማላውቅሽ
ለምታይኝ ለማላይሽ
ቡናሽን እየጠጣሁ ከወደየት ነሽ የማልልሽ
በልፋትሽ ደምቄበት
በእጣንሽ ታጅቤበት
በጤና አዳምሽ ታክሜ
በሳቅሽ ዳግም ለምልሜ
ለምለይሽ
ለማልረባሽ
'ማላዋይሽ
'ማልሰማሽ )

የሜክሲኮው ፊሊ ቡና ትልቅ የአምስት ብር ኖት በስዕል ተስሏል። ይወስዳል በቃ። ቡና እና ተስፋ'ዬ ይላል። ምናልባት ተስፋዬ የቡና ለቃሚው ስም ነው። እንደአንድ ብሩ ልጅ እያየን የሚፈግግበት ጊዜ የለውም። ሳየው ሸካራ እጆች ትዝ ይሉኛል። የደደሩ። ኑሮን በመታገል።

ደግሞ ከዚህ ስዕል በተቃራኒ በኩል ጆንያ ተሸክሞ የሚሄድ አለ። ቡና ይመስለኛል። እና ጸሀይ እየወቀጠው ይመስል ቀይ ሸሚዙን ጭንቅላቱ ላይ ጣል አድርጎ ፊቱን ቅጭም አድርጎታል በቃ።

ያሳስባል። ቡናችን ከየት መጣች ምናምን። ከዱር ወጥታ ሲኒያችን ውስጥ እንዴት ተገኘች?

እኔማ ሆንኹብህ ፈረንጅ እንዳለው ነው ሎሬቱ።

ብቻ እንኳን ለአለምአቀፍ የቡና ቀን አደረሳችሁ!

መስከረም 20/2016
@coffeeandscribblings
ትኩሳት remains one of the most misunderstood books in Amharic literature. It is a beautiful book which needs a liberated eye and definitely a better የሽፋን ገጽ please!
Read ትኩሳት! If you don't think it is a masterpiece, read it again!
This was the first book cover.
Forwarded from HOME || ቤት 🏚 (Yonathan)
🖤
ትኩሳትን እያነበብኹ ይህቺ የባህራን ሀገር ኢራን እንዴት ሆነች ስል፣ ዛሬ ከኢራን አንዲት human and women rights activist እስር ቤት እንዳለች የኖቤል የሰላም ሽልማት ተሸልማለች።ናርጊስ መሐመዲ። ስሟ።

ያው ግን የሚያብሰከስኩ ነገሮች አሉ።

ለሁሉም ሰው ሰላም የሚመጣበት ጊዜ በቶሎ ይምጣ።
#ትኩሳትንአንብቡ

@coffeeandscribblings
Playlist pour samedi
1. ዘሪቱ ከበደ- ቀን ቀን
የዘፈኑ ርዕስ ቀን ቀን በመሆን ፈንታ ማታ ማታ መሆን ነበረበት። ወይ ሲመሽ። የ90ዎቹ ወጣቶች ትዝ ይሉኛል። በBIC ደብዳቤ የሚጻጻፉ፣ ስልክ የሌላቸው፣ ማታ ማታ ቆንጆ ትዝ ሲላቸው የሚዘፍኑ እንጂ text ማድረግ የማይችሉ።

2.Ali Farka Toure- Ai Du
በሰማኹት ቁጥር ትዝ ትለኛለህ።
እኚህ ጋሼ አሊ ነጭ ጨርቃቸውን በጭንቅላታቸው እንደጠቀለለ፦
"የዚያ ልጅ ነገር እንዲሁ መቅረቱ ሀዘን ነው።" ይሉኛል።
"ጋሼ ዝም ብለው ይዝፈኑ" እላቸዋለሁ።
3. Cesaria Evora- Sodad
በሸገር አውቶብስ እየሄድኹ ቆሜያለሁ። ደግሞ ሰው ሁሉ ይገፋኛል። ዝናብ ደብድቦኛል። ጳጉሜ 3 ነው ደግሞ። ግን ይህቺ ሴትዮ በጆሮዬ sodad እያለች ደስ ደስ ይለኛል። የሚስጥር ተካፋይ የሆንሁ መስሎኛል። ንፋስ እንደመታው ቅጠል ቀስ ቀስ እያልሁ እወዛወዛለሁ። ውጪው ደግሞ በቢጫ ፈክቷል። ቢጫ ደግሞ የኔ ቀለም ነው። ይህች cesaria ሸገር አታውቅ፣ ጳጉሜ አታውቅ፣ አዲስ አመት አታውቅ፣ sodad ማለት ብቻ ነው የምታውቀው። ሌላ ቦታ ወሰደችኝ። ያልተለየኹት እና ያለኝ ነገር ሁሉ እየናፈቀኝ በረርኹ።
4. ቴዎድሮስ ታደሰ- ከተማው
ኧረ ምነው ? ስለምን ነው? ፍቅር ቅጣት የሚሆነው?

ጥሩ ጥያቄ ነው በእውነት።
ሰው መውደድ 12ተኛ ክፍል ለመድረስ አጸደህጻናት መግባት ነው እላለሁ። መኃሉ የቤት ስራ፣ የክፍል ስራ፣ መድገም፣ መገረፍ፣ በየጠዋቱ መቀስቀስ፣ ማትሪክ ምናምን የሚል ጣጣ ነው።

ኧረ ምነው? ስለምን ነው?

5. Kedarnath- Namo namo
ዘፈን እኮ አይደለም። መዝሙር ነው። ለአንዱ የሂንዱ አምላክ እንግዲህ። ግን ሆድ ይበትናል። ልጁ ሰው ተሸካሚ ነው። በቃ እየተሸከመ ሰው የሚያጓጉዝ። በጭንቅላቱ። እና ለዚህ የሂንዱ አምላክ መስገድ የፈለገችን ሴት እያሳሳቀ ምናምን ተራራ ለተራራ ተሸክሞ መቅደሱ ውስጥ ሲያደርሳት ምናምን ነው።
እና እንዲህ ይላል

* መች ጥም ታውቃለህ?
የጋንጀስ ወንዝ ምንጩ ጸጉርህ ነው።
* በሼል ውስጥ እንደሚያበራ እንቁ፣ በቀፎ ህይወቴ የምታበራው አንተ ነህ።

በቃ ደስ ደስ ይላል።

6. በዛወርቅ አስፋው- ትዝታ
እኔ በትዝታ አምናለኹም፣ እገረማለኹም። ትዝታ ብቻ የምሰማበት እና የምደነቅበት ጊዜ ነበር። ለምን ይሄ ጠይም ህዝብ አንድ ሙሉ ቅኝት ለትዝታ ጽንሰ ሀሳብ ሰጠ? ያጠያይቃል።

ትዝታ ብቻ ነው የልብ ጓደኛ
ለታመመች ህይወት መጽናኛ፣ መዳኛ
ቀን ብዙ ያሳያል እኔን ተካሁ እኔ
እያዩ ማለፍን ለመደልኝ አይኔ

በዛወርቅ ደግሞ በተለየ ነው ትዝታን የምትዘፍነው። እያዩ የማለፍ ቅላጼ አለው ድምጿ። እየተወዘወዘች አይደለም። ትንሽ ትንሽ እየናወዘች ብቻ። የሚጋልብ ፈረስ ሳይሆን የሚጎተት ባቡር።
ትላንትን ያየ ስለ ነገ ያውቃል እንዳለችው ትዝታ ድንቅ ቅኝት ነው።
@coffeeandscribblings
Forwarded from Hakim
Forwarded from Hakim
የCOVID 19 ወረርሽኝ ሲመጣ የአራተኛ አመት የህክምና ተማሪዎች ነበርን። 10 ወር ቤታችን ተቀምጠናል። ቀላል ጊዜ አልነበረም። ግን ድጋሚ መፈጠር የማይችል የተለየ እድልም ነበር። አለም ቆሞ እየጠበቀን ራሳችንን የተዋወቅንበት።

በዛ ጊዜ ካደረግናቸው ሚሊየን ነገሮች መኃል ፖድካስቶች ማዳመጥ ነበር። በቤት የፈለገውን እየሰራን ብዙ ፖድካስቶች አዳመጥን። በጣም አሪፍ ነገር ነው አልን።
ያም ጊዜ በህክምና ትምህርት ቤት ከለመድናቸው ነገሮች መዐት ነገሮች አንዱ እየዞሩ ስለስነተዋልዶ ጤና ማስተማር ነበር። እኔ ሱስ ቢጤ እየሆነብኝ ነበር። ለእናቶች፣ ለማታ ተማሪዎች፣ ለሀይስኩል ተማሪዎች፣ ለሌሎች የህክምና ተማሪዎች በየወር አበባ ንጽህና አጠባበቅ፣ በማህጸን ካንሰር፣ በጡት ካንሰር፣ በወሊድ መቆጣጠሪያዎች፣ በኤች አይ ቪ፣ በጾታዊ ጥቃት ላይ ማውራት ማስተማር ሁሌ የማደርገው ነበር።

ቤታችን ስንቀመጥ ያ መቅረት ሁሉ ቅር ቅር ይለኝ ነበር። ኋላ የፖድካስት ፍቅር እና ስነተዋልዶ ጤናን የማስተማር ፍቅር አንድ ላይ ሆነው ታንኳ ተፈጠረ።

ታንኳ፣ እኔና ጓደኞቼ በስነተዋልዶ ጤና ላይ የምንሰራት ፖድካስት ናት። እያነበብን፣ እየተናጋገርን በተለያዩ ሀሳቦች ላይ እየተናገሩ መቅዳት በቃ። ሰዎች መጋበዝ፣ ሰዎች የሚያስቡትን መጠየቅ። መወያየት። ( የሰው ልጅ ችግር ቁልፉ ሁሉ ውይይት ነው ብዬ በጽኑ ነው የማምነው እኔ።)
ስንጀምራት ፖድካስት አዲስ ነገር ነበር። ፍቅራችን እንጂ ሌላ የሚደግፋት ነገር አልነበረም።
በኋላ የፖድካስት አፕልኬሽን ተጀመረ። ተራኪ። እሱ ላይ ገባች።
Rise up የአንድ አመት ወጪሽን እሸፍንልሻለሁ አላት። ድምጸ መቅርጾች፣ ማይክራፎኖች ገዛች።
ትልቁ ደስታ ግን ያለው በዝግጅቱ ነው። ለአለም አቀፍ ኤድስ ቀን ቀዝቃዛ ወላፈንን ማየት፣ ሰዎችን ስለአእምሮ ጤናና ስነተዋልዶ መያያዝ መጠየቅ፣ በግጭቶች ላይ ጥናቶችን ማንበብ፣ የድምጽ ጥራትን ለማስተካከል እና ድምጾችን ለማዋኃድ መማሩ ላይ ነው።

ይህን ሀሳብ ስናስበው ጀምሮ እስካሁን ያልተለየን St. Paul Institute for reproductive health and rights በጣም ምስጋና ይገባዋል። ብዙ ሀሳቦች የሚደግፋቸውና የሚያበረታታቸው በማጣት ቀርተዋል። የኛ አንዱ ያልሆነው በናንተ ነው።

ታንኳ የዛሬ አመት፣ የዛሬ አምስት አመት ትኑር አትኑር እንጃ። ግን በየሳምንቱ ለሁለት አመታት ስለስነተዋልዶ እያስተማርን ተምረንባታል። ሌሎች መቶዎችም እንደዚሁ። በዚህም ደስተኛ ነኝ።

ውይይቶችን ለጤናና ለሌሎችም ችግሮች እንደመፍትሔ የመጠቀም ባህል... ጥሩ ነው።

እናንተም ታንኳን እየሰማችሁ ሀሳባችሁን አኑሩ።

Linktree: https://linktr.ee/tankua
Teraki: https://terakiapp.page.link/P7upqa1vy7JHap9dA

ዶ/ር ሎዛ አድማሱ

@HakimEthio
* እንደጦርነት በቃ አስቀያሚ ነገር የለም። በቃ በጣም አስቀያሚ ነው። ጦርነት ማሰብ የማትችለውን መስዋዕትነት ነው የሚያስከፍልህ። በቃ እኔ ሌላ ቦታ ስለሆንሁ አትከፍልም ትል ይሆናል። ግን በቃ ትከፍላለህ። የነገራት ጅማሬ እና ፍጻሜ ካርታ የለም እንጂ ቢኖር... ወይኔ ቢኖር... ይሄኔ ያችን ልጅ ያጣኃት በዛኛው ጦርነት ሰበብ ነው። አስቀያሚ ነው። ካሙ ጦርነትና ወረርሽኝ ሁሌ ሰው ያስደነግጣል እንጂ መች ከሰው ታሪክ ጠፍቶ ያውቃል ይላል። ጠፍቶ አለማወቁም ያስደነግጣል። በምንም አይነት ቅርጽ ቢሆን ጦርነት አስቀያሚ አስቀያሚ አስቀያሚ ነው።
@coffeeandscribblings
2025/06/30 15:51:51
Back to Top
HTML Embed Code: